ጉዲፈቻ (የማደጎ ልጅ)
በደኅንነታችን ውስጥ ካገኘናቸው በረከቶች መካከል በጣም የሚያስደስተንና የሚያጽናናን የእግዚአብሔር ጎልማሳ ልጆች ከመሆናችን የተነሣ ያለን የተትረፈረፈ የርስት ዋስትና ነው። በዚህ ረገድ እግዚአብሔር አዲስ ሕይወትን፥ ከክርስቶስ ጋር ኅብረትን እንዲሁም ከበደላችን ነፃ መውጣትን የሰጠን ብቻ ሳይሆን በተጨማሪም የራሱ ልጆችና የሰማያዊ ክብር ወራሾችም እንድንሆን መብት ሰጥቶናል። የእግዚአብሔር አዋቂ (ጎልማሳ) ልጆች የመሆን በረከት የ«ጉዲፈቻ የማደጎ ልጅ» መሆን ማለት ነው። ጥያቄ፡- ኤፌ 1፡5ን አንብብ፡፡ እግዚአብሔር ምን እንድንሆን ነበር የመረጠን? ጥያቄ፡- ገላ.4፡1-7 አንብብ፡፡ ሀ) ገና ሕፃን ወራሽ የሆነ ልጅ ሁኔታ ምን ይመስላል (ቁ. 1-2)? ለ) እኛስ በዚህ ዓይነት ሁኔታ የነበርነው መቼ ነው? (ቁ 3) ሐ) ክርስቶስ ባዳነን ጊዜ ምንን ተቀበልን (ቈ 5)? መ) አሁን የእግዚአብሔር ልጆች እንደ መሆናችን መጠን በተጫማሪ እግዚአብሔር ምን አድርጎልናል (ቈ 7)? ጥያቄ፡- ርሜ 8፡14-17 አንብብ። ሀ) በእግዚአብሔር መንፈስ ስለሚመሩት ያለው እውነታ ምንድን ነው (ቈ 14)? ለ) ምን ዓይነት መንፈስ ነው እና ያልተቀበልነው (ቁ 15 )? ሐ) የተቀበልነውስ ምን ዓይነት መንፈስ ነው (ቁ 15)? መ) ያ መንፈስ ምንን ይመሰክርልናል (ቁ 16)? ሠ) የእግዚአብሔር ልጆች በመሆናችን በተጨማሪ የተረጋገጠልን ምንድን ነው ( 17)? ጥያቄ፡- ሮሜ 8፡23 አንብቡ። ምንን እንጠባበቃለን? ስለ ልጅነት ያለውን የደኅንነት በረከት ሁኔታ ከመገንዘባችን በፊት፥ ለለ ልጅነት ወይም እንደ ራስ ልጅ አድርጎ ስለ መቀበል፥ በአዲስ ኪዳን ዘመን የነበረውን ባሕል ማወቅ ይገባናል። ዛሬ በብዙ ባሕሎች በአዲስ ቤተሰቦች ውስጥ ልጆች ለማደጎ የሚወሰዱት የራሳቸው ወላጆች ሳይኖራቸው ሲቀር ብቻ ነው። የአንድ ሕፃን አባት ወይም እናት ሲሞቱ ወይም ልጃቸውን ሲጥሉ፥ በዚህን ጊዜ ለልጁ እንደ ወላጅ የሚሆኑ አዲስ አሳዳጊዎች ልጁን ይወስዱና እንደ ወለዱት ልጅ አድርገው ያሳድጉታል። ሆኖም፥ በአዲስ ኪዳን ዘመን ሮማውያን ያልወለዱትን ልጅ ወስደው ማደጎ የሚያሳድጉበት ለየት ያለ ባሕል ነበራቸው። ይህም አንድ ሰው ልጅ ያልወለደ ከሆነ፣ የሕፃኑ ወላጆቹ በሞት ባይለዩትምና በሚገባ ቢንከባከቡትም እንኳ የሌላ ቤተሰብን ልጅ ተቀብሉ በማደጎ ደንብ እንደ ራሱ ልጅ አድርጎ ያሳድገዋል። አንድ ሮማዊ የሌላውን ቤተሰብ ልጅ በማደጎ ወስዶ የሚያሳድገው ያፈራው ሀብትና ንብረት ወራሽ እንዲሆንለት ነው። ስለዚህ በርማውያኑ ባሕል የሌላውን ልጅ ወስዶ እንደ ራሱ ልጅ አድርጎ የማሳደግ ዓላማ የሀብትና ንብረት ወራሽ እንዲሆን የቤተሰቡ አባል የማድረግ ሂደት ነበር። 1. እንደ ራስ ልጅ በማደጎ ተቀብሎ የማሳደግ ሁኔታ በኃላፊው ዘላለም ውስጥ፡ ኤፌ. 1፡5 አዲስ ኪዳን በእግዚአብሔር ቤተሰብ እንደ ልጅ የተደረግንበትን ሁኔታ በሦስት ደረጃ ዎች ይመለከተዋል። ይህ መንፈሳዊ ሂደት ሦስት መሠረታዊ ደረጃ ዎች ያሉት ሲሆን፥ እያንዳንዱ ደረጃም ልጅ የመደረግ ሂደትን የተለየ አፈጻጸም አጽንኦት ይሰጥበታል። የዚህ እንደ ልጅ ወደ እግዚአብሔር ቤተሰብ የመምጣት ሁኔታ የመጀመሪያው ደረጃ ልጅነታችንን ለማረጋገጥ እግዚአብሔር ቀደም ባለው ዘመን የፈጸመው ተግባር ነው። በኤፌ 1፡5 ላይ «ልጆቹ እንድንሆን አስቀድሞ ወሰነን» ይላል። ሰኛው ትምህርት ላይ እንደተመለከትነው፥ እግዚአብሔር አስቀድሞ ባደረገው ምርግ መሠረት የወራሽነት መብት ሊሰጠን የቤተሰቡ አካል አድርጎ በልጅነት ተቀበለን። ነገር ግን እግዚአብሔር ለውርስ የደረስን ጎልማሳ ልጆቹ አድርጎ እንዴት ይቀበለናል? ዛሬስ የቤተሰቡ አካል አድርጎ ሊቀበለን ምን አድርጎአል? 2. በአሁኑ ደኅንነታችን እንደ ማደጎ ልጅ መሆናችን፡ ገላ. 4፡1-7 ጳውሎስ በገላ. 4፡1-7 ውስጥ እንደተናገረው፥ በኋለኛው ጊዜ እግዚአብሔር እንደ ልጆቹ አድርጎ እንዴት እንደ ተቀበለን ይገልጻል። ገለጻውንም በመቀጠል አንድ ልጅ ምንም እንኳን የወራሽነት መብት ቢኖረውም፣ በሕፃንነት ዕድሜ ባለበት ጊዜ በውርሱ ላይ ሥልጣን እንደሌለውና በዚህን ጊዜ ሁሉም ነገር በሞግዚቶች እጅ እንደሚሆን ያስረዳል። ሕፃኑ በዚህ ዕድሜው በሚገኝበት ጊዜ በአመዛኙ ከባርያ የማይለይ በመሆኑ የዚቶቹ ታዛዥ ሆኖ እንደሚቆይና እንደ ባለ ሙሉ ሥልጣን ወራሽ ሆኖ እንደማይታይ ያላነዝባል። ጳውሎስ እንደሚለው ሁላችንም በእምነት ወደ ክርስቶስ ከመምጣታችን በፊት የነበርንበት ሁኔታ ያን ይመስላል። የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ለመጠራትም ሆነ የእርሱ ወራሾች ለመሆን ምንም ዓይነት ሕጋዊ መብት አልነበረንም። እንደ እውነቱ ከሆነ፣ ሕጋዊ መብት እንዳለው ልጅ ሳይሆን በባርነት ደረጃ ላይ የነበርን ሰዎች ነን። ሙሉ በሙሉ ለዓለም ሥርዓቶች የተገዛን ነበርን። ጳውሎስ ለዓለም ሥርዓቶች የተገዛችሁ ነበራችሁ ሲል ምን ማለቱ ነው? «ከዓለም መሠረታዊ ትምህርት» ሲል በጊዜው ለዚህ ማብራሪያ በሥራ ላይ የነበረው የግሪክ ቃል የሰማይን አካላት (ክዋክብትንና፡ ፕላኔቶችን) ይቆጣጠራሉ የተባሉ የግሪክ የሐሰት አማልክትንና የዓለምን ሕዝቦች የሚያመለክት ነበር። እነዚህ የሐሰት አማልክት የፍጥረትና የሕዝቦች «መሠረታዊ ተቆጣጣሪ» ኃይላት ነበሩ። በጊዜው ግሪክኛ ይናገሩ የነበሩ አይሁዳውያንም ይህን ቃል እግዚአብሔር በእነርሱ አማካይነት ሕጉን ለሙሴ የሰጠባቸውን መላእክትና (ገላ 3፡19፤ የሐዋ. 7፡53) በዓለም ሕዝቦች ላይ ተቆጣጣሪዎች ናቸው ብለው የሚያምኑባቸውን መላእክት ለመግለጽ ይጠቀሙበት ነበር። የእስራኤል ሕዝብም ሆነ የአሕዛብ የቅርብ ተቆጣጣሪዎች ነበሩ ባይ ናቸው። በዚያን ዘመን የሰዎችን ሕይወት ይቆጣጠራሉ ተብለው የሚታወቁ መሠረታውያን የዓለም ትምህርቶች ክፉና መልካም መላእክትን የሚያጠቃልሉ ኃይላት ነበሩ። ጳውሎስ ሊል የፈለገው አንድ ጊዜ እኛ በእነዚህ መናፍስት ኃይላት ቁጥጥር ሥር ነበርን፥ ዛሬ ግን ነፃ ነን ለማለት ነው። እውነትም ከአጋንንታዊ ኃይላት ማለትም ግሪኮች ይሰግዱላቸው ከነበሩት ዓይነት ሐሰተኛ አማልክት ቁጥጥር ነፃ ነን። ደግሞም መልካም በሆኑ መላእክት ከተሰጡት ሕጎች ቁጥጥር ነፃ ነን። ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት እንዲኖረን መልካም ይሁኑ ክፉዎች የማናቸውም መናፍስት ኃይላት አማላጅነት አያስፈልገንም። ስለዚህ ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት ሊያደናቅፉብን አይችሉም። ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት እንዲኖረን እንደ ግርዛት ያሉትን የአይሁዳውያንን ሥርዓት ከመከተል ነፃ ነን። ከእነዚህ መናፍስት ኃይላት ነፃ የሆንነው እንዴት ነው? እግዚአብሔር ጌታ ኢየሱስ ሰው ሆኖ እንዲወለድ በላከው ጊዜ፥ የሕግ ባሪያዎች ከመሆን አድኖ እንደ ልጆቹ አድርጎ በመቀበል የቤተሰቡ አካል አደረገን። እንደ ጎልማሳ ልጆች መብትን ሰጠን። ከዚያ በፊት በመናፍስት ኃይላት ቁጥጥር ሥር የነበርንና የሌላ ቤተሰብ አካል ነበርን። አይሁዳውያን በሙሴ ሕግ ሥርዓት ሥር ነበሩ። ነገር ግን ::ግዚአብሔር እኛን እንደ ራሱ ልጆች የቤተሰቡ አካል አድርጎ ተቀበለን። ለውርስ የምንበቃ ጎልማሳ ልጆቹ አድርጎ የወራሽነት መብትን ሰጠን። መንፈስ ቅዱስም በውስጣችን አድሮ እኛ የእርሱ ቤተሰብ አካል መሆናችንን እንዲያሳስበንና እንዲያረጋግጥልን አደረገ። በዚሁ መሠረት እግዚአብሔር የመለኮታዊ ውርሱ ወራሾች እንድንሆን ጎልማሳ ልጆች አደረን። ጥያቄ፡- ሀ) በአካባቢአችሁ የሚኖሩ ሰዎች በምን አኳኋን የመናፍስት ኃይላትን አማላጅነት ይሻሉ? ለ) ይህ ክፍል ለእነዚህ ሰዎች ምን መልእክት ይሰጣቸዋል? ሐ) በእናንተ አካባቢ ያሉ ሰዎች የብሉይ ኪዳንን ሥርዓተ አምልኮ መከተል እንደሚገባቸው የሚያስቡት በምን አኳኋን ነው? መ) ይህ ክፍል ለእዚህ ሰዎች ምን ትምህርት ይሰጣቸዋል? ገላ. 3፡23-25 እና 5፡1ን አንዳንድ አሳቦችን ላለመጨበጥ ያክል ተመልከት። ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ ሰዎች በመናፍስት ኃይል ቁጥጥር ሥር ያሉ ይመስላቸዋል። ብዙ ሰዎች መንፈሳዊ ኃይላትን ማክበርና የሕይወትን በረከት ለማግኘት፥ እንደዚሁም ከሚያጋጥማቸው ሁሉ ለመጠበቅ የመንፈሳዊ ኃይላት አማላጅነት የሚያስፈልጋቸው አድርገው ያምናሉ። ሌሎች ሰዎች ደግሞ መላእክትን ማክበርና ለአማላጅነት እነርሱን ለመማጠን ወደ እነርሱ ዘንድ መቅረብ እንዳለባቸው ይሰማቸዋል። አንዳንዶቹ ደግሞ ለመናፍስት ስጦታና መሥዋዕት ማቅረብን ተግባራቸው አድርገው ይይዛሉ፡ አንዳንድ ሰዎች እንዲጠብቋቸው ወይም በረከት እንዲያገኙ ለመናፍስት ማለትም ውቃቢ ወይም ዛር ስጦታና መባ ማቅረብ እንዳለባቸው ይሰማቸዋል። እርግጥ ሰዎች ክርስቶስን እንደ መድኃኒታቸው አድርገው ከመቀበላቸው በፊት እነዚህ ክፉ መናፍስት ተጽዕኖ ሊያደርጉባቸው ችለው ይሆናል። ነገር ግን ገላ. 4፡1-7 እንደሚነግረን፥ ማንኛውም ሰው አንዴ በክርስቶስ ካመነ በኋላ በመናፍስት ቁጥጥር ሥር ሊውል አይችልም። ያመኑ ሰዎች የመላእክትንም ሆነ የሌሎች መናፍስትን አማላጅነት አይሹም። ስጦታም ሆነ መሥዋዕት ለመናፍስቱ ማቅረብ አይኖርባቸውም። እግዚአብሔር ከማንኛውም መናፍስት ባርነት ነፃ አውጥቶ የቤተሰቡ አካል አድርጎአቸዋል። እግዚአብሔር እንደ ጎልማሳ ልጆቹ በመቀበል ለተትረፈረፈ ውርሱ ወራሾች አድርጎአቸዋል። ልጆቹ መሆናቸውንም እንዲያረጋግጥላቸው መንፈስ ቅዱስን ሰጥቶአቸዋል። እግዚአብሔር እኛን እንደ ልጆቹ ተቀብሎ የቤተሰቡ አካል አደረገን ማለት በምንም ዓይነት (ከአሁን ወዲያ እኛ) በክፉ መናፍስት ቁጥጥር ሥር ልንሆን አንችልም ማለት ነው። ዛሬም ቢሆን በኢትዮጵያ ውስጥ አንዳንድ ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር ለመቀራረብና ቤተኛ ለመሆን የብሉይ ኪዳንን ሥርዓተ
