ብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ቃል ነው
የውይይት ጥያቄ፡- 2ኛ ጢሞ. 3፡16-17 ና 2ኛ ጴጥ. 1፡20-21 አንብብ። ሀ) እነዚህ ቁጥሮች መጽሐፍ ቅዱስን በማስገኘት ረገድ ስለ እግዚአብሔር ድርሻ ምን ይናገራሉ? ለ) እነዚህ ቁጥሮች መጽሐፍ ቅዱስን በማስገኘት ረገድ የሰው ድርሻ ምንድን ነው ብለው ያስተምራሉ? ሐ) እነዚህ ቁጥሮች እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን ለእኛ የሰጠበት ምክንያት ምንድነው ብለው ያስተምራሉ? መ) መጽሐፍ ቅዱስ በአንተ ሕይወት ውስጥ ለትምህርት፥ ለተግሣጽ፥ ልብን ለማቅናትና በጽድቅ ላለው ምክር እንዴት እንዳገለገለ ግለጥ። መጽሐፍ ቅዱስ ምንድን ነው? እንደ ቁርአንና ሌሎች ሃይማኖታዊ ጽሑፎች ሁሉ የሰው ሥራ ነውን? ወይስ ሰውን መሣሪያ አድርጎ ሳይጠቀም እግዚአብሔር በቀጥታ ለሰዎች የሰጠው ነው? ዓላማውስ ምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ በራሱ ኃይል ያለው የምትሀት መጽሐፍ ነውን? እነዚህ ብሉይ ኪዳንን ማጥናት ከመጀመራችን በፊት ልንመልሳቸው የሚገቡ በጣም አስፈላጊ ጥያቄዎች ናቸው። ክርስቲያኖችም ሆኑ አይሁዶች ብሉይ ኪዳን የተለየ የእግዚአብሔር ቃልና በውስጡም እግዚአብሔር ራሱንና ዓላማውን ለሰው ልጅ የገለጠበት መጽሐፍ እንደሆነ ይናገራሉ። ክርስቲያኖች ከአይሁዶች የሚለዩት አዲስ ኪዳንም የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ ስለሚያምኑ ነው። ብዙውን ጊዜ ክርስቲያኖች ስለ እግዚአብሔር ቃል ሁለት የተሳሳቱ ግንዛቤዎች አሉአቸው። የመጀመሪያው፥ ብዙ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር እንዲጻፍ የፈለገውን ቃል ለተለያዩ ሰዎች ቃል በቃል አጽፎአቸዋል ብለው ያስባሉ፤ ስለዚህ አንዳንዶች ብሉይ ኪዳን በሚጻፍበት ጊዜ ጸሐፊዎቹ ምንም ድርሻ አልነበራቸውም ብለው ያስተምራሉ። በዚህ መልክ የተጻፉ አንዳንድ ክፍሎች ቢኖሩም (ለምሳሌ ዘጸ. 24፡4-7)። እነዚህን የብሉይ ኪዳን ክፍሎች የጻፉት ጸሐፊዎች ግን የሚጽፉት ጉዳይ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገባ የቅዱሳት መጻሕፍት አካል መሆኑን እንኳ አያውቁም ነበር። አልፎ አልፎም ጸሐፊዎቹ ከሌሎች መጻሕፍት የቀዱበት አጋጣሚ ነበር (ለምሳሌ፡- ዘኁል. 22፡14-15፤ ኢያ. 10፡13)። በሁለተኛ ደረጃ፥ እራሳቸውን ክርስቲያን አድርገው የሚቆጥሩ አንዳንድ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ ያለማሰባቸው ነው። ይልቁንም መጽሐፍ ቅዱስ የሰው ሥራ እንደሆነ ያስተምራሉ። መጽሐፍ ቅዱስ የአይሁድን ሃይማኖታዊ ልምምድ ለመረዳት የሚጠቅም እንጂ፥ እውነት አይደለም ብለው ያስባሉ። ሌሎች ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስ እንደ ቁርአን ወይም እንደ ሂንዱ እምነት መጻሕፍት ነው፤ ምክንያቱም ሁሉም የሚናገሩት ሰው እግዚአብሔርን ለማወቅ ያደረገውን ጥረት ነው ይላሉ። አንዳንድ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ገና ተጽፎ አላለቀም በማለት ዛሬም ቢሆን «የእግዚአብሔር ቃል» የሚሏቸውን ብዙ የሐሰት ትምህርቶች (ኑፋቄዎች) በመጨመር ላይ ይገኛሉ። የእነዚህ ትምህርቶች አመንጪ የሆኑት ሰዎች አሳባቸውን ከመጽሐፍ ቅዱስ እኩል በመቁጠር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያክላሉ፤ (ለምሳሌ፡- የይሖዋ ምስክሮች፥ የክርስቲያን ሳይንስ አማኞች፥ የሞርሞን ተከታዮች፥ ወዘተ)። ስለ መጽሐፍ ቅዱስ በርካታ የተሳሳቱ አሳቦች በመኖራቸው፥ እምነታችን የተመሠረተውም በእርሱ ላይ በመሆኑ፥ ክርስቲያን የሆንነው ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ማመን ያለብን ነገር ምን እንደሆነ ግልጽ አሳብ ሊኖረን ያስፈልጋል። ስለዚህ ጉዳይ አጭር አሳብ ከዚህ እንደሚከተለው ቀርቧል፡- መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ነው። በ2ኛ ጢሞ. 3፡16 እና 2ኛ ጴጥ. 1፡19 መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ እንደሆነና ጸሐፊዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው እንደጻፉት እናነባለን። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን ራሱ በግልጥ ይናገራል፤ ስለዚህ እኛ ክርስቲያኖች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ የሚከተሉትን ነገሮች እናምናለን፡- ሀ. መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሙሉ ሥልጣን አለው። የእግዚአብሔርን ቃልና ፍላጎቶች ይዟል፥ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን በምናነብበት ጊዜ እግዚአብሔር በመካከላችን ያለና የሚናገረን ያህል ነው። እግዚአብሔር የተናገረውም የተጻፈውም ቃሉ እኩል ሥልጣን አላቸው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የእግዚአብሔርን ቃል ስለ መስበክም ሆነ ስለ ማስተማር ይህ ምንን ያስተምረናል? ለ) ሥልጣኑ ያለው የት ላይ ነው? (ኢሳ. 55፡11 ተመልከት)። የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንደ መሆናችን መጠን ሥልጣን ያለው የእግዚአብሔር ቃል ብቻ እንደሆነ ማስታወስ አለብን። የእኛ ቃላት ሥልጣን የሌላቸውና ስሕተት ሊገኝባቸው የሚችሉ ናቸው፤ ስለዚህ በምንሰብክበትና በምናስተምርበት ጊዜ የእኛ ኃላፊነት ሰዎች የእኛን አሳብ ሳይሆን የእግዚአብሔርን ቃል እንዲሰሙ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ያለ አንዳች ስሕተት በግልጥ ማወጅ ነው (2ኛ ቆሮ. 4፡1-5፤ 2ኛ ጢሞ. 2፡15 ተመልከት)። ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል በሚሰሙበት ጊዜ ሥልጣኑና ኃይሉ ሕይወታቸውን ይለውጠዋል። ለ. መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔርም የሰውም ሥራ ነው። መጽሐፍ ቅዱስን ለማስገኘት እግዚአብሔር ሰዎችን በመሣሪያነት በመጠቀም በራሳቸው ቃላትና የአስተሳሰብ መንገድ እንዲጽፉት አደረገ፤ ነገር ግን የጻፉት ቃል ውጤት ብሉይ ኪዳንን ጨምሮ በሙሉ የእግዚአብሔር ቃል ነው። ኢየሱስ እንዳለው በመጽሐፍ ቅዱስ ከሁሉ የምታንሰው ፊደል ወይም ነጥብ እንኳ በእግዚአብሔር ቁጥጥር ስለ ተጻፈ ሳይፈጸም አያልፍም (ማቴ. 5፡18 ተመልከት)። ሐ. መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሥራ ስለሆነ አንዳችም ስሕተት የለበትም። እግዚአብሔር ሊዋሽና ስሕተት ሊሠራ ጨርሶ እንደማይችል ሁሉ (ዕብ. 6፡ 18) ቃሉም አይዋሽም። ስለዚህ የእግዚአብሔር ቃል በግልጥ ከሚያስተምረው ነገር ጋር የማይስማማ ማንኛውም ዓይነት አመለካከት ስሕተት ነው። እውነት ምን እንደሆነ የሚተረጉመው የእግዚአብሔር ቃል መጽሐፍ ቅዱስ ነው። በማንኛውም ጊዜ እኛም ሆንን ሌሉች የአንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን እውነትነት በሚመለከት መጠየቅ ስንጀምር፥ በእግዚአብሔር ቃል ላይ እንፈርዳለን፥ በእግዚአብሔር ላይም ፈራጆች ሆንን ማለት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሥልጣን አለው እያልን ትክክል መሆን አለመሆኑን መጠየቅ አንችልም። መጽሐፍ ቅዱስ ስሕተት ካለው በሕይወታችን ላይ ምንም ሥልጣን ሊኖረው አይችልም። ይሁን እንጂ ይህንን ዐረፍተ ነገር በመጠኑ ግልጽ ማድረግ ይኖርብናል። መጽሐፍ ቅዱስ በቅጅዎቹ ሳይሆን በመጀመሪያው አንዳችም ስሕተት የለበትም። ይህም ማለት ሙሴ፥ ዳዊት፥ ጳውሎስ ወይም ሉቃስ ቅዱሳት መጻሕፍትን ሲጽፉ ሙሉ ለሙሉ የእግዚአብሔር ቃልና አንዳችም ስሕተት የሌለበት ነገር ጽፈዋል፤ ነገር ግን ሌሎች ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል በሚገለብጡበት (በሚቀዱበት) ጊዜ አንዳንድ ስሕተቶች ነበሩ ማለት ነው። በጥንት ዘመን በርካታ መጻሕፍትን ለማባዛት የሚያስችሉ ማተሚያ ቤቶች እንዳልነበሩ ማስታወስ ያስፈልጋል። ዛሬ እንኳ መጽሐፍ ቅዱስ በሚታተምበት ጊዜ የሆሄያት ስሕተት ሊኖር ይችላል፤ ስለዚህ ቅዱሳት መጻሕፍት በእጅ ሲጻፉ በዘመናት ሁሉ የነበሩ ጸሐፊዎች አንዳንድ ስሕተቶችን ሠርተዋል፥ ስለዚህ በአሁኑ ጊዜ ባሉት በርካታ ትርጉሞች ውስጥ ተርጓሚዎቹ አንዳንድ ጥቅሶችን በተለየ መንገድ ሊተረጉሙ እንደሚችሉ በመግለጥ የግርጌ ማስታወሻዎችን ጽፈዋል። የውይይት ጥያቄ፥ ማር.16ን በአዲሱ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ተመልከት። ከ9-20 ስላሉት ቁጥሮች በገጹ በስተግርጌ ላይ ምን ተጽፏል? ይህንን ሐቅ ለመረዳት ያስቸግራል። በአሁኑ ዘመን፣ የመጀመሪያዎቹ ጹሑፎች የትኞቹ እንደነበሩ ለመወሰን ዐብይ ሥራቸው አድርገው የያዙት የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን አሉ። በሺህ የሚቆጠሩ የብሉይና የአዲስ ኪዳን ቅጂዎችን በመመልከት፣ የመጀመሪያው ቃል የቱ እንደነበር ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ለመወሰን ይታገላሉ። የእነዚህ ምሁራን ሥራ ያላለቀ ስለሆነና እኛም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስላሉ ጥቅሶች መቶ በመቶ እርግጠኞች መሆን ባንችልም፥ ሆኖም ግን ምሁራኑ የሚከተሉትን ነገሮች ይነግሩናል። መጽሐፍ ቅዱስ ከማንኛውም ሌላ ጥንታዊ መጽሐፍ በተሻለ ሁኔታ ተጠብቋል፤ ምክንያቱም አይሁዶችና ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ ያምኑ ስለነበር በትክክል ሊገለብጡት ይችሉ ዘንድ ከፍተኛ ጥንቃቄ አድርገዋል፤ ስለዚህ ከቁርአንም ሆነ ከማንኛውም ሌላ ጥንታዊ መጽሐፍ በተሻለ ሁኔታ ትክክለኛነቱ የተጠበቀ ነው። ደግሞም በሚጽፉበት ጊዜ ጸሐፊዎቹን የመራቸው መንፈስ ቅዱስ በመሆኑ፥ ቅጂዎቹ ለዘመናት በሚጻፉበት ጊዜ ሁሉ ጉልህ ስሕተት እንዳይፈጽሙ ረድቶአቸዋል። በተለያዩ ቅጂዎች መካከል ያሉት ልዩነቶች በአንድነት ሲታዩ፥ የአጠቃላዩ መጽሐፍ ቅዱስ ትንሽ ክፍል ናቸው። በሁሉም ቅዱሳት መጻሕፍት መካከል ስምምነት ስላለ፥ በእጃችን ያለው መጽሐፍ ቅዱስ ዘጠና ከመቶ በላይ (90%) ከመጀመሪያው መጽሐፍ ቅዱስ ጋር አንድ ዓይነት እንደሆነ እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን። በቅዱሳት መጻሕፍት ቅጂዎች መካከል ያለው ማንኛውም ልዩነት በየትኛውም የመጽሐፍ ቅዱስ ዋና ትምህርት ላይ ለውጥ የሚያመጣ አይደለም። ስለ እግዚአብሔር፥ ስለ ክርስቶስ ወይም ስለ መንፈስ ቅዱስ ማንነት፥ ስለ ድነት (ደኅንነት) መንገድ፥ ወዘተ ባለን ግንዛቤ ላይ የሚያመጡት አንዳችም ለውጥ የለም፤ ልዩነቶቹ እምነታችንን የሚለውጡ አይደሉም (ለምሳሌ በዕዝ. 2፡3-70 እና በነህ. 7፡6-73 ያሉትን ዝርዝሮች አነጻጽር። በእነዚህ ሁለት ዝርዝሮች ውስጥ ያሉትን ልዩነቶች ጥቀስ)። መ. መጽሐፍ ቅዱስ በነገሮች ሁሉ ላይ የመጨረሻው ባለሥልጣን ነው። እግዚአብሔር ማን እንደሆነ፥ ቀድሞ ምን እንዳደረገና ወደፊትም ምን እንደሚያደርግ፥ እንዲሁም ከፍጥረቱ የሚፈልገው ነገር ምን እንደሆነ በመናገር ረገድ የመጨረሻው ባለሥልጣን መጽሐፍ ቅዱስ ነው። ሌሎች እምነቶችና ልምምዶች በሙሉ መመዘን ያለባቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት
ብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ቃል ነው Read More »
