የማርቆስ ወንጌል የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ምልከታ እና ትርጓሜ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቅፍርናሆም በተመለሰ ጊዜ ቃሉን ለመስማት የመጣው ሕዝብ ብዛት እስከ ደጃፍ ድረስ ቦታ እስኪታጣ ድረስ ነበር። በዚህ መሃል አራት ሰዎች አንድ ሽባ የሆነ ሰው ተሸክመው መጡ ፤ ነገር ግን ከሰዎች ብዛት የተነሳ ወደ ጌታ መቅረብ አልቻሉም። እነዚህ ሰዎች ግን ተስፋ አልቆረጡም ፤ ይልቁንም ወደ ቤቱ ጣሪያ ወጥተው ጣሪያውን በመንደል ሽባውን ሰው ከነአልጋው በኢየሱስ ፊት አወረዱት። ጌታም የእነርሱን እምነት አይቶ ለሽባው ሰው “ልጄ ሆይ ኃጢአትህ ተሰረየችልህ” አለው። በዚያ የነበሩ ጻፎች ግን በልባቸው “እግዚአብሔር ብቻ ካልሆነ በቀር ኃጢአት ሊያስተሰርይ ማን ይችላል?” በማለት ይከራከሩ ነበር። ኢየሱስም የልባቸውን አውቆ ኃጢአትን ይቅር የማለት ሥልጣን እንዳለው እንዲያውቁ ሽባውን “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ወደ ቤትህ ሂድ” አለው። ሰውየውም ወዲያው ተነስቶ አልጋውን ተሸክሞ በሁሉ ፊት ወጣ።
ይህ ታሪክ እጅግ ጥልቅ የሆኑ መንፈሳዊ እውነቶችን ይዞልናል። በመጀመሪያ የአራቱ ጓደኛሞች ተግባር “ማህበራዊ እምነት” ወይም ለሌሎች መዳን የምናደርገውን ጥረት ያሳያል። ጌታ ተአምራቱን ያደረገው ሽባው በራሱ ባሳየው እንቅስቃሴ ሳይሆን በጓደኞቹ ጽኑ እምነት ምክንያት መሆኑን ማርቆስ ይነግረናል ፤ ይህም እኛ ለሌሎች በጸሎትና በድካም የምናደርገው ተፅዕኖ ውጤት እንዳለው ያስገነዝበናል።
በሁለተኛ ደረጃ ጌታ ለሽባው ሰው ከሥጋዊ ፈውስ ይልቅ የኃጢአት ይቅርታን ማስቀደሙ የሰው ልጅ ትልቁና ዋነኛው ችግር የነፍስ በሽታ መሆኑን ለማሳየት ነው። ኃጢአት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ያለውን ግንኙነት ያበላሸ ዋነኛ ጠላት በመሆኑ ፤
ጌታ መጀመሪያ የውስጥ ሰላሙን መለሰለት። ጻፎቹ “እግዚአብሔር ብቻ ካልሆነ በቀር ኃጢአት ሊያስተሰርይ ማን ይችላል?” ማለታቸው እውነት ቢሆንም ፤ ስህተታቸው ግን በፊታቸው የቆመው ኢየሱስ እግዚአብሔር መሆኑን አለማወቃቸው ነው።
በመጨረሻም ጌታ “ኃጢአትህ ተሰረየችልህ” ከሚለው የማይታይ መንፈሳዊ ቃል ይልቅ “ተነሣና ሂድ” የሚለው የሚታይ ተአምር ቀላል እንደሆነ አስረድቷል። ነገር ግን የሚታየውን ተአምር በማድረግ የማይታየውን የኃጢአት ይቅርታ የማድረግ ሥልጣን እንዳለው አረጋገጠ። ይህ ድርጊት ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ልጅን ከሥጋ ደዌ ብቻ ሳይሆን ከዘላለም የኃጢአት እስራት ነጻ የሚያወጣ አምላክ መሆኑን በግልጽ ያሳያል። እውነተኛ ፈውስ የሚጀምረው ከልብ ውስጥ መሆኑንና ጌታችን ደግሞ ለሁለቱም ፍጹም ባለቤት መሆኑን እንረዳለን።
ተግባራዊ የውይይት ጥያቄዎች
👉ሽባውን የተሸከሙት አራት ሰዎች ያሳዩት እምነትና ጥረት ምን ያስተምረናል?
👉ኢየሱስ ከፈውሱ ቀድሞ ለምን የኃጢአት ይቅርታን አወጀ?
👉ጻፎቹ በልባቸው “ይህ ሰው ለምን እንዲህ ይናገራል?” ማለታቸው የእነርሱን ሃይማኖታዊ አቋም እንዴት ይገልጻል?
👉”ኃጢአትህ ተሰረየችልህ” ከማለትና “ተነሥተህ ሂድ” ከማለት የትኛው ይከብዳል? ለምን?
👉”የሰው ልጅ” የሚለው ርዕስ በዚህ ክፍል ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ መጠቀሱ ምን ዓይነት ሥነ-መለኮታዊ ትርጉም አለው?
👉ሽባው ሰው ተነሥቶ በአልጋው መሄዱ በታዛቢዎች ላይ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረ?
👉ይህ ተአምር የኢየሱስን መለኮታዊ ሥልጣን እንዴት ያረጋግጣል?
👉በጣራው ላይ ቀዳዳ መሥራታቸው ስለ ጽናትና ስለ ፍላጎት ጥልቀት ምን ያስተምራል?
👉ኢየሱስ የሰዎችን ልብ ማወቁና ሃሳባቸውን መረዳቱ ስለ መለኮታዊነቱ ምን ይናገራል?
👉ኃጢአት ከሥጋዊ ደዌ ጋር ስላለው ተያያዥነት በዚህ ክፍል ምን ፍንጭ እናገኛለን?
