ትንቢተ ዘካርያስ

ዘካርያስ 1-14

ብዙ ሰዎች እግዚአብሔር ትንቢትን የሰጠው ወደፊት ምን እንደሚሆን እንድናውቅ ነው ብለው ያስባሉ። ስለዚህ የትንቢትን መጻሕፍት የሚያጠኑት በከፍተኛ ጉጉት ነው። ወደፊት በመካከለኛው ምሥራቅ ምን እንደሚሆን ለማወቅ፥ ወይም ሩስያ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተጠቅሳ እንደሆነ ወይም በመጨረሻዎቹ ቀናት ከእስራኤል ጋር የሚዋጉት አገሮች የትኞቹ እንደሆኑ ለማወቅ በመጓጓት ያጠናሉ። የውይይት ጥያቄ፥ አንዳንድ ክርስቲያኖች ትንቢትን በተመለከተ የዚህ ዓይነት አመለካከት ሲጠቀሙ ያየኸው እንዴት ነው? እግዚአብሔር የትንቢት መጻሕፍትን መልእክት የሰጠን ወደፊት ምን እንደሚሆን የማወቅ ፍላጎታችንን ለማርካት አይደለም። ትንቢት የተሰጠው የእግዚአብሔርን ሕዝቦች በተለይም ደግሞ በስደት ውስጥ የሚኖሩትን እግዚአብሔር የበላይ ተቆጣጣሪ መሆኑን በማስተማር ለማበረታታት ነው። እግዚአብሔር ስለመጪው ጊዜ ዕቅድ አለው። ይህ ዕቅድ ጦርነቶችንና ፍርድን የሚጨምር ነው። ይህም ቢሆን በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር የሚፈጸም ነው። ይህ ዕቅድ በሚጠቃለልበት ጊዜ እግዚአብሔር ፍጹም በሆነው ምድር ይነግሣል። ኃጢአትና ሞት ይደመሰሳሉ። ክርስቲያኖች በእምነታችን ምክንያት በምንሰደድበት ጊዜ ወይም ብዙ ችግሮች ሲያጋጥሙን ፍጻሜያችን መልካም መሆኑን በማስታወስ ልብ ገዝተን ልንኖርና በእምነታችን ልንጸና እንችላለን። ወደፊት እግዚአብሔር ምን ሊያደርግ እንዳለው በእምነት መመልከት እንችላለን። በትንቢተ ዘካርያስ ውስጥ ዘካርያስ ተስፋ የቆረጡትን አይሁድ የሚያበረታታበት ዋና መንገድ የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን መምጣትና እርሱም የሚያመጣውን በረከት በማሳየት እግዚአብሔር የሁሉ ነገር የበላይ ተቆጣጣሪ መሆንን በማረጋገጥ ነበር። የውይይት ጥያቄ፥ ዘካርያስ 1-14 አንብብ። ሀ) ዘካርያስ ያያቸውን የተለያዩ ራእዮች ዘርዝር። የእነዚህ ራእዮች ትርጉም ምን ይመስልሃል? ለ) በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ወደፊት ስለሚሆኑ ነገሮች የተጠቀሱትን የተለያዩ ትንቢቶች ዘርዝር። ሐ) ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠቀሱትን የተለያዩ ትንቢቶች ዘርዝር። ክፍል 1፥ አይሁድ ቤተ መቅደሱን በመሥራት ላይ ሳሉ የመጡላቸው መልእክቶች (ዘካርያስ 1-8) 1. ዘካርያስ ንስሐ እንዲገቡ ለሕዝቡ ጥሪ አደረገ (ዘካርያስ 1፡1-6) አይሁድ ለእግዚአብሔር ታዝዘው ቤተ መቅደሱን እየሠሩ ቢሆኑም እንኳ በሕይወታቸው አሁንም ኃጢአት ነበር። ስለዚህ ትንቢተ ዘካርያስ የሚጀምረው አይሁድን ስለ ኃጢአታቸው በመውቀስና ንስሐ እንዲገቡ ጥሪ በማድረግ ነው። ለእግዚአብሔር አንድ ነገር ከምናደርግለት ይልቅ ብንቀደስለት ይመረጣል። እግዚአብሔር የምናደርግለትን ነገር የሚቀበለው ከኃጢአታችን ንስሐ ስንገባ ብቻ ነው። አይሁድ የዘካርያስን መልእክት ከሰሙ በኋላ ንስሐ ገቡ። እግዚአብሔርም ይባርካቸው ዘንድ ከሚችልበት ሁኔታ ላይ ደረሱ። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በዚህ ዘመን ብዙ ክርስቲያኖች ቅዱሳን ከመሆን ይልቅ የእግዚአብሔርን ነገር ማከናወን የሚቀላቸው ለምንድን ነው? ለ) ይህ ነገር ሲፈጸም እንዴት እንደተመለከትህ የሚያስረዱ ሥዕላዊ መግለጫዎችን ዘርዝር። ሐ) እግዚአብሔር ለእርሱ ምንም ነገር ከማድረጋችን በፊት እንቀደስ ዘንድ በእጅጉ አበክሮ የሚናገረው ለምን ይመስልሃል?  2. ዘካርያስ በሌሊት ያያቸው ስምንት ራእዮች (ዘካርያስ 1፡7-6፡8) ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት እንዲኖራቸው ካደረገው መልእክቱ ቀጥሎ፥ ዘካርያስ በአንድ ሌሊት ያያቸውን ስምንት ራእዮች ያቀርባል። እነዚህ ራእዮች በአሕዛብ እንደተጨቆኑ በመቁጠር ኃዘን የተሰማቸውንና ለእግዚአብሔር በሚሠሩት ሥራ ተስፋ ቆርጠው የነበሩትን አይሁዶች የሚያበረታቱ ነበሩ፤ እያንዳንዳቸው እግዚአብሔር ለአይሁዶች የሰጠውን ግልጽ የሆነ ልዩ የማበረታቻ መልእክት የያዙ ነበሩ። ሀ. የመጀመሪያው ራእይ – በዛፎች መካከል ቆሞ የነበረው ፈረሰኛ (ዘካርያስ 1፡7-17)  አይሁድ ወደ አገራቸው ቢመለሱም፥ ገና በአሕዛብ ቁጥጥር ሥር ነበሩ። አሕዛብ በምቾት ሲዝናኑ እነርሱ ግን በመከራ ውስጥ ነበሩ። ነገር ግን እግዚአብሔር ነገሮችን ተቀጣጥሮ ነበር። ፈረሰኛው በዓለም ሁሉ ተዘዋውሮ ሰላምን እንዳገኘ ሁሉ እግዚአብሔርም ቤተ መቅደሱ እንደሚሠራና የእስራኤል ሕዝብ በሰላም እንደሚኖር ለአይሁድ ተስፋ ሰጠ። ሰላም እየመጣ ነበር፤ ዳሩ ግን እግዚአብሔር በእነርሱ ምትክ ሆኖ እስኪሠራና የይሁዳን ምድር እስኪያድስ ድረስ መጠበቅ ነበረባቸው። ለ. ሁለተኛው ራእይ – አራት ቀንዶችና አራት ጠራቢዎች (ዘካርያስ 1፡18-21)  ለአይሁድ ቀንድ የብርታትና የኃይል ምልክት ነበር። እነዚህ ቀንዶች እስራኤልን የበተኑትን መንግሥታት ወይም በአሕዛብ ላይ የነገሡትን ነገሥታት ሊያመለክቱ ይችላሉ። ቀንዶቹ እስራኤልን የበተኑና አይሁድን ወደ ምርኮ የወሰዱትን መንግሥታት የሚወክሉ ነበሩ። በዚህ ስፍራ የቀንዶቹ አራት መሆን አራት የተለያዩ መንግሥታትን የሚወክል ይሆናል የሚለው አሳብ ምሁራንን ያከራክራቸዋል። አንዳንዶች እነዚህ አራት መንግሥታት ባቢሎን፥ ሜዶንና ፋርስ፥ ግሪክና ሮም ናቸው ሲሉ፥ ሌሎች ደግሞ አሦር፥ ግብፅ፥ ባቢሎንና እንዲሁም ሜዶንና ፋርስ ናቸው ይላሉ። አራቱ ጠራቢዎች የሚወክሉት ደግሞ ለአይሁድ መበተን ምክንያት የሆኑት የአሕዛብ መንግሥታት የሚቀጡባቸውን የእግዚአብሔርን የፍርድ መሣሪያዎች ነው። እስራኤልን የወጉ ሁሉ በተራቸው ይደመሰሳሉ። አንዳንድ ምሁራን እነዚህ አራት ጠራቢዎች ባቢሎንን የደመሰሰው ሜዶንና ፋርስ፥ ሜዶንና ፋርስን የደመሰሰው ግሪክ፣ ግሪክን የደመሰሰው ሮም፥ በመጨረሻ ላይ የሮምን መንግሥት የሚደመስሰው መሢሑ ነው ብለው ያምናሉ። ዋናው ትምህርት የእስራኤልን ጠላቶች እግዚአብሔር በራሱ ጊዜ ይደመስሳቸዋል የሚለው ነው። እግዚአብሔር ጠላቶቹን የሚደመስስባቸው የተለያዩ ዓይነት ጠራቢዎች አሉት። ሐ. ሦስተኛው ራእይ – የመለኪያ ገመድ የያዘው ሰው (ዘካርያስ 2) በዘካርያስ ዘመን የኢየሩሳሌም ቅጥሮችና የከተማው አብዛኛው ክፍል ተደምስሶ ነበር። ነህምያ ከአይሁድ ጋር ቅጥሩን ለመሥራት የሚመጣው ገና ከብዙ ዓመታት በኋላ ነበር። በጥንት ጊዜያት አንድ ከተማ ቅጥር ከሌለው፥ የማይረባና ጥቃት መፈጸም ለሚፈልግ ጠላት ሁሉ የተጋለጠ ነበር። በዚህ ራእይ ዘካርያስ የኢየሩሳሌምን ከተማ ለመለካት የመለኪያ ገመድ የያዘ ሰው ይመለከታል። ዳሩ ግን በኢየሩሳሌም ከተማ የሚኖረው ሕዝብ እጅግ ብዙ ስለነበር ለመለካት ጨርሶ የማይቻል ነበር። እግዚአብሔር አንድ ቀን የኢየሩሳሌም ከተማ ቅጥር ሊኖራት እስከማይችል ድረስ እጅግ ታላቅ ትሆናለች የሚል ተስፋ ሰጠ። እግዚአብሔር ራሱ በከተማዋ ውስጥ ስለሚኖርና የእሳት ቅጥር ስለሚሆናት ለጥበቃ የሚሆን ምንም ዓይነት ቅጥር የማያስፈልግበት ጊዜ ይመጣል። ከአይሁድ መካከል ከምርኮ የተመለሱት ጥቂቶች ብቻ ነበሩ። ብዙዎቹ በባቢሎንና በሌሎች አሕዛብ መካከል በምቾት መኖርን መረጡ። ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ጥሪ አደረገላቸው። አንድ ቀን አይሁድን ሁሉ ከዓለም ዙሪያ በመሰብሰብ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚያመጣቸው ተናገረ። በዚያም ከእነርሱ ጋር ከሚተባበሩ ሌሎች ሕዝቦች ጋር እግዚአብሔር አብሮአቸው ይሆንና ይባርካቸዋል። መ. አራተኛ ራእይ – ለታላቁ ካህን ለኢያሱ የተሰጡ ንጹሕ አልባሳት (ዘካርያስ 3)  ኢያሱ የእስራኤል ሊቀ ካህን ነበር። ይሁን እንጂ የሚሠራበት ቤተ መቅደስና ከእርሱ አስቀድሞ የነበሩ ካህናት ይለብሱአቸው የነበሩት ዓይነት ንጹሕና ጌጠኛ አልባሳት አልነበሩትም። ታዲያ እርሱ በእርግጥ የሕዝቡ መንፈሳዊ መሪ ነበርን? እግዚአብሔር አገልግሎቱን ተቀብሏልን? ኢያሱ በእግዚአብሔር የተመረጠ መሣሪያ መሆኑን ለሕዝቡ ለማሳየት እግዚአብሔር ለዘካርያስ ራእይ ሰጠው። በዚያ ራእይ ሰይጣን ንጹሕ አይደለም በማለት ኢያሱን በእግዚአብሔር ፊት ሲከሰው እንመለከታለን። (እድፋም ልብስ የመንፈሳዊ ንጽሕና ጉድለት ምልክት ነበር።) እግዚአብሔር ግን ኢያሱን የመረጠው እርሱ እንደሆነና በፊቱ ንጹሕ እንደሆነ ለሰይጣን ያረጋግጥለታል። (ጥሩ ልብስና ንጹሕ ጥምጥም ተደረገለት።) ሊቀ ካህን መሆን እንደሚገባው ለማረጋገጥ እግዚአብሔር ለኢያሱ የሊቀ ካህን ልብስ ሰጠው። ካህን እንዲሆን የተጠራው ኢያሱ የእስራኤል ሕዝብ ተምሳሌትም ነበር (ዘጸአት 19፡5-6)። ሰይጣን ኢያሱን እንደከሰሰ የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ የሆኑትን እስራኤልንም ንጹሕ አይደላችሁም በማለት ከሰሳቸው። ዳሩ ግን እግዚአብሔር አንጽቶ እንደገና የእርሱ ካህናት ይሆኑ ዘንድ ጠራቸው። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ሰይጣን ኃጢአተኛ ነህ በማለት ለሚከሰው ክርስቲያን እግዚአብሔር ስለሚሰጠው መልስ ይህ ራእይ ጥሩ መግለጫ የሚሆነው እንዴት ነው? ለ) ኃጢአታችን የተሸፈነው በምንድን ነው? በዚህ ራእይ ስለ ኢየሱስ የሚናገር አሳብ እናገኛለን፤ እርሱም ቅርንጫፍ ተብሏል። ይህም በኢሳይያስ 4፡2 እና በሌሎችም የብሉይ ኪዳን ክፍሎች ከዳዊት ሥር የሚመጣውን መሢሕ ለማመልከት የተጠቀሰ ተምሳሌታዊ አገላለጽ ነው። ይህ ትንቢት ሙሉ በሙሉ የሚፈጸመው በእርሱ ብቻ ነው። የሰዎችን ኃጢአት ለመሸፈንና አይሁድን ለማዳን በመስቀል ላይ በተፈጸመው የክርስቶስ የሞቱ ሥራ አንድ ቀን ኃጢአት ከምድሪቱ ፍጹም ይወገዳል፤ ሰላምም ይኖራል። ሠ. አምስተኛ ራእይ – የወርቅ መቅረዝና ሁለት የወይራ ዛፎች (ዘካርያስ 4)  የቤተ መቅደሱ ሥራ መጓተት ብዙዎቹን አይሁድ ተስፋ አስቆርጦ ነበር። የሰሎሞንን ቤተ መቅደስ ያህል ትልቅ እንዳልነበር አወቁ። ስለሆነም ምናልባት በዘሩባቤልና በኢያሱ ላይ ማጉረምረም ሳይጀምሩ አልቀሩም። እግዚአብሔር የእስራኤል ሕዝብ የፖለቲካ መሪ የነበረውን ዘሩባቤልንና መንፈሳዊ መሪ የነበረውን ኢያሱን በመንፈሱ እንዳበረታቸው ለሕዝቡ የሚያስረዳ አምስተኛ ራእይ ለዘካርያስ ሰጠው። በዚህ ራእይ ዘካርያስ ሰባት መብራቶች የነበሩበትን አንድ የወርቅ መቅረዝ አየ። በወርቅ መቅረዙ ላይ የዘይት ማሰሮ ነበር። በወርቅ መቅረዙ አጠገብ በማሰሮው ግራና ቀኝ

ዘካርያስ 1-14 Read More »

በትንቢተ ዘካርያስ ውስጥ የሚገኙ ዐበይት ትምህርቶች

1. የመጨረሻዎቹ ዘመን  ከሥነ መለኮት ትምህርት ዐበይት ክፍሎች አንዱ «ኤስካቶሎጂ በመባል የሚታወቅ ሲሆን፥ ይህም በመጨረሻው ዘመን ስለሚሆኑት ነገሮች የሚመለከት ጥናት ነው። እስካሁን ድረስ የተመለከትናቸውን የነቢያትን መጻሕፍት ስናጠና ሁሉም በአንድ ወይም በሌላ መንገድ በመጨረሻው ዘመን ስለሚሆኑ ነገሮች እንደሚናገሩ አስተውለናል። በሩቁ መጪ ጊዜ ስለሚፈጸሙት ተናጠል ክስተቶች ለመናገር «የጌታ ቀን» ወይም «በዚያ ቀን» የሚሉ ሐረጎችን ይጠቀማሉ። ዳሩ ግን በመጨረሻው ዘመን ስለሚሆነው ነገር በጊዜ ቅደም ተከተል የሰፈረ ዝርዝር መግለጫ ያቀረበ አንድም ነቢይ የለም። የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን በዘመን መጨረሻ በሚሆኑ ነገሮች የአፈጻጸም ቅደም ተከተል ላይ የማይስማሙበት አንዱ ምክንያት ይህ ነው። ስለዚህ በተለያዩ ስፍራዎች የተሰጡትን መረጃዎች ማጠናቀርና ስለ መጨረሻው ዘመን ወደ አንድ አሳብ መድረስ የራሳችን ኃላፊነት ነው። በብሉይ ኪዳን ከሚገኙት መጻሕፍት ሁሉ በተሻለ ሁኔታ በመጨረሻው ዘመን ስለሚፈጸሙት ነገሮች ግልጽ መረጃ የሚሰጡን ሁለት የትንቢት መጻሕፍት አሉ። እነርሱም ትንቢተ ዳንኤልና ዘካርያስ ናቸው። ትንቢተ ዳንኤል የሚያተኩረው በመጨረሻ ዘመን በአሕዛብ መንግሥታት ዘንድ ምን እንደሚሆን በመናገር ላይ ነው። ዳንኤል ስለ አይሁድ ቢናገርም እንኳ፥ ታሪካቸውን አስቀድሞ የሚናገረው ከአሕዛብ መንግሥታት ጋር ካላቸው ግንኙነት አንጻር ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ዘካርያስ የሚያተኩረው የእግዚአብሔር የቃል ኪዳን ሕዝብ የሆኑትን የእስራኤልን ሕዝብ በሚመለከት ጉዳይ ላይ ነው። ዘካርያስ በተጨማሪ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት በግልጽ ከተነገሩ መረጃዎች አንዳንዶቹን ይሰጠናል። ቀጥሎ ዘካርያስ የጠቀሳቸውን የመጨረሻውን ዘመን ክስተቶች ልብ ብለህ ተመልከት፡- ሀ. እስራኤል በመጨረሻው ዘመን እንደገና ትሰበሰባለች፣ ትታደላለችም (ዘካርያስ 10፡9-12)  ለ. ኢየሩሳሌም በመጨረሻው ዘመን ትከበባለች (ዘካርያስ 12፡1-3፤ 14፡1-2)፣  ሐ. በመጀመሪያ አሕዛብ እስራኤልን ያሸንፋሉ (ዘካርያስ 14፡2)፤ መ. እግዚአብሔር ኢየሩሳሌምን ይታደጋል (ዘካርያስ 14፡3-4)፤  ሠ. እግዚአብሔር በአሕዛብ ላይ ይፈርዳል (ዘካርያስ 12፡9)፤  ረ. ይሁዳና እስራኤል እንደገና አንድ ሕዝብ ይሆናሉ (ዘካርያስ 10፡9-12)  ሰ. አይሁድ የገደሉትን መሢሑን በሚያዩበት ጊዜ ይለወጣሉ፤ ከኃጢአትም ይነጻሉ (ዘካርያስ 12፡10-13፡9)፤  ሸ. የደብረ ዘይት ተራራ ለሁለት ይሰነጠቃል። ከኢየሩሳሌም የሚፈስስ ወንዝ ይወጣል (ዘካርያስ 14፡4-6)  ቀ. አዲስ ፍጥረት፥ አዲሲቷ ኢየሩሳሌም፥ እንዲሁም አዲስ ቤተ መቅደስ ይሠራል፥ እግዚአብሔር በእስራኤል ላይ ይገዛል (ዘካርያስ 14፡6-2)  በ. አሕዛብ በኢየሩሳሌም ያመልካሉ (ዘካርያስ 14፡16)።  2. መሢሑ ኢየሱስ ክርስቶስ ትንቢተ ዘካርያስ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እጅግ አስደናቂ ትንቢቶችን የያዘ መጽሐፍ ነው። ትንቢቶቹ ዛሬ የኢየሱስን ታሪክ ለምናውቅ ለእኛ አስደናቂ ላይሆኑ ይችላሉ። ይሁን እንጂ እነዚህ ትንቢቶች ከመፈጸማቸው ከአራት መቶ ዓመታት በፊት መሰጠታቸውንና ያለ አንዳች ስሕተት በትክክል መፈጸማቸውን ስናስብ እንደነቃለን። ከአራት መቶ ዓመታት በኋላ የሚፈጸመውን ነገር ቀርቶ ከአሥር ዓመት በኋላ የሚሆኑትን ነገሮች እንኳ ማን አስቀድሞ ሊናገር ይችላል? ዳሩ ግን እግዚአብሔር ያለፈውን እንደሚያውቅ ሁሉ የወደፊቱንም ያውቃል። ለእርሱ በመቶ ወይም ከሺህ ከሚጠሩ ዓመታት በፊት እንኳ የሚሆኑትን ነገሮች አስቀድሞ መናገር እጅግ ቀላል ነው። ቀጥሎ የቀረበው ሰንጠረዥ ስለ መሢሑ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጡ ትንቢቶች እንዴት እንደተፈጸሙና የወደፊቶቹ ደግሞ እንዴት እንደሚፈጸሙ ያሳየናል። ትንቢት ኢየሱስ ትሁት ይሆናል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 6፡12፤ 13:7 የትንቢቱ ፍጻሜ  ማቴዎስ 26፡31 56 ትንቢት ኢየሱስ ሰው ይሆናል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 6፡12፤ 13፡7 የትንቢቱ ፍጻሜ  ሉቃስ 2 ትንቢት ኢየሱስ ተቀባይነት አይኖረውም፤ በሠላሳ ብርም ይሸጣል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 11፡12-13 የትንቢቱ ፍጻሜ  ማቴዎስ 26፡15፤ 27፡9-10 ትንቢት ኢየሱስ በጦር ይወጋል፤ ይገደላል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 12፡10፣ 13፡7 የትንቢቱ ፍጻሜ  ማቴዎስ 26፡31፣ ዮሐ. 19:37  ትንቢት ኢየሱስ ካህን ይሆናል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 6፡13 የትንቢቱ ፍጻሜ  ዕብራውያን 6፡20  ትንቢት ኢየሱስ የሰላምና የጽድቅ ንጉሥ በመሆን በኢየሩሳሌም ይነግሣል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 6፡13፤ 9፡9፤ 14፡9፡16 የትንቢቱ ፍጻሜ  ማቴዎስ 21፡5፤ ራዕይ 11፡15፤ ራእይ 19፡6  ትንቢት ኢየሱስ በክብር በመመለስ ሕዝቡን እስራኤልን ነጻ ያወጣል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 14፡1-6 የትንቢቱ ፍጻሜ  ማቴዎስ 25፡31 ትንቢት ኢየሱስ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ይሠራል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 6፡12-13 ትንቢት ኢየሱስ አዲስ የዓለም ሥርዓት ይመሠርታል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ14፡6-19 የትንቢቱ ፍጻሜ  ራእይ 21፡22-27፡ 22:1፣ 5 ትንቢት ኢየሱስ በቃል ኪዳኑ ደም እስራኤልን ያድሳል የተነገረበት ክፍል  ዘካርያስ 9፡11 የትንቢቱ ፍጻሜ  ማርቆስ 14፡24 ትንቢት ኢየሱስ ለተበተኑና እንደ በጎች ለሚቅበዘበዙት ሕዝቡ እረኛ ይሆናል የተነገረበት ክፍል   ዘካርያስ 10፡2 የትንቢቱ ፍጻሜ   ማቴዎስ 9፡36 ** የትንቢት መጻሕፍት የኢየሱስን የመጀመሪያና ዳግመኛ ምጽአት በግልጽ ለይተው እንደማያመለክቱ ልብ በል። አንድ ጊዜ ተቀባይነት ስለማይኖረውና ተሰቅሎ ስለሚገደለው ስለ ትሑቱ ኢየሱስ ይናገራሉ። በሚቀጥለው ቁጥር ደግሞ አይሁዳውያን ስለሚቀበሉት እንዲሁም በጽድቅና በሰላም ስለሚገዛው ንጉሥ ይናገራሉ። በሸለቆ ሥር ቆሞ አሻግሮ የሚመለከት አንድ ሰው እጅግ የተቀራረቡ በሚመስሉ ተራሮች መካከል ያለውን ርቀት በትክክል መናገር እንደማይችል፥ የወደፊቱን ብዙ መቶ ዓመታት አሻግረው የተመለከቱት ነቢያት በኢየሱስ የመጀመሪያና ዳግም ምጽአት መካከል ያለውን ልዩነት ለመመልከት አልቻሉም። ነቢያቱ የሚናገሩት ስለ ሁለት የተለያዩ ጊዜያት መሆኑ የታወቀው ከኢየሱስ የመጀመሪያ አመጣጥ በኋላ ነው። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በዘመን መጨረሻ የሚፈጸመውን ነገር ማወቅ ዛሬ በክርስቲያናዊ ጉዞአችን የሚያበረታታን እንዴት ነው? ለ) የዘካርያስ ትንቢቶች የሚያበረታቱን እንዴት ነው? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡) የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡

በትንቢተ ዘካርያስ ውስጥ የሚገኙ ዐበይት ትምህርቶች Read More »

የትንቢተ ዘካርያስ አስተዋጽኦ እና አላማ

የትንቢተ ዘካርያስ አስተዋጽኦ ክፍል 1፥ አይሁድ ቤተ መቅደሱን በመሥራት ላይ እያሉ የተነገሯቸው መልእክቶቹ (ዘካርያስ 1-8)  1. ሕዝቡ ንስሐ እንዲቡ ዘካርያስ ጥሪ ማድረጉ (ዘካርያስ 1፡1-6)፣  2. ዘካርያስ በሌሊት ያያቸው ስምንት ራእዮች (ዘካርያስ 1፡7-6፡8)፣  ሀ. የመጀመሪያው ራእይ – በዛፎች መካከል የቆመው ፈረሰኛ (ዘካርያስ 1፡7-17)።  ለ. ሁለተኛው ራእይ – አራቱ ቀንዶችና አራት ጠራቢዎች (ዘካርያስ 1፡18-21)፥  ሐ. ሦስተኛው ራእይ – የመለኪያ ገመድ የያዘ ሰው (ዘካርያስ 2)፥ መ. አራተኛው ራእይ – ለታላቁ ካህን ለኢያሱ የተሰጡት ንጹሕ አልባሳት (ዘካርያስ 3)፥  ሠ. አምስተኛው ራእይ – የወርቁ መቅረዝና ሁለት የወይራ ዛፎች (ዘካርያስ 4)፥  ረ. ስድስተኛው ራእይ – በራሪ የመጽሐፍ ጥቅልል (ዘካርያስ 5፡1-4)፥  ሰ. ሰባተኛው ራእይ – በኢፍ መስፈሪያ ውስጥ ተቀምጣ የነበረችው ክፉ ሴት (ዘካርያስ 5፡5-11)፥  ሸ. ስምንተኛው ራእይ – አራቱ ሰረገሎች (ዘካርያስ 6፡1-8)።  3. የታላቁ ካህን የኢያሱ ተምሳሌታዊ አክሊል መጫን (ዘካርያስ 6፡9-15)፥  4. ጾምን የሚመለከት ችግርና የወደፊት ታላላቅ ተስፋዎች (ዘካርያስ 7-8)፡  ክፍል 2፥ መጪውን ጊዜ የሚመለከቱ ለአይሁድ የተሰጡ ሁለት መልእክቶች (ዘካርያስ 9-12)።  1. የመጀመሪያው መልእክት – የመሢሑ መምጣትና ተቀባይነት ማጣት (ዘካርያስ 9-11)፥  2. ሁለተኛው መልእክት – የመሢሑ መምጣትና ተቀባይነት ማግኘት (ዘካርያስ 12-14)። ** የትንቢተ ዘካርያስ ሁለተኛ ክፍል የተጻፈው የመጀመሪያው ክፍል ከተጻፈ ከብዙ ዓመታት በኋላ ሳይሆን አይቀርም። ብዙ ምሁራን ሁለተኛው ክፍል የተጻፈው የቤተ መቅደሱ ሥራ ከተጠናቀቀ በኋላ ነው ብለው ያስባሉ። የትንቢተ ዘካርያስ ዓላማ ማንኛውም የቤተ ክርስቲያን መሪ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለመምራት የሚያስችሉ ስጦታዎች ሁሉ ለብቻው ሊኖሩት አይችሉም። ዳሩ ግን እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያንን ያዋቀረው እንደ አንድ አካል በመሆኑ፥ እያንዳንዱ የቤተ ክርስቲያን አባል የተለዩ ስጦታዎችና ችሎታዎች ይኖሩታል፡፡ እነዚህም በኅብረት በመሥራት ጠንካራ ቤተ ክርስቲያንን ያስገኛሉ። እግዚአብሔር ሐጌን የጠራው ከምርኮ የተመለሱ አይሁዳውያን ቤተ መቅደሱን እንዲሠሩ ለማነሣት ነበር። ዳሩ ግን የእግዚአብሔር ፍላጎት ከቤተ መቅደስ ሕንጻ ሥራ የላቀ ነበር። የቤተ መቅደሱ ሕንጻ ሥራ እንደተጠናቀቀ ሕዝቡ ያመልኩት ዘንድ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲዘጋጁ ይፈልግ ነበር። ስለዚህ እግዚአብሔር ነቢዩ ዘካርያስን በመጥራት፥ በሕዝቡ መካከል መንፈሳዊ መነቃቃትን ለማምጣት ተጠቀመበት። ሐጌና ዘካርያስ በአንድነት በመሆን ቤተ መቅደሱ እንዲሠራና በሕዝቡ መካከል መንፈሳዊ ተሐድሶ እንዲካሄድ ለማድረግ ቻሉ። ዘካርያስ እግዚአብሔር ዛሬም ከአንድ የቤተ ክርስቲያን መጋቢ ወይም መሪ የሚፈልገው ዓይነት ሰው ምሳሌ ነው። ዘካርያስ አንድ የቤተ ክርስቲያን መጋቢ ለሕዝቡ መንፈሳዊ ዕድገትና ተሐድሶ ለማምጣት ከፈለገ ማድረግ ያለበትን ብዙ ተግባራት አሟልቶአል። ትንቢተ ዘካርያስ የተጻፈው በሚከተሉት ምክንያቶች ነው፡- 1. ዘካርያስ ሕዝቡ ለእግዚአብሔር የገቡትን ቃል ኪዳን በመተላለፋቸው ሕዝቡን ይወቅሳቸዋል። እግዚአብሔር በፍርድ እንዳስማረካቸው እንደ ቀድሞ አባቶቻቸው ሆነው ነበር (ዘካርያስ 1፡3-5፤ 7፡8-14)። ዘካርያስ መልካም መጋቢዎች ሁሉ እንደሚያደርጉት፥ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ጋር ያፋጥጣቸዋል፤ ንስሐ እንዲገቡ አለበለዚያ ግን ስለ ኃጢአታቸው የእግዚአብሔር ፍርድ እንደሚጠብቃቸው በመንገር ያስጠነቀቃቸዋል። 2. ዘካርያስ ሕዝቡን መውቀስ ብቻ ሳይሆን፥ ለችግራቸው የሚሆን መፍትሔም ይሰጣቸዋል። ንስሐ እንዲገቡና ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ይነግራቸዋል (ዘካርያስ 1፡3-5)። እግዚአብሔር በቤተ መቅደስ የሚያቀርቡትን አምልኮ የሚቀበለው ንስሐ ገብተው እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ላደረገው ቃል ኪዳን ሲታዘዙ ብቻ እንደሆነ ይገልጥላቸዋል። እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ለሚታዘዙ ሊሰጥ ቃል የገባው በረከት ወደ ሕዝቡ የሚመጣው ይህን ካደረጉ በኋላ ብቻ ነበር (ዘካርያስ 6፡9-15፤ 8፡13)።  3. ዘካርያስ እውነተኛ ንስሐ የሰዎችን ባሕርይ እንደሚለውጥ ያውቅ ነበር። ስለዚህ ሕዝቡ እንዴት መለወጥ እንዳለባቸው ይናገራል። ለእግዚአብሔር ያላቸው መታዘዝ ከጎረቤቶቻቸው ጋር በሚኖሩት ኑሮና በማኅበራዊ ፍትሕ መገለጥ አለበት (ዘካርያስ 7፡9-10)።  4. ዘካርያስ በእግዚአብሔር ላይ ባላቸው እምነት ተስፋ ቈርጠው የነበሩትን አይሁድ ለማጽናናትና ለማበረታታት ፈልጎ ነበር። ይህንንም በሁለት ዐበይት መንገዶች አደረገው፤ በመጀመሪያ፥ ሌሊት ባያቸው ራእዮች እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር እንደሆነና ለሕዝቡ እንደሚጠነቀቅ አስተማራቸው። አሁንም አሕዛብን እየተቆጣጠረ ነበር። እግዚአብሔር መሪዎቻቸው ከሆኑት ከዘሩባቤልና ከኢያሱ ጋር ነበር። (በዘካርያስ ዘመን ለአይሁድ የተሰጠው የማበረታቻ መልእክት በዘካርያስ 1-8 ይገኛል።)  ሁለተኛ፥ የሩቁን መጪ ጊዜ በማሳየት አበረታታቸው። ስለሚመጣው መሢሕና እግዚአብሔር በዘመናት ሁሉ የገባላቸውን ቃል ኪዳን ሁሉ ይህ መሢሕ እንዴት እንደሚፈጽምላቸው ነገራቸው። (ስለ መጪው ጊዜ በመናገር አይሁድን ያበረታታበት መልእክት በዘካርያስ 8-14 ይገኛል፡፡) የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አራቱ የዘካርያስ ዓላማዎች የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ከምእመኖቻቸው ጋር ሊኖሯቸው ከሚገቡ ዓላማዎች ጋር የሚመሳሰሉት እንዴት ነው? ለ) በቤተ ክርስቲያንህ ያሉ መሪዎች እነዚህን አራት ዓላማዎች በሙሉ ያሟሉባቸውን መንገዶች የሚገልጹ ምሳሌዎችን ስጥ። ሐ) እነዚህን ዓላማዎች በተሻለ መንገድ እንዴት ሊያሟሏቸው ይችላሉ? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡) የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡

የትንቢተ ዘካርያስ አስተዋጽኦ እና አላማ Read More »

የትንቢተ ዘካርያስ ታሪካዊ ሥረ-መሠረት

አይሁድ በ539 ዓ.ዓ. ከምርኮ በተመለሱ ጊዜ ከፍተኛ መነቃቃትና ደስታ ተሰማቸው። ከሰባ ዓመታት በኋላ ከምርኮ እንደሚመለሱ እግዚአብሔር ለኤርምያስ የሰጣቸው ትንቢቶች እየተፈጸሙ ነበር። እግዚአብሔር በኢሳይያስ፥ በኤርምያስና በሕዝቅኤል የሰጣቸው ሌሎች ትንቢቶችም በቶሎ እንደሚፈጸሙ ያምኑ ነበር (ለምሳሌ፡- ኤርምያስ 30-33፤ ሕዝቅኤል 36-39)። እነዚህ ትንቢተች አይሁድ ወደገዛ ምድራቸው እንደሚመለሱ፥ መሢሑ እንደሚመጣ፥ በአሕዛብ አገዛዝ ሥር መኖራቸው እንደሚያከትም፥ ታላቁ ቤተ መቅደስ እንደገና እንደሚሠራ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደሚጀምርና ስራቸው እንደሚያበቃ የሚናገሩ ነበሩ። ስለዚህ በታላቅ ደስታ የሚመጣውን በረከት በሚጠባበቅ ልብ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው፥ እግዚአብሔርን ለማምለክ መሠዊያ ከማቆማቸውም የቤተ መቅደሱን ሥራ ጀመሩ። ነገር ግን እነዚህ ተስፋዎች አለመፈጸማቸውን ለማወቅ ብዙ ጊዜ አልወሰደባቸውም። የቤተ መቅደሱን ሥራ እንደጀመሩ በተለይ ከሳምራውያን በኩል ተቃውሞ ገጠማቸው። ሳምራውያን ከፊል አይሁዳውያን ከፊል አሕዛብ የሆኑ በጥንታዊቷ የእስራኤል ምድር ይኖሩ የነበሩ ናቸው። አይሁድ የቤተ መቅደሱን ሥራ ወዲያውኑ ለማቆም ተገደዱ። ይህም አይሁድ ከአሕዛብ ተጽዕኖ ነጻ እንዳልሆኑና አገራቸው ከቁጥር የማትገባ የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ግዛት ክፍለ ሀገር እንደነበረች አረጋገጠላቸው። አይሁድ በየስፍራው የሚመለከቱት ከ50 ዓመታት በፊት ባቢሎን ኢየሩሳሌምን በደመሰሰች ጊዜ የተረፉትን ፍርስራሾች ነበር። የቤተ መቅደሱ፥ የኢየሩሳሌም ቅጥርና በውስጧ የሚገኙ ቤቶች ፍርስራሽ በአካባቢው ነበር። አይሁድ የቤተ መቅደሱን ሥራ ለማቆም ስለተገደሉ የየራሳቸውን ቤቶች መሥራት ጀመሩ። የእግዚአብሔርን ነገሮች ረስተው፥ ለራሳቸው ፍላጎት ብቻ የሚጠነቀቁ ራስ ወዳዶች ሆኑ። ወዲያውኑ ሁሉን ነገር የሚያጥላሉ ሆኑና እግዚአብሔር የሰጠውን ተስፋ ይፈጽም ይሆንን? የሚል ጥያቄ አቀረቡ። ሌሎች ደግሞ ተስፋ መቁረጥ ጀመሩ። ደግሞም የተመለሱት አይሁድ ቁጥር ጥቂት ስለነበረ ብዙ ሕዝብ አልነበረም፡፡ ድርቅና ራብ አከታትሉ ያጠቃቸው ነበር። የእግዚአብሔር ተስፋዎች የታሉ? እግዚአብሔር በተስፋዪቱ ምድር እንደሚባርካቸው አምነው መመለሳቸው ስሕተት ነበርን? በዚህ ሁኔታ ዓመታት እየተቀጠሩ ሲሄዱ ሕዝቡ የበለጠ ተስፋ እየቆረጡና ለመንፈሳዊ ነገሮች ያላቸው ፍላጎት እየቀነሰ ይሄድ ነበር። በመካከሉ እግዚአብሔር ሁለት ነቢያትን ጠራ፡፡ በመጀመሪያ ሐጌ እግዚአብሔር ሕዝቡን ያልባረከው በራስ ወዳድነት ተይዘው የየራሳቸውን ፍላጎት ብቻ ለማሟላት ይጥሩ ስለነበር እንደሆነ ነገራቸው። ንስሐ በመግባትና ቤተ መቅደሱን በመሥራት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ነበረባቸው። ሁለተኛ፥ ከሁለት ወራት በኋላ እግዚአብሔር ዘካርያስ የተባለ ሌላ ነቢይ ጠራ። አይሁድ ቤተ መቅደሱን መሥራት ከጀመሩ አምስት ወር አልፏቸው ነበር። በዚያኑ ወቅት ተንትናይ የተባለና ሌሎች የፋርስ ባለ ሥልጣናት አይሁድ ቤተ መቅደሱን በመሥራታቸው በፋርስ መንግሥት ላይ በእርግጥ ዓምፀው እንደሆነ ለመመርመር መጡ። እነርሱም የመሪዎችን ስም ጻፉና ወደ ዳርዮስ ደብዳቤ ላኩ። አይሁድ የግንባታውን ሥራ የቀጠሉ ቢሆንም ሥራውን መቀጠል የሚችሉት እስከመቼ እንደሆነ በማሰብ ሳይደነቁ አልቀሩም። ከዚህ ቀደም እንደሆነው ጠላታችን ያስቆሙን ይሆን? ብለው መሥጋታቸው አልቀረም። ስለዚህ ተስፋ መቁረጥ ጀመሩ። እግዚአብሔር ዘካርያስን የጠራው እዚህን ተስፋ የቆረጡ ሕዝብ እንዲያገለግል ነበር። አገልግሎቱ የሕዝቡን መንፈሳዊ ሕይወት እንደገና ማደስ ነበር። ዘካርያስ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር የገባውን ቃል ኪዳን በማፍረሳቸው ተጠያቂዎች እንደሆኑ በመንገር ሕዝቡን ያስጠነቅቃቸዋል። ሕዝቡ ንስሐ እንዲገቡና ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ይነግራቸዋል። እግዚአብሔር የሚባርካቸው ይህ ሲሆን ብቻ ነበር። እግዚአብሔር ከእነርሱና ከመሪዎቻቸው ከዘሩባቤልና ከኢያሱ ጋር እንደሆነ የሰጣቸውም ተስፋ እንደሚፈጸም በመናገር ሕዝቡን ያበረታታል። የቤተ መቅደሱ ሥራ ይጠናቀቃል፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን ይጠብቃል፡፡ በመሲሁም መምጣት የእግዚአብሔር ተስፋዎች ይፈጸማሉ፡፡ የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በዚያን ዘመን አይሁድ የነበራቸው ዝንባሌ ዛሬ ብዙ ክርስቲያኖች ካላቸው ዝንባሌ ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ለ) በዘካርያስ ዘመን የእግዚአብሔርን በረከት ለማግኘት የሚያስችሉት ቅድመ-ሁኔታዎች ከዛሬዎቹ ጋር አንድ ዓይነት የሚሆኑት በምን መንገድ ነው? ሐ) እግዚአብሔር ወደፊት ስለሚያደርገው ነገር እኛም እንደ ዘካርያስ በመናገር ክርስቲያኖችን እንዴት ማበረታታት እንችላለን? ዘካርያስ አገልግሎቱን ለብዙ ዓመታት ቀጥሉ ነበር። ዘካርያስ የአይሁድ ሕዝብ መንፈሳዊ ተሐድሶ በተካሄደና ቤተ መቅደሱ እንደገና በተሠራ ጊዜ ታላቅ ድርሻ እንዳበረከተ ከመጽሐፈ ዕዝራ እናነባለን (ዕዝራ 5፡2)። የቤተ መቅደሱ ሥራ በ516 ዓ.ዓ. ሊጠናቀቅ ዘካርያስ ምስክር እንደነበር አንጠራጠርም። አገልግሎቱን በሚጀምርበት ጊዜ ወጣት የነበረ ይመስላል (ዘካርያስ 2፡4)። ስለዚህ አስቴርን እስካገባው ንጉሥ እስከ ቀዳማዊ አርጤክስስ ዘመነ መንግሥት ድረስ ሳይኖር አልቀረም (465-424 ዓ.ዓ.)። የውይይት ጥያቄ፥ ስለ ዘካርያስ ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት አንብብ። በመዝገበ ቃላት ውስጥ የምታገኛቸውን ጠቃሚ ትምህርቶች ዘርዝር፡ (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡) የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡

የትንቢተ ዘካርያስ ታሪካዊ ሥረ-መሠረት Read More »

የትንቢተ ዘካርያስ መግቢያ

ትንቢተ ሐጌ ያተኮረው እግዚአብሔር የሚመለክበትን ቤተ መቅደስ በመሥራት ላይ ነበር። ዳሩ ግን አንድን ሕንጻ ለቤተ መቅደስነት መሥራት ትክክለኛ የሆነ አምልኮ ለመካሄዱ ዋስትና አይደለም። ብሉይ ኪዳን ለእውነተኛ አምልኮ ትክክለኛ የልብ ዝንባሌ አስፈላጊ መሆኑን በተደጋጋሚ ይናገራል (ለምሳሌ፡- 1ኛ ሳሙኤል 15፡22-24፤ መዝሙር (51)፡16-17)። ከነቢዩ ሐጌ በኋላ ሁለት ወር ዘግይቶ አገልግሎቱን የጀመረው ነቢዩ ዘካርያስ ተገቢና ትክክለኛ በሆነ አምልኮ አስፈላጊነት ላይ ያተኩራል። ዘካርያስ ንስሐ እንዲገቡና መንፈሳዊ ተሐድሶ እንዲኖራቸው ለሕዝቡ ጥሪ አደረገ፡፡ የእግዚአብሔር ሕዝብ በንጹሕ ልብና እግዚአብሔርን ለማምለክ በሚፈልግ ዝንባሌ ወደ እግዚአብሔር በሚቀርብበት ጊዜ ከሁሉም የበለጠ ለአምልኮ የሚያስፈልገውን ነገር አሟልተዋል ማለት ነው። አምልኮ የሚፈልገው ሕንጻን ሳይሆን በሚገባ የተዘጋ ልብን ነው፡፡ ስለዚህ ዘካርያስ የቤተ መቅደሱ ሥራ በሚጠናቀቅበት ጊዜ ሕዝቡ እግዚአብሔርን በሚገባ እንዲያመልኩ በቅድሚያ የሕዝቡን ልብ ለማዘጋጀት ጥሯል። የውይይት ጥያቄ፦ ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች ለአምልኮ የሚሆን ትክክለኛ የልብ ዝንባሌ ሳይኖራቸው፥ የአምልኮ ሥርዓትን ብቻ በመፈጸም እግዚአብሔር የማይቀበለውን አምልኮ የሚያቀርቡት እንዴት ነው? ለ) ክርስቲያኖች ራሳቸውን ለትክክለኛና ለእውነተኛ አምልኮ ማዘጋጀት እንዴት ይችላሉ? ሐ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎች አባሎቻቸው በየእሑዱ ለሚያካሄዱት የአምልኮ ፕሮግራም ራሳቸውን እንዲያዘጋጁ ለመርዳት ምን ማድረግ ይችላሉ? የትንቢተ ዘካርያስ ጸሐፊ ዘካርያስ 1፡1 «የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዘካርያስ እንዲህ ሲል መጣ» በሚል ዓረፍተ ነገር ስለሚጀምር ቃሉ የመጣው ወደ ዘካርያስ እንደሆነ እንመለከታለን። ስለዚህ የትንቢተ ዘካርያስ ጸሐፊ ዘካርያስ እንደሆነ ለመገመት እንችላለን። ዘካርያስ ልክ እንደ ኤርምያስና ሕዝቅኤል ነቢይ ብቻ ሳይሆን፥ ካህንም ነበር፡፡ ዘካርያስ የተወለደው ከሌዊ ነገድ ከአሮን የዘር ግንድ ነበር። የተወለደውም በባቢሎን አገር በምርኮ ዘመን ሳይሆን አይቀርም። ሆኖም በ538 ዓ.ዓ. አይሁድ ወደ አገራቸው በተመለሱ ጊዜ ከአያቱ ከዒዶ ጋር አብሮ የተመለሰ ይመስላል። የዘካርያስ አያት ዒዶ ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱት ዐበይት ካህናት ኣንዱ ነበር (ነህ. 12፡4 ተመልከት)። በኋላ ኢያሱ ሊቀ ካህን በነበረ ጊዜ ስለ ዘካርያስ አባት ምንም ነገር ስለማንሰማ እርሱ ሞቶ ዘካርያስ የቤተሰቡን የክህነት ሥራ ተክቶ ሳይሠራ አልቀረም (ነህምያ 12፡16)። የዘካርያስ አባት በራክዩ በመጽሐፈ ዕዝራና ነህምያ ውስጥ ስላልተጠቀሰ ብዙ ሰዎች ዘካርያስ ገና ወጣት ሳለ አባቱ በመሞቱ፥ ያደገው በአያቱ በዒዶ እጅ እንደሆነ ይስማማሉ። ዘካርያስ የነቢይነት አገልግሎቱን የጀመረው ሐጌ ማገልገል ከጀመረ ከሁለት ወራት በኋላ ስለነበር፥ ሁለቱም በኣንድነት አገልግለዋል (ዕዝራ 5፡1፤ 6፡14 ተመልከት)። ይህ ማለት ዘካርያስ አገልግሎቱን የጀመረው በ520 ዓ.ዓ. ነበር ማለት ነው። ይሁን እንጂ የዘካርያስ አገልግሎት ከሐጌ ኣገልግሎት ለበለጠ ጊዜ ቆይቷል። የመጨረሻው ትንቢቱ በ518 የተናገረው ነበር። ዳሩ ግን ዘካርያስ 9-12 የተጻፈው በዘካርያስ ሕይወት መጨረሻ ገደማ ነበር። መጽሐፉ በአጠቃላይ በዘካርያስ ብቻ ወይም በሌሎች ሁለትና ሦስት ሰዎች ስለ መጻፉ ምሁራን ክርክር ይገጥማሉ። ብዙዎቹ ሊቃውንት ዘካርያስ 1-8 የተጻፈው ቤተ መቅደሱ ከመጠናቀቁ በፊት ከ520-518 ዓ.ዓ. በነበረው ጊዜ ውስጥ በዘካርያስ እንደሆነ ይስማማሉ። ክርክሩ የሚካሄደው ከዘካርያስ 9-14 ባለው ክፍል ላይ ነው። አንዳንድ ምሁራን ዘካርያስ 9-11 የተጻፈው ባልታወቀ ሁለተኛ ሰው ሲሆን፥ ዘካርያስ 12-14 ደግሞ በሌላ ሦስተኛ ሰው እንደ ተጻፈ ያምናሉ። ሌሎች ምሁራን ደግሞ ዘካርያስ 9-14 የተጻፈው በሌላ ሁለተኛ ሰው ነው ይላሉ። እነዚህ ምሁራን የዘካርያስ የመጨረሻ ክፍል የተጻፈው ከ300-100 ዓ.ዓ. ነው ይላሉ። አንዳንድ ምሁራን ትንቢተ ዘካርያስን ቢያንስ ሁለት ሰዎች እንደጻፉትና የመጨረሻው ክፍል ዘግይቶ እንደተጻፈ የሚያምኑት ለምንድን ነው? በመጀመሪያ ደረጃ የትንቢተ ዘካርያስ የመጨረሻ ክፍል ከመጀመሪያዎቹ ስምንት ምዕራፎች ጋር ሲወዳደር በአጻጻፍ ስልቱና በሥነ-መለኮት ትምህርቱ ከፍተኛ ልዩነት ማሳየቱ በሌላ ጸሐፊ መጻፉን የሚያመለክት ነው ይላሉ። ሁለተኛ፥ ዘካርያስ “አፖሊፕቲክ” ተብሎ የሚጠራ የሥነ-ጽሑፍ ዓይነት ክፍል እንደሆነ ይናገራሉ። አፖካሊፕቲክ ሥነ-ጽሑፍ በአብዛኛው ስለ መላእክት፥ ስለ ሕልሞችና ራዕዮች ስለፍርዶችና የእግዚአብሔር ልጆች ባልተለመዱ መንገዶች ስለዳኑበት ሁኔታ የሚተርክ ነው። እነዚህ ምሁራን የዚህ ዓይነቱ የአጻጻፍ ስልት የተጀመረው ከ300 ዓ.ዓ. በኋላ ነው ይላሉ። ስለዚህ ዘካርያስ ይኖር ከነበረበት ከብዙ ዓመታት በኋላ በአንድ ሌላ ሰው ተጽፎ በትንቢተ ዘካርያስ ላይ እንደተጨመረ ያስባሉ። ወግ አጥባቂ ከሆኑ ምሁራን ግን ይህንን መጽሐፍ በአጠቃላይ የጻፈው ዘካርያስ ነው ብለው ያምናሉ። የአጻጻፍ ስልት ልዩነት የመኖሩ ምክንያት ዘካርያስ የተለያዩ ዓይነት የአጻጻፍ ስልቶችና ጽሑፎችን መጠቀሙ ነው። ዘካርያስ ቀዳሚዎቹን ስምንት ምዕራፎች የነቢይነት አገልግሎቱን በጀመረበት የመጀመሪያው የወጣትነት ዘመኑ የጻፋቸው ሲሆን፥ የመጨረሻዎቹን አራት ምዕራፎች ደግሞ በሕይወቱ ዘመኑ መጨረሻ ገደማ እግዚአብሔር ወደፊት ስለሚሆነው ነገር ከሰጠው ራእይ በኋላ የጻፋቸው ናቸው ብለው ያስባሉ። መጽሐፉ የተጠቃለለው ከ500-470 ዓ.ዓ. ነው ብለው ያስባሉ። ሁለት ወይም ከሁለት በላይ የሆኑ ጸሐፊዎች እንደ ጻፉት የሚጠቁም ምንም መረጃ ስለሌለ መጽሐፉን በሙሉ የጻፈው ዘካርያስ እንደሆነ መቀበል የተሻለ አማራጭ ነው። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡) የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡

የትንቢተ ዘካርያስ መግቢያ Read More »