የመስጠት ጸጋ፣ ክፍል 1 (ቆሮንቶስ 8፡1-24)
ከጳውሉስ ሦስተኛ የሚሲዮናዊነት ጉዞ አበይት አገልግሎቶች አንዱ በይሁዳ ለሚኖሩ ድሀ ክርስቲያኖች ልዩ «የርዳታ ስጦታ» ማድረግ ነበር። ጳውሎስ ከዚህ በፊት አንድ ጊዜ የዚህ ዓይነት አገልግሎት ያበረከተ ሲሆን (የሐዋ. 11፡27-30)፥ አሁንም ተመሳሳይ ግልጋሎት ለመስጠት ደስተኛ ነበር። የተዘነጋውንና «ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው» (የሐዋ. 20፡35) የሚለውን የጌታችን ብፅዕና ያስታወሰው ጳውሎስ እንደ ነበር መረዳት አስፈላጊ ነው። ይሁንና ድሆችን በገንዘብ ከመርዳትም በተጨማሪ በጳውሎስ አእምሮው ውስጥ የሚመላለሱ ሌሎችም በረከቶች ነበሩ። ከባሕር ማዶ ለሚገኙ የአይሁድ ማኅበራት የአሕዛብ አብያተ-ክርስቲያናት የሚያደርጉትን እርዳታ በማስታወስ፥ ይህ የቤተ ክርስቲያን አንድነት በበለጠ እንዲጠናከር ይፈልግ ነበር። ጳውሎስ አሕዛብ የአይሁድ «ባለ ዕዳዎች» እንደ ሆኑ አድርጎ ይመለከታል (ሮሜ 15፡25-28)፤ ልዩ የርዳታ አሰባሰቡም ያንኑ ዕዳ ለመክፈል አንድኛው መንገድ ነበር። እንዲሁም ይህ ስጦታ ለአይሁድ አማኞች (አሁንም አንዳንዶቹ ለሕጉ ይቀኑ ነበር) ጳውሎስ እንደሚወራበት የአይሁዶች ወይም የሙሴ ጠላት እንዳልነበር የሚያረጋግጥ ማስረጃ ነበር (የሐዋ. 20 ከቁ 17 ጀምሮ)። ጳውሎስ በአገልግሎቱ መጀመሪያ አካባቢ ድሆችን ለማሰብ ተስፋ የሰጠ ሲሆን (ገላ 2፡6-10)፥ ያንኑ የተስፋ ቃል ለመጠበቅ በትጋት ይሠራ ነበር፤ ሆኖም ግን እግረ መንገዱንም የአይሁዶችን የቅናት መንፈስ ለመስበር በማሰብ ከአሕዛቦች የሚደረግላቸው እርዳታ እንዲጠናከር ያበረታታ ነበር። የሚያሳዝነው፥ የቆሮንቶስ ሰዎች የበኩላቸውን ድርሻ እየተወጡ አልነበረም። እንደ ብዙዎቹ ሰዎች፥ የተስፋ ቃሎችን ቢሰጡም፥ ዳሩ ግን አልፈጸሙም ነበር። እንዲያውም፥ አንድ ዓመቱ በሙሉ በከንቱ ባክኗል (2ኛ ቆሮ.8፡10)። ለዚህ ምክንያቱ ምን ነበር? የቤተ ክርስቲያኗ በዝቅተኛ መንፈሳዊ ደረጃ ላይ መገኘቷ ነበር። ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ እስካልሆነች፥ በልግስና ልትሰጥ አትችልም። ሌላው ምክንያት ደግሞ የሚችሉትን ያህል ገንዘብ ከቤተ ክርስቲያን ሳይዘርፉ ያልቀሩት የአይሁድ ሃይማኖት አስፋፊዎች ወረራ ነበር (11፡7-12፥ 20፤ 12፡14)። ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ለዚህ የልግስና ስጦታ ተካፋይ ማድረጉ ቀላል እንደማይሆን ስለ ተረዳ፥ ልመናውን ወደ ከፍተኛ መንፈሳዊ ደረጃ ያሳድገዋል፡- መስጠት የጸጋ ተግባር እንደ ሆነ ያስተምራቸዋል። ጳውሎስ ስጦታውን ለማመልከት በዘጠኝ የተለያዩ ቃላት ቢጠቀምም ዳሩ ግን ከሁሉም በላይ የተገለገለበት «ጸጋ» በሚባለው ቃል ነበር። መስጠት በመሠረቱ ሌሉችን የሚረዳ አገልግሉትና ኅብረትን የሚያሳይ (8፡4) ቢሆንም፥ ዳሩ ግን የመመንጫው ምክንያት በልብ ውስጥ ያለው የእግዚአብሔር ጸጋ ሊሆን ይገባል። ጳውሎስ ይህ የርዳታ አሰባሰብ የአሕዛቦች ዕዳ መቅረፊያና (ሮሜ 15፡27) የክርስቲያናዊ ሕይወታቸው ፍሬ (ሮሜ 15፡27) ፍሬ እንደ ሆነ ቢያውቅም በሌላ በኩል ደግሞ ከዚህም የላቀ ምክንያት እንደ ነበረው ተረድቶ ነበር፤ ከሁሉም በላይ የእግዚአብሔር ጸጋ በሰው ልብ ውስጥ የመሥራቱ ውጤት መሆኑን ያምንበት ነበር። ስለዚህ ክርስቲያኖች ከልብ መስጠት ከመቀበል ይልቅ የተባረከ መሆኑን አምነው፥ ወደ መስጠት ጸጋ በሚገቡበት ጊዜ አስደናቂ ነገር ይሆናል። ጥያቄው ግን «በጸጋ መስጠትን» እየተለማመድን መሆኑን እንዴት ልናውቅ እንችላለን? የሚለው ነው። ጳውሎስ ስጦታችን በጸጋ የተነቃቃ ለመሆኑ ማስረጃ የሚሆኑ ምልክቶች እንዳሉ አመልክቷል። በሁኔታዎች ሳንገደብ ስንሰጥ (2ኛ ቆሮ.8፡1-2) ጳውሎስ በምሳሌነት የጠቀሳቸው የመቄዶንያ አብያተ ክርስትያናት፥ የራሳቸው የሆኑ ከፍተኛ ችግሮች ቢኖሩባቸውም፥ ዳሩ ግን በልግስና ለመስጠት ወደ ኋላ አላሉም ነበር። «በብዙ መከራ ተፈትነው» (ቁ 2) ነበር እንጂ፥ እንዲሁ በ«መከራ» ውስጥ ብቻ ያለፉ አልነበሩም። በከፍተኛ ድህነት ማለትም «በመናጢነት» ደረጃ ላይ ነበሩ። በዚህ ሥፍራ የተጠቀሰው ቃል ምንም ነገር የሌለውንና ለወደፊትም ምንም ነገር የማግኘት ተስፋው የመነመነን ለማኝ የሚገልጽ ነው። ይህ አስቸጋሪ ሁኔታቸው የመነጨው ምናልባትም ክርስቲያን በመሆናቸው የተነሣ፥ ከሥራቸው በመፈናቀላቸው ወይም ከጣዖት አምልኮ ጋር ለመተባበር ባለመፈለጋቸውና ከንግድ ማኅበራት በመገለላቸው ምክንያት ሊሆን ይችላል። ይሁንና የነበሩባቸው ሁኔታዎች ከመስጠት አላቀቡዋቸውም ነበር። እንዲያም፥ በደስታና በልግስና ሰጡ። ማንኛውም ኮምፒውተር ይህንን የሚከተለውን አስደናቂ ስሌት ሊገነዘብ አይችልም፡- ትልቅ መከራና ጥልቅ ድህነት ሲደመር ጸጋ ለ ብዙ ደስታና ብዙ ልግስና! ይህም በጳውሎስ አገልግሎት ውስጥ የነበረውን የተቃራኒ ነገሮች ዝርዝር ያስታውሰናል፡- «ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለጠጎች እናደርጋለን። (6፡10)። በተጨማሪም የመገናኛው ድንኳን (ዘጸ. 35፡5-6) እና ቤተ መቅደሱ (1ኛ ዜና 29፡6-9) በተሠሩ ጊዜ የተሰጡትን የልግስና ስጦታዎች ያስታውሰናል። አንተም የእግዚአብሔርን ጸጋ በሕይወትህ ውስጥ እስከ ተለማመድህ ድረስ ለሌሎች ለመስጠት አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ማመካኛ አድርገህ አትጠቀምባቸውም። ለነገሩማ እንዲያውስ ሁኔታዎች የመስጠት አገልግሎታችንን ያበረታቱበት ወቅት ጨርሶ ይኖር ይሆን? በመጀመሪያው የመጋቢነት አገልግሎቴ ወቅት፥ አዲስ ቤተ ክርስቲያን ማነጽ በጣም ያስፈልገን ነበር፤ ዳሩ ግን አንዳንድ ሰዎች «ከኢኮኖሚው ሁኔታ» የተነሣ ተቃወሙት። በዚያን ወቅት የብረትና የሌሎችም ፋብሪካዎች ሥራቸውን በአድማ ለማቆም የተነሣሡበት ነበር። በተጨማሪም የባቡር ሐዲዶችና የነዳጅ ማደያዎችም ችግር ፈጥረው ነበር ..ስለሆነም ቤተ ክርስቲያንን ለማነጽ የማይቻል ይመስል ነበር። ዳሩ ግን «በጸጋ መስጠት»ን የሚያምኑ በቂ ሰዎች ስለ ነበሩ፥ ቤተ ክርስቲያኗ አዲስ ሕንፃ ለማሠራት ቻለች ያንን ሁሉ የኢኮኖሚ ችግር በመወጣት! በጸጋ መስጠት ማለት በሁኔታዎች ሳይገደቡ መስጠት ማለት ነው። በፍላጎት ስንሰጥ (2ኛ ቆሮ.8፡3-4) በልግስና መስጠትና ደግሞም ያለ ፍላጎት መስጠት፥ ሁለቱም ይቻላሉ። አንድ ቆንቋና ምዕመን፥ «ሰባኪው እስኪጎዳኝ ድረስ መስጠት እንዳለብኝ ይናገራል፤ ለእኔ ግን፥ ስለ መስጠት ማሰቡ ራሱ ይጎዳኛል» እስከ ማለት መድረሱ ይነገራል። የመቂዶንያ አብያተ ክርስቲያናት፥ እንደ ቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን መቀስቀስ ወይም ማስታወስ አላስፈለጋቸውም። እንዲያውም ከሚሰባሰበው ገንዘብ ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ ለማዋጣት ፈቃደኞች ነበሩ። ይህም ዕድል እንዲሰጣቸው እስከ መማጸን ደርሰዋል። ለመሆኑ አንድ ክርስቲያን ስጦታውን ሌላው እንዲቀበለው እስከ መለመን የደረሰበት ሁኔታ ስንት ጊዜ አጋጥሞህ ይሆን? ስጦታቸው ፈቃደኝነትና ግብታዊነት የሚታይበት ነበር። የጸጋ እንጂ፥ ከመገደድ የተነሣ የተፈጸመ አልነበረም። ለልግስናው የተሽቀዳደሙት የእግዚአብሔርን ጸጋ ስለ ተለማመዱና ለመስጠት ስለፈለጉ ነበር። ጸጋ ከኃጢአት ማንጻት ብቻ ሳይሆን፥ ከራሳችንም ያነጻናል። የእግዚአብሔር ጸጋ ልብህንና እጅህን ይፈታዋል። የምትሰጠውም በቀዝቃዛ የሂሳብ ስሌት ተመርተህ ሳይሆን፥ ዳሩ ግን ከሙቅ ልብ በሚመነጭ ሐሤት ነው። እንደ ኢየሱስ ስንሰጥ (2ኛ ቆሮ.8፡5-9) በአገልግሎትም ይሁን በመከራ፥ ወይም ራስን በመሠዋት ሁሉ አማኙ ሊከተለው የሚገባው ከሁሉም የላቀውን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌነት ነው። የኢየሱስ ክርስቶስን ፈለግ በመከተል የመቄዶንያ ክርስቲያኖችም ራሳቸውን ለእግዚአብሔርና ለሌሎች አሳልፈው ሰጥተዋል (ቁ 5)። ራሳችንን ለእግዚአብሔር ከሰጠን፥ ንብረታችንን ለእግዚአብሔር መስጠቱ ብዙም አይከብደንም። እንዲሁም ራሳችንን ለእግዚአብሔር ከሰጠን፥ ለሌሎችም ደግሞ ራሳችንን እንሰጣለን። እግዚአብሔርን እየወደዱ የባልንጀራችንን ችግር ችላ ማለት የማይቻል ነገር ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ለእኛ ሲል ሰጥቶአል (ገላ. 1፡4፤ 2፡20)። እኛስ ራሳችንን ለእርሱ መስጠት የለብንም? የሞተልን ለራሳችን ሳይሆን፥ ዳሩ ግን ለእርሱና ለሌሉች እንኖር ዘንድ ነው (2ኛ ቆሮ. 5፡15)። የመቄዶናውያን ስጦታ፥ ልክ እንደ ክርስቶስ በፍቅር አነሣሽነት የተከናወነ ነበር (8፡7-8)። ይህ በመንፈሳዊ በረከቶች ለበለጸጉት የቆሮንቶስ ሰዎች ምንኛ ተግሣጽ ነበር (1ኛ ቆሮ.8:4-5)። እነርሱ ግን በመንፈስ ቅዱስ ስጦታዎች ዙሪያቸውን ታጥረው ስለ ነበር፥ የመንፈስ ቅዱስን የጸጋ ስጦታዎችንም ሆነ በጸጋ ተነሣሥተው መለገስን ዘንግተው ነበር። የመቄዶንያ አብያተ – ክርስቲያናት «ጥልቅ ድህነት» (2ኛ ቆሮ. 8፡2) ደርሶባቸው ሳለ፥ ዳሩ ግን አብዝተው ሊሰጡችለዋል። የቆሮንቶስ ሰዎች ግን በርካታ መንፈሳዊ ስጦታዎች ቢኖሯቸውም፥ ዳሩ ግን ተስፋ የሰጡትን ቃል ለመጠበቅና በሚሰበሰበው ገንዘብ ውስጥ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት ግድ የለሾች ነበሩ። የመንፈሳዊ ስጦታዎችን አገልግሎት በልግስና ለማከናወን የመስጠት ተግባር ምትክ ሊሆን ይችላል ብለን ልንከራከር አይገባም። «በሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ ስለማስተምር፥ መስጠት አያስፈልገኝም» የሚለው ማመካኛ እንጂ፥ አጥጋቢ የማሳመኛ ነጥብ አይደለም። ስጦታዎቹ በእርግጥም ስጦታዎች እንደ ሆኑ የሚያስብ ክርስቲያን ምን ጊዜም የሚነሣው ለሌሉች ለመስጠት እንጂ በጌታ አገልግሎት ሽፋን «ልደበቅ» አይልም። እኔንም ቢሆን፥ አንዳንድ ሙሉ ጊዜያቸውን ለጌታ አገልግሎት በማዋላቸው፥ ለመስጠት እንደማይገደዱ በመግለጽ የተከራከሩኝ መጋቢዎችና ሚሲዮናውያን አጋጥመውኛል። ጳውሎስ ከዚህ የሚቃረን አሳብ ነበረው፡- ከእግዚአብሔር ዘንድ ግሩም ስጦታ ስለ ተሰጣችሁ፥ አብልጣችሁ ለመስጠት መሻት አለባችሁ። ከዚህም ሌላ ጳውሎስ እንዲሰጡ ያዘዛቸው ራሱ እንዳልሆነ በግልጽ እንዲያውቁት ይጠነቀቅ ነበር። እንዲያውም የቆሮንቶስን ሰዎች አመለካከትና ከመቄዶንያ ሰዎች ጋር እያነጻጸረ ነበር። የመቄዶንያ ክርስቲያኖች የጌታን ምሳሌ እየተከተሉ መሆናቸውን በግልጽ መሰከረ፡ ድሆች ሆነው ሳሉ ሰጡ። ከዚህም በመነሣት የቆሮንቶስ ሰዎች ጳውሎስን እንደሚወዱት ይናገሩ ስለ ነበር፥ በሚሰበሰበው ገንዘብ ውስጥ ተካፋይ
የመስጠት ጸጋ፣ ክፍል 1 (ቆሮንቶስ 8፡1-24) Read More »
