የአዲስ ኪዳን መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት

2ኛቆሮ.2:12-13

ጥያቄ 7. በቁጥር 12 ላይ “ለጌታ ሥራ በር ምንም ቢከፈትልኝ” ሲል ስለዚህ በር ሰፋ አድርገህ አብራራ።  ሐዋርያው ጳውሎስ አገልገሎቱ በአንድ ቦታ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ ቦታዎች አንደሆነ በሐዋርያት ሥራ እናነባለን። አሁንም ሐዋርያው በቆርንቶስ ቤተ ክርስቲያን ችግር እንዳለ ከሰማ በኋላ ችግሩን እንዲያርሙ ልቡ በሃዘን ተሞልቶ 1ኛ ቆሮንቶስን ጻፈ። የደብዳቤውንም ውጤት ቲቶ እንዲያመጣለት በታላቅ ናፍቆት ይጠባበቅ ነበር።  ልቡ በሃዘን ስለተሞላ የቲቶን መልስ ለመጠበቅ ወደ መቄዶንያ ተሻገረ። ይህን እርምጃ የወሰደው ለአገልግሎት የተከፈተለትን በር ትቶ ነው። በ2ኛ ቆሮ. 7:5 ላይ ይህንን ታሪክ ይቀጥላዋል። አሁን ግን ለጊዜው በሌላ ትምህርት ላይ ነው የሚያተኩረው።  ስለ በር መከፈት በአጭሩ እንወያይ። በዚህ ቃል ላይ እንደምናየው በር ከፋቹ ሐዋርያው ሳይሆን ራሱም በሩ በራሱ ሳይሆን ሌላ ከፋች አለው፤ እርሱም እግዚአብሔር ነው። ስለ በር መከፈት ሐዋርያው ጸሎት እንዲደረግለት በቆላ.4:3 ይናገራል። ይህም በር ሁለት አቅጣጫ አለው። አንደኛው ሐዋርያው ወንጌልን ይዞ በአንድ ሥፍራ እንዲሄድ የሥፍራው በር መከፈቱን ያመለክታል። ሁለተኛው አቅጣጫ ደግሞ እግዚአብሔር የአድማጮችን ልብ መክፈቱን ያመልክታል። ለዚህ ማስረጃ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት የሐዋ. 14:27፤ 16፡14። ሰው በወንጌል የሚያምነው እግዚአብሔር ልቡን ሲከፍትለት ስለሆነ ጌታ የሰዎችን ልብ በመክፈት ለወንጌል ሥራ መሳካትን እንዲሰጥ ልንጸልይ ይገባል። የእኛንም ልብ ከፍቶ የወንጌልን ብርሃን በልባችን ስላበራ ስሙ የተባረከ ይሁን።  ጥያቄ 8. እግዚአብሔር እንዴት አድርጎ የአገልገሎት በር ለአንተም ሆነ ለቤተ ክርስቲያንህ አንደከፈተ ምሳሌዎችን በመስጠት አስረዳ። 

2ኛቆሮ.2:12-13 Read More »

2ኛ ቆሮ.2:5-11

ጥያቄ 5. በዚህ ክፍል አጥፊው በሃዘን እንዳይዋጥ ቤተ ክርስቲያኒቱ ይቅር እንድትለው ያዛል፡፡ ይህ አጥፊ ጥፋቱ ምን ነበር? (1ኛ ቆሮ.5፡1-2)።  በቁጥር 5 ላይ አጥፊው የበደለው የክርስቶስን ቤተ ክርስቲያን በሙሉ እንጂ በተለይ ሐዋርያውን እንዳልሆነ ያስገነዝባቸዋል። በቁጥር 6 «ከእናንተ የምትበዙት የቀጣችሁት ቅጣት ይበቃዋልና» ይላል። ከእናንተ የምትበዙት ሲል በስብሰባቸው ላይ በድምፅ ብልጫ የተወሰነውን ውሳኔ ያመለክታል። በ1ኛ. ቆሮ.5፡3-5 ላይ ከእንጀራ እናቱ ጋር የዝሙት ሥራ የፈፀመ አባል መቀጣት እንዳለበት ጽፎ ነበር። የቆሮንቶስም መዕመናን ይህን ሐዋርያዊ ትዕዛዝ ፈጸሙ። ተሰብስበው በድምጽ ብልጫ ቅጣት ወሰኑ። ይህም ቅጣት ንስሐ እስኪገባ ድረስ ከቤተ ክርስቲያን ማኅበር መስወገድ ነበር። ይህን ቅጣት የወሰኑት አብዛኞቹ ሲሆኑ ጥቂቶች ግን የሐዋርያውን ትእዛዝ እንዳልተከተሉ እንረዳለን፡፡  አሁን ግን ይህ ሰው ንስሐ ስለገባ እንደገና በፍቅር እንዲቀበሉት ያዛል፤ «የቀጣችሁት ቅጣት ይበቃዋልና እንደዚህ ያለው ከልክ በሚበዛ ሃዘን እንዳይዋጥ ይልቅ ተመልሳችሁ ይቅር ማለትና ማጽናናት ይገባችኋል»። በክርስቶስ መንግሥት ሰው ንስሐ ከገባ ምሕረትን የሚቀበል መሆኑን ቃሉ ይመሰክራል፤ (1ኛ ዮሐ.1:9-2:1)።  በቁጥር 8 መጨረሻ ላይ “እለምናችኋለሁ” ካለ በኋላ አራት ነጥብ መኖር አለበት። ቁጥር 9 “ስለዚህ ደግሞ ጽፌ ነበርና” የሚለው ከሚከተለው ጋር እንጂ ካለፈው ጋር አይያያዝም፡፡ ከዚህ ቀደም የጻፈው ንስሐ የገባውን እንዲቀበሉት ሳይሆን እንዲቀጡት ነበር፤ (1ኛ ቆሮ.5፡1)። ስለዚህ ቁጥር 9 የሚለው አጥፊው ይቀጣ ብዬ የጻፍሁት መታዘዛችሁን ለማየት ነበር፤ በመቅጣታችሁ መታዘዛችሁን አየሁ! ያ የጻፈላቸው ደብዳቤም 1ኛ ቆሮንቶስ ነበር።  ንስሐ የገባን ሰው ቶሎ በፍቅር አለመቀበል ለሰይጣን እድል መስጠት ነው ሲል ሐዋርያው ያስጠነቅቃል፤ (ቁጥር 11)። የሰይጣን አንዱና ዋነኛው ግቡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ክፍፍልን ፈጥሮ በክርስቲያኖች ሕይወት ውስጥ ተስፋ መቁረጥንና ስደትን ማስከተል ነው። አንድ ክርስቲያን ወደ ትክክለኛው መንገድ ከተመለሰ በኋላ ምንም ዓይነት የፍቅርና የይቅርታ መንፈስ የማያይ ከሆነ ተስፋ ይቆርጥና እምነቱን ይተዋል። በቤተ ክርስቲያኖቻችን ውስጥ ክፋት የሥነ ሥርዓት መሠረት ከሆነና አባሎቻችን ይቅርታ ለማድረግና ፍቅርን ለመግለፅ ያላቸው ፍላጎት ዝቅተኛ ከሆነ የዚህ ዓይነት ሁኔታ ይፈፀማል፡፡ ሰይጣን የምንሰጠውን ማንኛውንም አጋጣሚ ቤተ ክርስቲያንንና ሕይወታችንን ለማበላሸት እንደሚጠቀምበት አስተውሉ።  ጥያቄ 6. ትክክለኛ ያልሆነውን የሥነ ሥርዓት እርምጃ በመጠቀም ወይም ይቅር ባይ ባለመኖሩ ሰይጣን እንዴት አድርጎ የምታውቀውን ሰው እንዳጠቃ ምሳሌ በመስጠት አስረዳ።  አንዳንድ ሊቃውንት አጥፊው ሐዋርያው ጳውሎስን በሁለተኛ ጉብኝቱ ጉዞው የተቃወመው ሰው ነው ብለው ይገምታሉ። ለዚህ ግን ምንም ማስረጃ የለም። እንዲያውም ይህ እንዳልሆነ የምንገነዘበው ሐዋርያው አጥፊውን ሳይገስጽ ዝም ብሉ ሄዶ በሩቅ ሳለ ቤተ ክርስቲያኑን ቅጡት ቢል ኖሮ እውነትም ከሳሾቹ እንዳሉት በመልእክቱ እንጂ ፊት ለፊት ፈሪ ነበር ማለት ነው፤ (10:10 እና 11)። ይህንም አንቀበልም። አጥፊው ከላይ እንደተባለው ዝሙትን የሠራው ነው። 

2ኛ ቆሮ.2:5-11 Read More »

2ኛ ቆሮ.1፡23-2:4

ጥያቄ 1. በቁጥር 23 ላይ ሐዋርያው በመሐላ ነገሩን ሲያረጋገጥ እናነባለን፤ ይህን ከማቴ.5፡37 ጋር በማስተያየት አስታራቂ ሃሳብ ጻፍ።  ጥያቄ 2. ሐዋርያው ጉብኝቱን የሰረዘው ለምንድነው ይላል?  ቁጥር 23፡- በምዕራፍ 1 ቁጥር 15 እና 16 ላይ አንደጠቀሰው ሐዋርያው ያሰበውንና የሰጣቸውን ሁለት ጊዜ የምጎብኘት ተስፋ እንዳልጠበቀ በማስታወስ ይህንን ያደረገው ለጥቅማቸው እንጂ ቃልን ያለመጠበቅ ጉዳይ እንዳልሆነ እንዲረዱለት በመሐላ ያረጋግጥላቸዋል።  “በነፍሴ ላይ እግዚአብሔርን ምስክር እጠራለሁ”። ይህ የመሐላ አነጋገር ነው። መሐላ አስፈላጊ የሆነበት ምክንያት በዓለም ውስጥ በኃጢአት ምክንያት ውሸት ስለበዛ ነው። እንኳን ሰው ቀርቶ እግዚአብሐርም ራሱ ነገሩን በመሐላ እንደሚያረጋግጥ በሚከተሉት ጥቅሶች ውስጥ እናነባለን፤ (ሉቃ.1:73፤ ዕብ. 6፡13-16)። በማቴ 5፡37 ላይ ጌታ መሐላን ይከለክላል። ይህም በፊት የተፈቀደውን መከልከሉ ሳይሆን በእርሱ ዘመን የነበሩ ፈሪሳውያን በመሐላ ካልተናገሩ በቀር መዋሽት የተፈቀደ ነው ይሉ ነበርና፤ እንዲሁም መተማመን ስለጠፋ በትንሽ ነገር እንኳ ይምሉ ስለነበር ነው።  ቁጥር 24፡- «በእምነታችሁ በእናንተ ላይ የምንገዛ አይደልንም። በእምነታችሁ ቆማችኋል» ። እንኳን ሌላ የቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቀርቶ ሐዋርያው እንኳ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ማገልገል እንጂ የመግዛት መብት እንዳልነበረው ያስረዳል። የቤተ ክርስቲያንም ሸማገሌዎች የእግዚአብሔርን ሕዝብ ማዘዝ የሚችሉት የክርስቶስን ትእዛዝ በማስተላለፍ ብቻ እንጂ ራሳቸው ትእዛዝ እያወጡ አለመሆኑን ይህ ቃል ያስተምረናል።  ጥያቄ 3. ሀ/ መሪነትን እንደ አገልገሎት ሳይሆን እንደ መግዛት የሚያዩ አንዳንድ መሪዎች በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ይገኛሉ? ለ/ አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ሕዝቡን በጭካኔ ከሚገዛ አብሮ በስምምነት ቢያገለግል የሚሻለው ለምንድነው?  2:1:- ሐዋርያው ከዚህ በፊት በሃዘን እንደጕበኛቸው እንረዳለን። ይህም ጉብኝት የመጀመሪያው አልነበረም። ግን በመጀመሪያ ወንጌልን ከሰበከ በኋላ ተመልሶ እንደጎበኛቸውና ያም ጉብኝት የሃዘን ጊዜ እንደበር ይናገራል። በጉብኝቱም ፋንታ በሃዘን ደብዳቤ ጻፈላቸው። ይህም ደብዳቤ 1ኛ ቆሮንቶስ ነው። አሁን ግን ንስሐ መግባታቸውን ስለተረዳ ጉብኝቱ የሃዘን ሳይሆን የደስታ ስለሚሆን ለሦስተኛ ጊዜ ሊጎበኛቸው እንደተዘጋጀ ይጽፋል (7:6-13፤ 12:14)።  እንደ ወላጅ ወይም እንደ ቤተ ክርስቲያን መሪ ለወንጌል ቅድስናና ለሰውዬው ዕድገት ስንል ጠንከር ያሉ የሥነ ሥርዓት እርምጃዎችን መውሰድ አለብን። በ1ኛ ቆሮንቶስ ምዕራፍ 5 ላይ ክፉው ሰውዬ ከቤተ ክርስቲያን ሕብረት ውጪ መሆን ነበረበት። እንደዚህ ዓይነት ውሣኔ በምንወስንበት ጊዜ ይህንን ውሣኔ እንድናደርግ የገፋፋንን በስተጀርባ ያለውን ሃሳባችንን መመርመሩ ተገቢ ነው። ከቅናት፥ ከጥላቻ ወይም ከንዴት የተነሣ መሆን የለበትም። በምትኩ የዚህ የሥነ ሥርዓት እርምጃ መሠረት ፍቅር መሆን አለበት። ልክ እንደ ጳውሎስ እርምጃው በእንባና በሃዘን የታከለ መሆን ይገባዋል። ሁሌ አንድ የሥነ ሥርዓት እርምጃ ለመውሰድ የሚያነሳሳን ምክንያት ከፍቅር የመነጨ መሆን አለበት እንጂ ከንዴት የመነጨ መሆን የለበትም።  ጥያቄ 4. ይህ ዓይነቱ ቅጣት ብዙ ጊዜ ወላጆችም ሆኑ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ከሚወስዷቸው የሥነ ሥርዓት እርምጃዎች ለየት የሚለው እንዴት ነው?

2ኛ ቆሮ.1፡23-2:4 Read More »

2ኛ ቆሮ.1:15-22

ጥያቄ 12. በቁጥር 15 እና 16 እንደተጻፈው ጳውሎስ ምን ፕላን አውጥቶ ነበር?  ጥያቄ 13. ይህን ቃሉን አላመፈጸሙና የሰበከው የወንጌል እውነተኝነት ምን ግንኙነት እንዳለው እንረዳለን?  ቁጥር 15ን ከ1ኛ ቆሮ.16፡5 ጋር ስናስተያይ ሐዋርያው ከመቄዶንያ ሲመለስ በቆሮንቶስ እንደሚያልፍና እንደሚጎበኛቸው ተስፋ እንደሰጣቸው እናነባለን። ይህ ክመቄዶንያ ሲመለስ ብቻ መጕብኘት በፊት ከነበራቸው የተቀየረ ነበር። በፊት የነገራቸው ወደ መቄዶንያ ሲሄድም ከመቄዶንያ ሲመለስም ሁለት ጊዜ እንደሚሆን ገልጾ እንደነበር በዚህ ክፍል እናነባለን። ያ በ1ኛ ቆሮ.16፡5 የጻፈው ፕላኑን እንደቀየረ የሚያስታውቅ ነበር። ይህ የፕላን መቀየር በቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ሐሜትንና ቅሬታን አስነሣ። ይህን ቅራኔ ለማስወገድ ሐዋርያው ይሞክራል። በቁጥር 17 ላይ «እንግዲህ ይህን ሳስብ ያን ጊዜ ቅሌትን አሳየሁን?» ብሉ ክሳቸውን ይጠቅሰዋል።  ዓለማውያን የሰጡትን ቃል አያከብሩም። ዛሬ የተናገሩትን ጥቅም የማይሰጣቸው ከሆነ ነገ ይለውጡታል። ሐዋርያው ግን ሃሳቡን የቀየረው ለጥቅማቸው አንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን ሁለት ጊዜ እንዲጉበኛቸው ስላሰበ እንደሆነ ይናገራል።  ሐዋርያው ዓለማዊ አለመሆኑን በሰበከላቸው ወንጌል ተረድተውታል። በጳውሎስ የተሰበከው ወንጌል በአንድ ጊዜ «አዎንና አይደለም» የሚል ሳይሆን ቃሉና ተስፋው የማይሻር ሆኖ ሁልጊዜ «አዎን» ነው። በቁጥር 18 ላይ የአማርኛው ትርጉም «እግዚአብሔር ግን የታመነ ነው» ይላል። ትክክለኛው ትርጉም ግን «እግዚአብሔር እውነት ነው» ማለቱ ነው። ይህም እንደ መሐላ ነው፡፡  ጥያቄ 14. ቃላችንን ስለመጠበቅ ይህ ክፍል የሚሰጠን ትምህርት ምንድነው? ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖች ቃላቸውን የማይጠብቁት በምን ዓይነት አኳኋን እንዳሆነ ምሳሌ በመስጠት ገለጽ።  እግዚአብሔር በቃሉ ውስጥ ለልጆቹ ብዙ ቃል ኪዳናችን ሰጥቷል። ለእነዚህ ቃል ኪዳኖች የሚያስፈልጉትን ቅድመ ሁኔታዎች ስናሟላ ቃል ኪዳኖቹ ይፈጸማሉ።  ጥያቄ 15. እግዚአብሔር ከሰጠን ቃል ኪዳናች ውስጥ አንዳንዶቹን ግለጽ።  እግዚአብሔር ቃል ኪዳናቱን (ለምሳሌ፡- ካመንን እንዳምንድን፥ ስንደልይ እንደሚሰማን፥ ሁሌ ከእኛ ጋር አብሮ እንደሚሆን) በመፈጸም ረገድ ታማኝ ነው። እኛም የእርሱ ልጆች እንደመሆናችን መጠን ልክ እንደ እርሱ ለሌሎች የምንገባላቸውን ቃል ኪዳኖች መፈጸም አለብን።  ስለ መንፈስ ቅዱስ ማህተምና መያዣ ቁጥር 21 እና 22 ይናገራል። ማህተም ሲል መንፈስ ቅዱስ ሕይወታችንን በመቀየር በተፈጥሮ ተሰጥቶን የነበረው እግዚአብሔርን መምሰል (ዘፍ.3፡16-17) በኃጢአት ግን የተበላሸው አሁን በወንጌል መታደሱን ነው። ይህም መታደስ የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ስለሆነ የመንፈስ ቅዱስ ማህተም ይባላል።  እግዚአብሔር በወንጌል ቃሉ የታመነ ለመሆኑ የመንፈሱን መያዣ ሰጥቶናል፤ (ቁጥር 21 እና 22)፡፡ ይህም ማለት መንፈስ ቅዱስ በሙላት ልንቀበለው ላለን ወንጌል ለሰጠን ለወደፊቱ ተስፋችን መያዣ (ቀብድ) ሆና ተሰጥቶናል ማለት ነው (ሮሜ 8፡9፤ ኤፌ.1:13፤ 4፡30)።  የመጨረሻውን ደህንነታችንን በተመለከተ፥ እንደ እግዚአብሔር ልጆች በቁጥር 21 እና 22 ላይ እግዚአብሔር የሰጠንን አራት ቃል ኪዳኖች እንመለከታለን።  በመጀመሪያ፡- በክርስትና እምነታችን አጽንቶ እንደሚያቆመን ቃል ይገባልናል።  ሁለተኛ፡- እግዚአብሔር በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት ቀብቶናል።  ሦስተኛ፡- መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር እንደሆንን የሚያሳይና የሚያረጋገጥ ማህተም ነው።  አራተኛ:- መንፈስ ቅዱስ በልባችን ውስጥ ነው ያለው። መንፈስ ቅዱስ እኛን ማደስ ብቻ ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ልጆች መንግሥተ ሰማይ እንደምንገባና ክርስቶስን ወደ መምሰል እንደምንደርስ የሚያረጋግጥልን ዋስትናችን ነው።  ጥያቄ 16. የመንፈስ ቅዱስ በሕይወታችን ውስጥ መያዣ ወይም ዋስትና ሆኖ መሰጠት እንዴት እኛን ሊያበረታታን ይችላል?

2ኛ ቆሮ.1:15-22 Read More »

2ኛ ቆሮ.1:12-14

ጥያቄ 8. በቁጥር 13 ላይ «ከምታነቡትና ከምታስተውሉት በቀር ሌላ አንጽፍላችሁና» ሲል ምን ማለቱ ነው?  ቁጥር 12 ላይ በቅንነትና በቀጥተኛነት በመካከላቸው እንደኖረ ሕሊናው ይመሰክርለታል። “በዓለማዊ ጥበብ ሳይሆን በእግዚአብሔር ቅድስናና ቅንነት” አንዳንዶች የእውነት መንገድ ሳይስማማቸው ሲቀር ወደ ማጭበርበርና ወደ ውሸት ያዘነብላሉ። ይህም የዓለም መንገድ ነው። ሐዋርያው ግን በእግዚአብሔር ተማምኖ ሥራውን ሁሉ በቅድስናና በቅንነት ይፈድም ነበር፡፡ ለዚህም የራሱ ሕሊና ምስክሩ ነበር፡፡  ጥያቄ 9. ክርስቲያኖች እንዴት ቅዱስና ቅን ሳይሆኑ ሊኖሩና ሊናገሩ እንደሚችሉ ምሳሌዎች ስጥ። ይህ ችግር በሁሉም ላይ ያለ ነውን?  ሰው ሥራውንና ሃሳቡን ከሌላ ሰው ሊሰውር ይችላል፤ ከራሱ ግን በምንም ዓይነት ሊሰውር አይችልም። ስለዚህ የሰው ሕሊና የእግዚአብሔር ረዳት በመሆን ሌላ ሰውም እንኳ ባያውቅ ሰውን ስለራሱ ሥራ ይከሰዋል። ሐዋርያው ግን በቅድስናና በቅንነት ይኖር ስለነበር እንኳን ሰው ቀርቶ የራሱም ሕሊና ይመሰክርለት ነበር።  በቁጥር 13 እና 14 ላይ “ከምታነቡትና ከምታስተውሉት በቀር ሌላ አንድፍላችሁምና” ይላል። አንዳንዶች በሐዋርያው ላይ የሐሰት ክስ ሰንዝረው ነበር። ይህም ሐዋርያው በዚህ ጊዜ እመጣለሁ ብሉ ባለበት ወቅት ሳይመጣ ስለቀረ “በተናገረው አይረጋም” የሚል ክስ ተሰነዘረበት፤ (ቁጥር 15-17ን ተመልከት)። ደግሞም “በደብዳቤው አንድ መልክ ይዞ ይቀርባል፤ ፊት ለፊት ግን መልኩን ይቀይራል” ብለውም ከሰውት ነበር፤ (10፡10 እና 11)። ስለዚህ ሐዋርያው በዚህ ክፍል ውስጥ ከምታነቡትና ከምታስተውሉት በቀር ሌላ አልድፍላችሁም ይላቸዋል። አንዳንዶች በዓለማዊ ልማድ ስለሚኖሩ የሚናገሩትና የሚያደርጉት ግንኙነት የለውም። በሐዋርያው ዘንድ ግን ይህ ዓይነት መቀላመድ የለም። እኛም ሁላችን የክርስቶስ ተከታዮች የሆንን እርሱ እውነት እንደሆነ በዓለም መንገድ በውሸት ሳይሆን በእውነት መንገድ መመራት አለብን። ለዚህም ሰውን ልናታልል ብንችልም የራሳችንን ሕሊና ግን ልናታልል አንችልምና በውስጣችን የልቦና ክስ የሌለብን ንጹሕ ክርስቲያኖች እንሁን።  ጥያቄ 10. ሀ/ አንዳንድ መሪዎች በሚናገሩትና በሚሠሩት መካከል ልዩነት የሚያሳዩት እንዴት ነው? ለ/ በምስክርነታቸውስ ላይ የሚያስከትለው ጉዳት ምንድነው?  ሰው አሁን በሕሊናው ደንዝዞ በውሽት ቢኖር በእግዚአብሔር ፍርድ ፊት አንድ ቀን ይጋለጣልና በጥንቃቄ መኖር አለበት። “በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቀን” እያለ በዚያን ጊዜ እርስ በርስ የማንተፋፈር ሆነን መገኘት እንዳለብን ያሳስበናል። ሐዋርያው ሕይወቱን በጥንቃቄ ስለመራ በፍርድ ቀን የቆርንቶስ ምእመናን ይኮሩበታል እንጂ አያፍሩበትም። በእነርሱ የማያፍርባቸው ሆነው እንዲገኙ ያሳስባቸዋል።  ጥያቄ 11. ሀ/ የአንተን ሕይወት በተመለከተ ይህን ዓይነት ምስክርነት ልትሰጥ ትችላለህ? ለ/ በዚያን ቀን (በክርስቶስ ቀን) ያለነቀፋ ትሆን ዘንድ ጊዜ ወስደህ ስለፈጸምካቸው የተሳሳቱ ድርጊቶችም ሆነ በልብህ ውስጥ ስላለህ የተሳሳተ አስተሳሰብ ራስህን መርምር።

2ኛ ቆሮ.1:12-14 Read More »

2ኛ ቆሮ.1:1-11

አጠቃላይ መግቢያ  በ 1ኛ ቆሮ.16፡5-9 ላይ ሐዋርያው የጉብኝት ፕላኑን እንደቀየረ ይነግራቸዋል። ከዚህ በፊት ከመቄዶንያ ሲመለስ ሳይሆን ወደ መቄዶንያም ሲሄድ እንደሚጉበኛቸው እንዲሁም ከመቄዶንያ ሲመለስ ደገሞ እንደሚጐበኛቸው ነገሮአቸው ነበር ማለት ነው፤ (2ኛ ቆሮ.1፡15-16)፡፡ ነገር ግን ይህን እንዳሰበው ሊፈድም እንዳልቻለና ከመቄዶንያ ሲመላስ ብቻ እንደሚጎበኛቸው በ1ኛ ቆሮ.16፡5-9 ባለው ክፍል ይነገራቸዋል።  በዚህ ምክንያት የሐዋርያው ተቃዋሚዎች «ጳውሎስ በተናገረው አይረጋም» የሚል ክስ ይሰነዘሩበታል፤ (2ኛ ቆሮ.1:17-19)። እርሱም ይህ እንዳልሆነ ግን ያልጎበኛቸው ዳግመኛ በኃዘን እንዳይጐበኛቸው ለእነርሱ አዝኖ እንደሆነ ይነገራቸዋል፤ (2ኛ ቆሮ.2:1-4)። ሦስተኛ ጉብኝቱን በቶሎ እንደሚፈድም እነሱም ለዚህ ጉብኝቱ ተዘጋጅተው እንዲጠብቁት ያስታውቃቸዋል፤ (2ኛ ቆሮ.12:14፤ 13:1)። ጠቅላላ መልእክቱም በዚህ ዝግጅት ይከፋፈላል።  ክፍል 1:- እመጣለሁ ብሎ ባለበት ጊዜ ያለመምጣቱን ምክንያት ያስረዳል፤ ከምዕራፍ 1-7።  ክፍል 2:- ለቅዱሳን ዕርዳታ መዋጮው ተሰብስቦ እንዲጠብቀው፤ ምዕራፍ 8 እና 9፡  ክፍል 3፡- ሦስተኛ ጉብኝቱ በእርግጥ ስለቀረበ ያመፁበትና እስካሁን ንስሐ ያልገቡትን እንደበፊተኛው ጊዜ ያላቅጣት እንደማይለቃቸው ማስጠንቀቂያ ከምዕራፍ 10-13  ጥያቄ 1. 2ኛ ቆሮንቶስን በሙሉ አንብበህ ከዚህ በላይ የተሰጠውን መግቢያ ከጥቅሶቹ አንብበህ ስለተሰጠው መግቢያ ያለህን አስተያየት በአጭሩ ጻፍ።  ጥያቄ 2. በቁጥር 1 ላይ ቅዱሳን የሚለው እነማንን ነው?  ጥያቄ 3. በቁጥር 5 ላይ «ክርስቶስ ሥቃይ በእኛ ላይ እንደበዛ» ሲል ምን ማለቱ ነው?  ጥያቄ 4. በቁጥር 10 እና 11 ላይ «በብዙ ሰዎች በኩል ስለተሰጠን ስለጸጋ ስጦታ» ሲል ምን ማለቱ ነው?  ቁጥር 1:- ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ሲጽፍ ሐዋርያነቱን ይጠቅሳል፤ ሐዋርያነት ሥልጣኑን የማይቀበሉ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ተነሥተው ነበርና። ጢሞቴዎስ የተባለው ወጣት በመጀመሪጀው የሐዋርያው ጉዞ ጌታን ተቀብሎ የሐዋርያው ተከታይ እንዲሆን በሁለተኛው ጉዞው መረጠው፤ (የሐዋ.16፡1-3)። አካይያ የተባለው አውራጃው ሲሆን ቆሮንቶስ ደግሞ ከተማው ነው። ይህ መልእክት የተጻፈው በቆሮንቶስ ትገኝ ለነበረችው ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በመላው ግሪክ ለነበሩ ክርስቲያናችም ጭምር መነበብ ነበረበት።  ቁጥር 2:- ሐዋርያው ምንም በልቡ ሃዘን ቢሰማው ልጆቹ የሆኑትን ምእመናንን ከማጽናናት አይሰለችም።  ከቁጥር 3-6፡- «የርኅራኄ አባት» እግዚአብሔር በርኅራኄው ሰፊ ስለሆነ የርኅራኄ አባት ተባለ። ልጆቹ ሲሠቃዩ እግዚአብሔር አባታችን ይገደዋል። «የመጽናናትም ሁሉ አምላክ» መጽናናት የሚለው ቃል ከመንፈስ ቅዱስ አገልግሎት ጋር የተያያዘ ነው፤ (ዮሐ. 14፡16)።  «የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት» ክርስቶስ በአምላክነቱ እግዚአብሔር አባቱ ነው፤ ያም ማለት ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ነው። ግን ሰው ሆኖ አማላጃችን ስለሆነ በሰውነቱ አብ አምላኩ ነው፤ (ዮሐ. 20: 17)።  ከቁጥር 4 ጀምሮ ሐዋርያው ስለመከራው ይናገራል። ይህም ስለ ወንጌል ከመከራ በስተቀር ከሰው ሌላ ክብር እንዳላገኘ ያስረዳል። መከራውም የእውነተኛነቱ ማረጋገጫ ማህተም ነበር። በመከራው የእግዚአብሔርን መጽናናት አየ። ይህ ማጽናናት ከመከራ ማዳን ብቻ ሳይሆን በመከራም ውስጥ የመንፈስ ጥንካሬ መስጠት ነው። ክርስቲያን በመከራ ውስጥ መጽናናትን ስለሚቀበል ዞሮ በመከራ ያሉትን ማጽናናት ይችላል።  ጥያቄ 5. ሀ/ በሕይወትህ መከራን በማምጣት እግዚአብሔር በእምነትህ ሲያሳድግህ ያየኸው እንዴት ነው? ለ/ ይህ መከራ ሌሎችን በመከራ ውስጥ ያሉትን እህትና ወንድሞችህን እንድትረዳቸው ያደረገህ እንዴት ነው?  “የክርስቶስ ሥቃይ በእኛ ላይ እንደበዛ” ክርስቲያን በወንጌል ምክንያት መከራ ሲቀበል ከክርስቶስ ጽዋ ተካፋይ ይሆናል። ይህም እንደክርስቶስ እርሱ አዳኝ ይሆናል ማለት አይደለዎ። ግን በክርስቶስ ምክንያት ስለ ጽድቅ መሰደድ ከክርስቶስ ጋር መተባበር ስለሆነ ይህ መልሶ የክርስቶስን መጽናናት በልብ ያመጣል። ክርስቶስ አሁን በክብር እንጂ በሥቃይ አይደለም። ያለፈውን የክርስቶስን መከራ የሚካፈሉ አሁን በመከራቸው የክርስቶስን መጽናናት በመጠኑ እንደቅምሻ ያህል ይቀበላሉ (ፊልጵ. 3:10፤ 1ኛ ጴጥ.4:13፤ ማቴ.20፡23)።  የሐዋርያው ሥቃይና መጽናናት ለቤተ ክርስቲያን በረከት ሆነ። ያም ወንጌልን ስላስተማረና በተቀበለውም መጽናናት አሁንም በቃሉ እኛን በዚህ ዘመን ስለሚያጽናናን ነው። በሐዋርያውና በቆርንቶስ ክርስቲያኖች መካከል በክርስቶስ በመጽናናት መደጋገፍ ሊበዛ እንጂ ክርስቲያን ለሌላ ክርስቲያን የሐዘን ምክንያት መሆን የለበትም! (ቁጥር 6)።  ከቁጥር 8-11:- በእስያ የደረሰበት ሥቃይ ለሕይወቱ እንኳ የሚያሰጋው ነበር፤ ግን በክርስቲያኖች ጸሎትና በክርስቶስ የትንሣኤ ኃይል ምክንያት ከብዙ አደጋ ተበበቀ። ጳውሎስ በእስያ ውስጥ ምን ዓይነት ችግር እንዳጋጠመው በግልጽ ባናውቅም በጣም ጠቃሚ ትምህርት እንዳስተማረው ግን እናውቃለን። በመከራው ውስጥ ጳውሎስ በራሱ ኃይል መተማመን ሳይሆን ለእግዚአብሔርም ሁለንተናውን መስጠትን ተምሯል።  ጥያቄ 6. ሀ/ 2ኛ ቆሮ.12፡9-10 አንብብ። እነዚህ ሁለት እውነታዎች የሚመሳሰሉት እንዴት ነው? ለ/ እግዚአብሔር እንዴት አድርጎ ነው በኃይልህና በጥበብህ ከመታመን ይልቅ በእርሱ መታመንን ያስተማረህ?  ጳውሎስ ከመከራው የተገላገለው በሌሎች ሰዎች ያላሰለሰ ጸሎት እንደነበር ተረድቷል። ይህ ለጳውሎስ የተሰጠ የጸጋ ስጦታ ነው። ጳውሎስ አንድ ፍሪ ያለው አገልገሎት ሊኖረው የሚችለው በጌታ ወንድምና እህቱ የሆኑ ሁሉ በጸሎት ሲያስቡት አንደሆነ ተገንዝቧል። እግዚአብሔር በእኛ ጸሎት አማካኝነት በሌሎች ሰዎች ሕይወት ውስጥ ይሠራል።  ጥያቄ 7. በጸሎትህ ሰዓት ለሌሎች (መጋቢዎች፥ ወንጌላውያን፥ ሽማገሌዎች፥ ወዘተ …) ምን ያህል ትጸልያለህ? ጸሎትህ ለእነዚህ ሰዎች አስፈላጊ እንደሆነ መገንዘብ ይገባሃል። አሁን ትንሽ ጊዜ ወስደህ የቤተ ክርስቲያንህን መሪዎች በጸሎት አማካኝነት በእግዚአብሔር ፊት አስባቸው፡፡

2ኛ ቆሮ.1:1-11 Read More »

1ኛ ቆሮ.16፡5-24

ጥያቄ 16. በዚህ ክፍል ላይ ስንት ነጥቦችን እንደሚጠቅስ በአጭሩ ዝርዝር።  የደብዳቤው መደደሚያ ላይ በሆነው በዚህ ክፍል ሐዋርያው የተለያዩ ነጥቦችን ይጠቅሳል፤ በአጭሩ እንዘርዝራቸው።  1ኛ/ ከቁጥር 5-6፡- «በጉዞዬ እንድትረዱኝ» ሲል ገንዘብ መጠየቁ እንዳልነበረ ከ9፡15 እንረዳለን። ምናልባት አንዳንድ ለጉዞው የሚያስፈልገው ስንቅና ሸኚዎች የመሳሰሉ ነገሮች ይሆናሉ።  2ኛ/ ከቁጥር 7-9፡- በኤፌሶን ለአገልገሎት አንደሚሰነብት ይነግራቸዋል። «ሥራ የሞላበት ትልቅ በር ተከፍቶልኛልና» እግዚአብሔር የአገልገሉት በር ሲከፍት እድልን መጠቀም እንደሚያስፈልግ ከሐዋርያው እንማራለን። ይህም በር ብዙ የተቃውሞ ግፊት የበዛበት እንደሆነ ይናገራል። የአገልገሎት በር መከፈት ማለት ተቃውዋ ጠፋ ማለትም እንዳልሆነ እንገንዘብ።  ጥያቄ 17. በአሁኑ ጊዜ የአገልግሎት በር ለቤተ ክርስቲያንህ ክፍት ነው ወይስ ዝግ ነው? እንደት ነው ይህንን የምታውቀው? በሚመጡት አጋጣሚዎችስ ይጠቀሙባቸዋል? ተቃውሞስ አለ? ካለ ተቃውሞው ከማነው?  3ኛ / ከቁጥር 10-11:- ጢሞቴዎስን በአክብሮት እንዲቀበሉት እንጂ እንዳይንቁት ያስጠነቅቃል። ምናልባት ጢሞቴዎስ አይን አፋር ሳይሆን አይቀርም፤ 1ኛ ጢሞ.4:11-12፤ 2ኛ ጢሞ. 1:7። ደግሞም የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች በአገልጋዮች መካከል ስለሚመርጡ ትዕቢተኞች እንደሆኑ ሐዋርያው ስላወቀ በአክብሮት እንዲቀበሉት ያስጠነቅቃቸዋል።  4ኛ/ ቁጥር 12፡- አጵሎስ አሁን ሊጉበኛቸው እንዳማይሄድ ያስታውቃቸዋል፡፡  5ኛ/ ቁጥር 13:- በእምነታቸው የበረቱ እንዲሆኑ ያበረታታቸዋል። ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ሰዎች አምስት ዋና ዋና ሊጠብቋቸው የሚገቡ ትእዛዞች ይሰጣቸዋል።  1. ንቁ፡- ራሳቸውን ከኃጢአትና ከትዕቢት መጠበቅ ነበረባቸው። ራሳቸውን ከሐሰተኛ ትምህርት መጠበቅ ነበረባቸው። ሰይጣን በሚያገኘው አጋጣሚ ወይም ባለመስማማታቸው ተጠቅሞ ሊያጠፋቸው እንደተዘጋጀ መገንዘብ ነበረባቸው።  2. በሃይማኖት ቁሙ፡- ሃይማናታችንን ጠብቀን፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሞቶ መቀበርና ትንሣኤ ላይ መመሥረታችንን ማረጋገጥ ይኖርብናል። ለእምነታችን ከዚህ ሌላ ምንም ዓይነት መሠረት ሊኖረው አይገባም። በመከራ ውስጥ ቢሆንም በኢየሱስ ላይ ያለንን እምነት ለመጠበቅ ቁርጥ ውሣኔ መውሰድ ይገባናል።  3. ጎልምሱ:- እውነቱን ከሚቃወሙት ከብዙዎቹ ፊት ለመቆም ጎበዞች መሆን አለብን። ሰዎች በሚያላግጡብንና በሚያሳድዱን ጊዜ በግልጽ እምነታችንን መግለጽ ጉብዝናን ይጠይቃል። መታወቅ ለሚፈልጉ ሰዎች ክርስትና ሃይማኖት ሊሆን አይችልም።  4. ጠንክሩ:- ልክ እንደ ሁለተኛውና ሦስተኛው ትእዛዝ ይህም ትእዛዝ በእምነታችን ጠንካሮች እንድንሆን ይገፋፋናል። በተጨማሪም ይህ ማለት ኃይልህንና ሁለንተናህን በእግዚአብሔር ሥራ አውል ማለት ነው። አስተውል! ይህ ኃይል የእኛ ሳይሆን እግዚአብሔር የሚሰጠን ኃይል ነው።  5. በእናንተ ዘንድ ሁሉ በፍቅር ይሁን፡- የእግዚአብሔር ትእዛዞች በሙሉ ፍጻሜ የሚያገኙት በፍቅር ነው። ፍቅር ከምንሠራው ሥራና ድንቅ ከሆኑት ስጦታዎች ሁሉ የበለጠ ጠቃሚ ነገር ነው። ለምስክርነታችን ኃይል የሚሰጠው ፍቅር ነው።  ጥያቄ 18. እነዚህን አምስት ትእዛዞች እየጠበቅህ ያለኸው እንዴት ነው? በሕይወትህስ ውስጥ የሚታዩት እንዴት ነው?  6ኛ/ ከቁጥር 14-18፡- ስለ እስጢፋኖስ ቤተሰብ እንዴት ለወንጌል ሥራ የነቁ እንደሆኑ ይናገራል፡፡  7ኛ/ ቁጥር 19 ላይ፡- “በቤታቸውም ካለች ቤተ ክርስቲያን” በማለት ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ሳትሆን የምእመናን ክምችት ወይም ጉባኤ መሆንዋን ይገልጻል።  8ኛ/ ቁጥር 21-24:- ስንብትና ቡራኬ 

1ኛ ቆሮ.16፡5-24 Read More »

1ኛ ቆሮ. 16፡1-4

ጥያቄ 12. በቁጥር 1 ላይ ለቅዱሳንዎ ገዝብን ስለ ማዋጣት» ሲል ምን ማለቱ ነው?  ጥያቄ 13. በቁጥር 2 ላይ የገንዘብ ማጠራቀሚያው ቀን ለምን ከሳምንቱ የመጃመሪያው ቀን ይሁን አለ?  «ለቅዱሳን ገንዘብን ስለማዋጣት» ስለዚህም ጉዳይ ሳይጠይቁት አይቀሩም። ይህ በኢየሩሳሌም ለነበሩት ክርስቲያኖች ገንዘብ አዋጥቶ መላክ ጳውሎስ ሥራዬ ብሎ የሚያካሄደው አገልግሉት ነበር። ለምሳሌ የሚከተሉትን የመድሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ብንመለከት ይህንን እንገነዘባለን። የሐዋ /ሥራ 24:17፤ ሮሜ 15፡25-28፤ 2ኛ ቆሮ.8፡16-21 ተመልከት።  በኢየሩሳሌም የነበሩ ክርስቲያኖች በችግር ላይ ነበሩ። ለምን ችግር ላይ ወደቁ የሚል ጥያቄ ተነሥቶ አንዳንድ ግምቶች ተሠንዝረዋል። ከእነዚህም አንዱ ያላቸውን እርሻም ሆነ ሌላ ነገር ያለ ጥሩ ፕላን ይሸጡ ስለነበር (የሐዋ.4:32-37) ቆይቶ ይህ ድህነት አስከተለባቸው የሚል ነው። በእርግጥ የችግራቸው መነሻ ምን እንደሆነ አይታወቅም። ሌሎች ክርስቲያናች ግን እንዲረጹ በሐዋርያው ታዘዋል።  የገንዘቡ አሰባሰብ ዘዴ እንደሚከተለው መሆን ነበረበት። ሐዋርያው እዚያ ከመድረሱ በፊት መዋጮው ተሰብስቦ ማለቅ ነበረበት። እያንዳንዱ አማኝ እግዚአብሔር እንዳስቻለው እሁድ እሁድ ካለው እየቆረሰ ማጠራቀም ነበረበት። ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን ማለት እሁድ ማለት ነው። እሁድ ክርስቲያኖች ለጸሎት የሚሰበሰቡበት ቀን ሆነ፤ (ዮሐ.19፡21፤ የሐዋ.20፡7፤ ራእይ 1:10)። ይህ ቀን ጌታ ከሞት የተነሣበት ቀን ስላበር የክርስቲያኖች ሰንበት ሆነ።  በአማርኛው ትርጉም ላይ «በቤቱ» የሚል ቃል በቁጥር 2 ላይ ገብቷል። በግሪኩ ላይ ግን ይህ የለም። እያንዳንዱ ክርስቲያን እግዚአብሔር እንዳበለጸገው ያስቀምጥ ይላል እንጂ የት ማስቀመጥ እንዳለበት አልተናገረም። ሆኖም እሁድ ቀን ክርስቲያኖች በአንድነት ለጸሎት የሚሰበሰቡበት ቀን ስለነበርና መዋጮውም በዚሁ ቀን ይሰብሰብ ስላል በቤተ ክርስቲያን ይሰብሰብ ማለቱ ነው ብለን እንገምታለን፡፡ ይህ ከብሉይ ኪዳን ጋር ይስማማል። በብሉይ ኪዳን መዋጥ መጠራቀም የነበረበት በየግል ቤት ሳይሆን በቤተ መቅደስ ወይም አንድ የሕዝብ ማጠራቀሚያ በሆነ ቦታ ነበር።  እግዚአብሔር እንዳስቻለው ይላል እንጂ እያንዳንዱ ክርስቲያን ስንት ማዋጣት እንደነበረበት ባይናገርም በብሉይ ኪዳን እነአብርሃም አሥራት ይሰጡ እንደነበር መዘንጋት የለበትም። እንዲሁዎ ጌታ በማቴ.23፡23 ላይ አሥራትን ደግፎ ተናግሮአል። ስለዚህ እኛም ለክርስቲያኖች እግዚአብሔር እንዳበለጸገን እንስጥ፤ ያም አሥራትን። በጥንቃቄ አሥራት መስጠት በስሜት ተገፋፍቶ በድንገተኛ ሰጥቶ ከመጸጸትና እንዲሁም በቂ ባለመስጠት የእግዚአብሔርን ሥራ ከመበደል ይጠብቀናል።  ጥያቄ 14. ከምታገኘው ነገር 10% ለእግዚአብሔር ትሰጣለህ? ሌሎች ቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ያሉ ሰዎች 10% የሚሰጡ ይመስልሃል? ብዙ ሰዎች የቤተ ክርስቲያን መሪዎችን ጨምሮ አሥራት የማይሰጡት ለምን ይመስልሃል?  ይህ የተዋጣው ገንዘብ በጥንቃቁ የተባለበት ቦታ እንዲደርስና ሐሜት እንዳይነሣ ራሳቸው የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ከራሳቸው ሰዎች መርጠው ስጦታውን እንዲልኩ ያዛል እንጂ፥ ሐዋርያው «እኔ አደርስላችኋለሁ» ብሎ እንዳልወሰደ ግልድ ነው። ገንዘብ ንጽሕናንና ጥንቃቄን ይጠይቃልና አጉል «እንተማመን» በሚል ሞኝነት ሐሜትና ጥርጣሬ አንፍጠር፤ (ቁጥር 3)።  ጥያቄ 15. ይህ ክፍል የቤተ ክርስቲያንን ገንዘብ በምን ዓይነት መንገድ ማስተደደር እንዳለብን ነው የሚያስተምረው?

1ኛ ቆሮ. 16፡1-4 Read More »

1ኛ ቆሮ.15:35-58)

ጥያቄ 6. በቁጥር 35 ላይ ሁለት ጥያቄዎች ተጠይቀው ሐዋርያው መልስ ሰጥቷል፤ ጥያቄዎቹን ከመልሶቻቸው ጋር አዛምድ።  ጥያቄ 7. በቁጥር 44 ላይ መንፈሳዊ አካል ሲል ምን ማለቱ ነው?  ጥያቄ 8. ሐዋርያው የነገራቸው ምሥጢር ምንድነው? (ቁጥር 51 እና 52)  ጥያቄ 9. በቁጥር 55 ላይ ሐዋርያው የጠቀሰው ጥቅስ የተወሰደው ከየት ነው?  ቁጥር 35-50፡- በቁጥር 35 ላይ ሁለት ጥያቄዎች ተነሥተዋል። ከዚያ ቀጥሎ ያለው ጽሑፍ በሙሉ እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ ነው። የመጀመሪያው ጥያቄ «ሙታን እንዴት ይነሣሉ?» የሚል ሲሆን ሁለተኛው ጥያቄ ደግም «በምንስ ዓይነት አካል ይመጣሉ?» እነዚህን ጥያቄዎች በሰፊው እንደሚከተለው ይመልሳል።  አስቀድሞ ግን ቢያስተውሉ ኖሮ ይህን ነገር ከተፈጥሮ ሊማሩ ይችሉ እንደነበር «ሞኝ» ብሉ አላማስተዋላቸውን ይገሥጻል፡፡ የሚከተሉትን የተፈጥሮ ሕጉች ለትንሣኤ ምሳሌ አድርጎ ያቀርባቸዋል።  1ኛ/ ስንዴ ዘሩ ተዘርቶ ሌላ ስንዴ ከነሰበዙ አምሮና ደምቆ፥ ከተዘራው ቅንጣት እጅግ ደምቆ ይበቅላል። እግዚአብሔር ይህን በተፈጥሮ ካዘጋጇ ትንሣኤንም እንዲሁ እንደሚያሳምረው መረዳት አለብን፤ (ቁጥር 36-38)። ይህንን ከቁጥር 42-44 ጋር አስተያይ፡፡ ይህ ምሳሌ በምድር ላይ ያለው አካላችንና መንፈሳዊ አካላችን ተመሳሳይነት እንዳላቸው ያስተምረናል። ተዘርቶ እንደሚበቅለው ስንዴ የእኛም አካል አሁን ካለው አካላችን ትንሽ ለየት የሚል ይሆናል።  2ኛ/ በሥጋም ደረጃ የተለያየ ሥጋ አለ። የሰውና የእንስሳ ሥጋ እንደ መልኩ በፈጣሪው ተለያይቷል። በምድር ላይ እንዲህ ያለ የተለያየ ሥጋ እንደለ ሁሉ ሰማያዊ ሥጋም ይናራል፤ (ቁጥር 39 እና 40)። ምንም እንከን ከሙታን የተነሣው አካላችን ከምድራዊው አካላችን ጋር መመሳሰል ቢኖረውም፥ ከሙታን የተነሣው ሰውነታችን የበለጠ ክብር አለው። ይህ አርጅቶ የሚሞተውና የሚበሰብሰው ሥጋዊ አካላችን ከሙታን ከተነሣን በኋላ ለሞትና ለመበስበስ የተጋለጠ አይሆንም። በሕይወታችን ውስጥ ያለው የማይከብረው የኃጢአት ተፈጥሮ ሙሉ በሙሉ ወደ ቅድስና ይለወጣል። በዚህ ሂደት ወስጥ መንፈሳዊ የሆነ አካል ይሰጠናል፡፡  «ፍጥረታዊ አካል ካለ መንፈሳዊ አካል ደግሞ አለ፤» (ቁጥር 44)። አሁን ያለን ሥጋ ፍጥረታዊ ነው። ይህ ፍጥረታዊው ግን በትንሣኤ መንፈሳዊ ሆኖ ይነሣል፡፡ ፍጥረታዊውን አካላችንን ከመጀመሪያው አባታችን ከአዳም ወረስን፤ በዚህም እርሱን መሰልን። እንዲሁ ዳግሞ አንድ ቀን የሕይወት ሰጭውን የክርስቶስን አካል መስለን የምንለወጥበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ክርስቶስም እንዲህ እንደ መጃመሪያው አዳም የርሱ የሆኑትን የራሱን መልክ እንዲመስሉ ስለሚለውጣቸው ሁለተኛው አዳም ተባለ፤ (ቁጥር 45-49)። ይህ እንዲህ ሊሆን ግድ ነው፤ ምክንያቱም በዚህ ሥጋ አካላችን የትንሣኤን ሕይወት መካፈል አንችልምና የግድ መለወጥ አለብን።  እዚህ ላይ መረዳት ያለብን የትንሣኤውን አካል «መንፈሳዊ» ሲል ረቂቅ የሆነ አካል ማለቱ ሳይሆን የክብሩን ታላቅነት መግለጡ ነው፡፡ ረቂቅ ማለቱ እንዳልሆነ የምናውቀው የክርስቶስ የትንሣኤ አካል ረቂቅ ባለመሆኑ ነው፤ (ዮሐ.20፡27)። እኛም በትንሣኤ እርሱን ስለምንመስል እርሱን መምሰል መንፈሳዊ አካል መልበስ ነው ማለት ነው።  ጥያቄ 10. ከመሞቱ በፊት የነበረው የኢየሱስ ክርስቶስ አካልና ከምቶ ከተነሣ በኋላ የነበረው አካሉ የሚመሳሰለው አንዴት ነው? የሚለያየውስ?  ከቁጥር 51-57:- ትንሣኤያችን መቼ ነው? ለዚህ ጥያቄ መልሱ ክርስቶስ ሲመለስ ነው። ጌታ ሲመጣ በሕይወት ያለነው ከመቅድበት እንለወጣለን፤ የሞቱትም አማኞች የትንሣኤ አካል ለብሰው ይነሣሉ። ይህ ሲሆን ሞትና ኃጢአት በክርስቶስ ፈድመው ድል ይሆናሉ። ጳውሎስ ይህን «ምስጢር» ብሎ ይጠራዋል። በመድሐፍ ቅዱስ «ምስጢር» የሚባለው አንድ የተደበቀና ለጥቂት ሰዎች የሚታወቅ ነገር ሳይሆን፥ ከዚህ ቀደም እግዚአብሔር በቃሉ ውስጥ ያልገለጸው ነገር ግን አሁን በደቀ መዛሙርቶቹ አማካኝነት የገለጸው እውነት ማለት ነው። ይህ አዲስ እውነት ያለመለኮታዊ መገለጥ ሊታወቅ የማይችል ነገር ነው። አዲስ ኪዳን በመፈጸሙ እንደዚህ ዓይነት ምስጢራት ዛሬ ለእኛ አይገለጹልንም። ሐዋርያው ከትንቢተ ሆሴዕ 13:14 በመጥቀስ ይደመድማል። ይህ የትንሣኤ ተስፋ ስላለን ተስፋ ሳንቆርጥ በብርታት ጌታን እናገለግላለን፤ (ቁጥር 58)።  ጥያቄ 11. የትንሣኤው እውነተኛነት እንዴት ነው ራሳችንን ሙሉ በሙሉ ለጌታ ሥራ እንድንሰጥ ሊያደርገን የሚችለው?

1ኛ ቆሮ.15:35-58) Read More »

1ኛ ቆሮ 15፡20-34

ጥያቄ 1. “ክርስቶስ ላንቀላፉት በኩራት ሆና ተነሥቷል” ማለት ምን ማለት ነው? (ቁጥር 29)  ጥያቄ 2. ክርስቶስ ሁሉ ከተገዛለት በኋላ እርሱ ራሱ ለእግዚአብሔር በመገዛት መንግሥቱን ያስረክባል ሲል ምን ማለቱ ነው? (ቁጥር 25-28)  ጥያቀ 3. ስለሙታን መጠመቅ ማለት ምን ማለት ነው? (ቁጥር 29)  ቁጥር 20፡- የክርስቶስ ትንሣኤ በእርሱ ለሚያምኑት ትንሣኤ ዋስ (መተማመኛ) ነው። ክርስቶስ ስለተነሣ በእርሱ የሚያምኑትዎ በእርግጥ ይነሣሉ።  ስለዚህ የክርስቶስ ትንሣኤ “በኩር” ይባላል። በኩር የሚለው ቃል የተወሰደው ከብሉይ ኪዳን ከዘሌዋውያን 23:10 ላይ ነው፡፡ መከሩ ለመጀመሪያ ሲደርስ የተወሰነ ነዶ ወደ ቤተ መቅደስ ለምስጋና መስዋዕት ይቀርብ ነበር። ይህ የበኩር መሥዋዕት የቀረው መከር እንደሚሰበሰብ ዋስትና (መተማመኛ) ነበር። እንዲሁም የክርስቶስ ትንሣኤ በእርሱ ለሚያምኑት ትንሣኤ መተማመኛ ነው። እርሱ ከሙታን ስለተነሣ በእርሱ የሚያምኑትም እንደሚነሁ በፍጹም የተረጋገጠ ነገር ነው።  ከክርስቶስ ትንሣኤ በፊት ከመቃብር የተነሱ ብዙ ሲሆኑ (ለምሳሌ አልዓዛር ) ለምን ክርስቶስ የትንሣኤ በኩር (የመጀመሪያ) ተባለ? ከእርሱ በፊት የተነሱት ተመልሰው ሞተዋል። ክርስቶስ ግን ዳግመኛ ላለመሞት ተነሥቷል። የእኛም የአማኞች ትንሣኤ እንዲሁ ዳግመኛ ላለመሞት ነው። ስለዚህ በዚህ ዐይነት ትንሣኤ እስካሁን የተነሣ ክርስቶስ ብቻ ስለሆነ የትንሣኤ በኩር ተባለ።  ከቁጥር 21-23:- በዚህ ክፍል ሁለት አዳሞች እንዳሉ ይነገረናል። በመጀመሪያው አዳም አማካይነት ሞት ለሰው ሁሉ እንደመጣ ሁሉ ÷ አሁንም በሁለተኛው አዳም (በክርስቶስ ) ትንሣኤ ለአማኞች መጣ፡፡ ከዚህ ጋር ሮሜ 5፡12-14ን አስተያይ። ክርስቶስ የተነሣው በመጀመሪያው የፋሲካ ቀን ጠዋት ላይ ነበር። አሁን ለዳግም ምፅዓቱ ግን ባለፉት ዘመናት ውስጥ በእርሱ ያምኑ የነበሩትን በሙሉ ነው ከሙታን የሚያስነሣው።  ከቁጥር 24-28:- ሁሉ ከክርስቶስ እግር ሥር ከተገዛ በኋላ ክርስቶስ ራሱ ሥልጣንን ለእግዚአብሔር መልሶ እርሱ ራሱም ሁሉን ላስገዛለት ይገዛል ይላል። በዚህ ጥቅስ ላይ ተመርኩዘው ሐሰተኛ አስተማሪዎች የክርስቶስን አምላክነት ይክዳሉ። ይህ ክፍል ክርስቶስን በአምላክነቱ ሳይሆን የሚመለከተው በሰውነቱ ነው። አዎን! ክርስቶስ በሰውነቱ ለእግዚአብሔር ሲጸልይ እግዚአብሔርን ሲያመልክ እንደነበር በወንጌል ተጽፏል። ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ መልሶ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንዳሆነ እርሱ ራሱ አምላክ እንደሆነ ያስተምራል።  እንግዲህ ክርስቶስ አሁን በሰውነቱ በዓለም ላይ ነግሶ ስላለ ወደፊት ሥልጣን ሁሉ በእግሩ ሥር እንደሚሆን መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምራል። ሥልጣን ሁሉ ለክርስቶስ ቢሰጥም እስካሁን ድረስ ሁሉን ነገር በራሱ ቁጥጥር ሥር አላደረገም። ሁሉንም በቁጥጥሩ ሥር የሚያደርገው በመጨረሻው ዘመን ነው። በዚህ ጊዜ ሞትን ብቻ ሳይሆን ሰይጣንንና በጌታ ኢየሱስ የማያምኑትን መንግሥታት በሙሉ ያወድማል። ሁሉም ተንበርክከው የእግዚአብሔርን ልጅ ያከብራሉ፤ (ፊል.2:10-11)። ሁሉ ነገር በእግሩ ሥር የሚሆነው የመጨረሻው ጠላት ያም ሞት ከወደመ በኋላ ብቻ ነው። እስከዚያ ድረስ ክርስቶስ በሰውነቱ የዓለም ገዥ ነው። በዚህ ጥቅስ መሠረት ግን ሁሉን በእግሩ ሥር ከገዛ በኋላ ሥልጣንን ከሰውነቱ አሳልፎ ለእግዚአብሔር ይሰጣል። በአምላክነቱ ግን እርሱዎ ዘለዓለማዊ ወልድ ስለሆነ ይህን ሥልጣን ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ይካፈላል። በዚህ ክፍል ላይ በሥላሴዎች መካከል ያለውን ዘላለማዊ ግንኙነት እንመለከታለን። ምንም እንኳን አብ፥ ወልድና መንፈስ ቅዱስ እያንዳንዱ እግዚአብሐርም ቢሆኑ፥ በሰብዓዊ ባሕርያቸውም እኩል ቢሆኑም፥ የግንኙነት ቅደም ተከተል አላቸው። እግዚአብሔር አብ ዋነኛውና የመጨረሻ ባለሥልጣን ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ እንደ ልጅ ሁሉ የአባቱን ፈቃድ ይፈጽማል። ስለዚህም የአባቱን ፈቃድ በመፈጸም የሰውን ልጅ ፈጠረ! ከኃጢአትም አዳናቸው። በተመሳሳይ ሁኔታም ሁሉን ነገር በራሱ ቁጥጥር ሥር አደረገ። አሁንም ቢሆን በእግዚአብሔር ሥልጣን ሥር ነው። መንፈስ ቅዱስ ደግሞ የአብና የወልድ ወኪል ሆኖ ፈቃዳቸውን የሚፈጽም ነው። ስለዚህ የመጨረሻው ፕሮግራም ሁሉ ነገር በክርስቶስ አማካይነት ለሥላሴ ተጠቃልሉ መገዛት ነው።  ጥያቄ 4. ከሞት በስተቀር ሌሎች የክርስቶስ ጠላቶች እነማን ናቸው? መቼስ ያሸንፋቸዋል?  ቁጥር 29:- በቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ለሙታን የጥምቀት ሥነ ሥርዓት ይካሄድ እንደነበር ከዚህ እንረዳለን። ምናልባት አምነው ሳይጠምቁ ለሞቱት ዘመዶቻቸው በእርሱ ምትክ ይጠምቁላቸው ነበር። ሐዋርያው ይህንን ሥርዓት አልደገፈውም አልተቃወመውም። ግን የሙታንን ትንሣኤ የሚክዱ ከሆነ «ታዲያ ለምን ለሙታን ትጠመቃላችሁ?» በማለት ራሳቸው እንኳ ለትንሣኤ በዚህ ሥርዓታቸው ምስክሮች እንደሆኑ ያስረዳቸዋል።  ከቁጥር 30-34:- ሙታን የማይነሡ ከሆነ ሐዋርያውም ለወንጌል ሥራ ብሉ ራሱን በየጊዜው ለሞት አሳልፎ መስጠቱ ለምንድነው? እንግዲህ ሙታን የማይነሡ ከሆነ ሰው ከዚህ ዓለም የተሻለ ደስታ ስለማያገኘ «ነገ እንሞታለንና እንብላ እንጠጣ» በሚል ፍልስፍና መመራት አለበት። ግን ክርስቶስ ከመቃብር ስለተነሣ የእኛም የአማኞች ትንሣኤ ተረጋግጧል። ስለዚህ በዚህ ዓለም ለክርስቶስ ክብር ሕይወታችንን ብንሠዋ በትንሣኤ ዋጋችንን አናገኛለንና በተስፋ አንሮጣለን።  ጥያቄ 5. ሀ/ አንዳንድ ሰዎች ወይም አማኞች በሥራቸው “ነገ እንሞታለንና እንብላ እንጠጣ” የሚለውን ፍልስፍና መደገፋቸውን እንዴት ያሳያሉ? ለ/ በክርስቲያን ትንሣኤ ቢያምኑ ሥራቸውን እንዴት ይለወጡ ነበር?

1ኛ ቆሮ 15፡20-34 Read More »