የብሉይና አዲስ ኪዳናት ዐበይት ጭብጦች
አንድ የልቦለድ መጽሐፍ ለማንበብ ትፈልጋለህ እንበል። በዚህን ጊዜ የመጽሐፉን የመጀመሪያ ምዕራፍ ብቻ እንዳነበብህ የታሪኩን አጀማመር ልታውቅ ትችላለህ፤ ታሪኩ እንዴት እንደተጠናቀቀ ግን ልታውቅ አትችልም። ከእያንዳንዱ ምዕራፍ አንዳንድ ገጽ ብታነብ ደግሞ ስለ ታሪኩ አጠቃላይ አሳብ ይኖርሃል፤ ነገር ግን በመጽሐፉ ውስጥ የሚገኙትን ክንዋኔዎች በትክክል ልትረዳ አትችልም። ወይም ደግሞ የመጽሐፉን ሁለተኛ ክፍል ብቻ ብታነብ ደግሞ፥ አንዳንድ ነገሮች ለምን በዚያ መንገድ እንደተጻፉ ለማወቅ የተለያዩ ጥያቄዎችን ማንሣት ትጀምራለህ። የውይይት ጥያቄ፦ መጽሐፍ ቅዱስ «የእግዚአብሔር ታሪክ ነው»። ይህ ታሪክ እግዚአብሔር ስለ ራሱ፥ ስለ ሰው ልጆችና በሁለቱ መካከል ስላለው ግንኙነት የተናገረበት እውነተኛ ታሪክ ነው። የሚያሳዝነው ታዲያ የእግዚአብሔርን ታሪክ በአግባቡ የሚያነቡ ብዙ ክርስቲያኖች አለመኖራቸው ነው። መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል እንዲነበብ በሚፈልገው መንገድ በማንበብ ፈንታ፥ እነርሱ የሚወዷቸውን ክፍሎች ብቻ ያነባሉ። ከዚህም የተነሳ ብዙ ክርስቲያኖች እጅግ ጠቃሚ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን ገለል አድርገው ይተዋሉ። ይህም ስለ እግዚአብሔርና ከሰዎችም ጋር ስላለው ግንኙነት ግራ የተጋባ ግንዛቤ ውስጥ እንዲገቡ ያደርጋቸዋል። አዲስ ኪዳን እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር ስለሚያደርገው ግንኙነት መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠን የመጨረሻው መለኮታዊ ትምህርት ነው። መደምደሚያ እንደ መሆኑ መጠን፥ እጅግ አስፈላጊ የሆነ የታሪኩ ክፍል ነው። እግዚአብሔር ከልጆቹ ጋር የሚያደርገውን ግንኙነት ለማወቅ ከፈለግን በአዲስ ኪዳን ውስጥ የሚገኙትን 27 መጻሕፍት በሚገባ መረዳት አለብን። በዚህ ጥናታችን በአዲስ ኪዳን ውስጥ የሚገኙትን ዐበይት ትምህርቶች በሙሉ ለመረዳት እንሞክራለን። በተጨማሪም፥ መንፈስ ቅዱስ ለአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች ሊያስተላልፍ የፈለገውን መልእክት እንዲገልጥልን እየተማጠንን እያንዳንዱን መጽሐፍ አጠር አጠር አድርገን እንመለከታለን። የእግዚአብሔርን ቃል ማጥናት ብቻ ሳይሆን ዛሬ በሕይወታችን ተግባራዊ ማድረግ ስላለብን፥ የአዲስ ኪዳንን እውነቶች ወስደን ከሕይወታችን ጋር ለማዛመድ እንጥራለን። እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ ልባችን ከእርሱ ጋር እንዲዛመድ ሳናደርግ ዝም ብለን ስለ እግዚአብሔር ማጥናቱ ምንም ፋይዳ የለውም። ስለሆነም፥ ቃሉን በምናነብበት ጊዜ ሳሙኤል እንዳለው፥ «ባሪያህ ይሰማልና ተናገር» ልንል ይገባል (1ኛ ሳሙ. 3፡9-10)። ለጥናቱ የሚረዱ መመሪያዎች ቀጥለህ የጥያቄዎቹን መልስ በደብተር ላይ ጻፍ። የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ-ቃላት ከሌለህ ለጥናትህ ስለሚረዳህ መግዛት ይኖርብሃል። አዲሱ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉምና የእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱስ ካሉህ ለጥናትህ ተጠቀምባቸው። የእያንዳንዱን ዕለት ትምህርት በአንድ ቀን ለማጠናቀቅ ሞክር። አንዳንዱ ትምህርት ከሌሎቹ ስለሚረዝም፥ ከሳምንታዊ ስብሰባው በፊት ጥናትህን ለማጠናቀቅ በቂ ጊዜ መመደብ ይኖርብሃል። በትምህርቶቹ ውስጥ አያሌ የማጣቀሻ ምንባቦች አሉ። «አንብብ» ተብሎ የተጻፈባቸውን ጥቅሶች የግድ ማንበብ ይኖርብሃል። እንደዚህ የሚል ማሳሰቢያ የሌለባቸውን ግን ጊዜ ካለህ ብቻ ልታነባቸው ትችላለህ። የመግቢያ ትምህርቶቹ ስለ አዲስ ኪዳን አንዳንድ ጠቃሚ አሳቦችን ያስጨብጡሃል። ምንም እንኳ እነዚህ አሳቦች አዲስና አስቸጋሪ ቢሆኑብህም፥ ለመረዳት ግን የተቻለህን ጥረት አድርግ። ከዚህ ጥናት ዓላማዎች አንዱ ተማሪው አዲስ ኪዳንን ሙሉ በሙሉ እንዲያነብ መርዳት ነው። ስለሆነም፥ ተማሪው እንዲያነብ የተጠየቀውን ክፍል በሙሉ ማንበብ አለበት። ከእያንዳንዱ ጥናቶች ጋር ተያይዘው የቀረቡት ጥያቄዎች ምን ያህል ግንዛቤህን ለመመዘን የቀረቡ በመሆናቸው ጊዜ ሰጥተህ ሥሪያቸው። (ማስታወሻ፦ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የቀረቡት ታሪኮች ሁሉ መንፈሳዊ እውነቶችን ለማብራራት የተዘጋጁ እንጂ፥ እውነተኛ ገጠመኞች አይደሉም።) የብሉይና የአዲስ ኪዳናት ዐበይት ጭብጦች መጽሐፍ ቅዱስ በዓለም ውስጥ ከሚገኙ መጻሕፍት ሁሉ እጅግ ልዩ መጽሐፍ ነው። መጽሐፍ ቅዱስን ጽፎ ለመጨረስ 1500 ዓመታት ፈጅቷል። ከኦሪት ዘዘፍጥረት እስከ ኦሪት ዘዳግም ያሉት የመጀመሪያዎቹ መጻሕፍት የተጻፉት በ1400 ዓ.ዓ አካባቢ ነበር። የመጨረሻው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የዮሐንስ ራእይ የተጻፈው በ100 ዓ.ም አካባቢ ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ የ66 ልዩ ልዩ መጻሕፍት ስብስብ ሲሆን፥ የደራስያኑም ቁጥር ቢያንስ 45 ይሆናል። ከእነዚህ መጻሕፍት መካከል አንዳንዶቹ የታሪክ መጻሕፍት ሲሆኑ፥ ሌሎቹ ደግሞ ግጥሞችን ያካተቱ ናቸው። ለግለሰቦችና ለአብያተ ክርስቲያናት የተጻፉ ደብዳቤዎችም ይገኙባቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ በረጅም ጊዜ ውስጥና በብዙ ደራስያን አማካይነት የተጻፈ በመሆኑ ብዙ የሚጋጩ አሳቦችና ስሕተቶች ይኖሩታል ብለን ልናስብ እንችላለን። ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስን በጥንቃቄ በምናጠናበት ጊዜ በውስጡ የሚገኙ መጻሕፍት ሁሉ የሚያስደንቅ የሃሳብ ስምምነት እንዳላቸው እንገነዘባለን። ምንም እንኳ እግዚአብሔር በሰዎች ተጠቅሞ መጽሐፍ ቅዱስን ቢጽፍም፥ ዋናው የመጽሐፍ ቅዱስ ደራሲ መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ግልጽ ነው (2ኛ ጴጥ. 1፡20-21)። በ1500 ዓመታት ውስጥ በተጻፉት 66 መጻሕፍት መካከል ያለውን ፍጹም ስምምነት ሊያብራራ የሚችለው ይህ መለኮታዊ እውነት ብቻ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በጥሩ ሁኔታ እንደተሠራ የጋቢ ጥለት፥ በውስጡ ከዳር እስከ ዳር እየተጠላለፉ የእግዚአብሔርን ታሪክ የሚያስተሳስሩ ታላላቅ ጭብጦች አሉት። መጽሐፍ ቅዱስን በአግባቡ ለመረዳት እነዚህን ጭብጦች ማወቅ አለብን። የውይይት ጥያቄ፦ ስለ ብሉይና ስለ አዲስ ኪዳን ባለህ ዕውቀት መሠረት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙት እነዚህ ጭብጦች ምን ምን እንደሆኑ ግለጽ። ፩. እግዚአብሔር ሁሉን ነገር የሚቆጣጠር ልዑል ፈጣሪ ነው መጽሐፍ ቅዱስ የሚጀመረው፥ «በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ» በማለት ነው (ዘፍጥ. 1፡1)። የመጽሐፍ ቅዱስ ዐቢይ ጭብጥ፥ የእግዚአብሔር ባሕርይና የዓላማው መገለጥ ነው። እግዚአብሔር የአጽናፈ ዓለሙ (ዩኒቨርስ) ማዕከል፥ ሁሉንም ነገር ወደ ሉዓላዊ ዕቅዱ የሚመራ፥ ሁሉን አዋቂና ሁሉን ቻይ አምላክ ነው። ምንም እንኳ በአጽናፈ ዓለሙ አማካይነት ስለ እግዚአብሔር አንዳንድ ነገሮችን ማወቅ ብንችልም፥ እግዚአብሔር ማን እንደሆነ ትክክለኛውን ማረጋገጫ የምናገኘው ከዘፍጥረት እስከ ራእይ በሚገኙት ቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ነው። እግዚአብሔር ልጁን ወደዚህ ምድር በላከው ጊዜ ራሱን ፍጹም አድርጎ እንደገለጠ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል። ሰዎች ክርስቶስን በሚመለከቱበት ጊዜ እግዚአብሔር አብን በማየት፥ የእግዚአብሔርን ባሕርይ ይበልጥ ፍጹም በሆነ መንገድ ይረዱታል (ዮሐ. 14፡8-11፤ ዕብ. 1፡1-3)። ይህም ሆኖ፥ ብዙዎች ነገሩ አልገባቸውም ነበር። አንዳንድ ጊዜ ሰይጣን እግዚአብሔር እኛን ማገልገል ይገባዋል ብለን እንድናስብ ያደርገናል። ሰው ከምንም ነገር በላይ ትልቅ ትኩረት ሊሰጠው ስለሚገባ፥ እግዚአብሔር ፍላጎታችንን ማሟላት አለበት ብለን እናስባለን። መጽሐፍ ቅዱስ ግን እግዚአብሔር የእውነት ሁሉ ማዕከል እንደሆነና ሰዎች እግዚአብሔርን ማገልገል እንደሚገባቸው በግልጽ ያስተምረናል። እርሱ ፈጣሪ፥ እኛ ደግሞ ፍጥረቱ ነን። ጳውሎስ እንዳለው፥ እኛ የተፈጠርነው እርሱን ለማክበር ነው (1ኛ ቆሮ. 10፡31፤ ኤፌ. 1፡11-12፤ 3፡20-21)። መጽሐፍ ቅዱስ አሁን ያለውን ነገር ሁሉ እግዚአብሔር እንደ ፈጠረና እርሱ ብቻ ያልተፈጠረ አምላክ እንደሆነ ያስረዳል። በዘፍጥረት 1-2 ላይ ስለ መጀመሪያው ፍጥረት እናነባለን። ዘፍጥረት 3 ስለ ሰው ልጅ ዓመፅ ቢገልጽም፥ እግዚአብሔር ግን የፈጠረውን ዓለም ለመቆጣጠር አልተሳነውም። ነገሮችን ከፍና ዝቅ እያደረገ ታሪክን በመቆጣጠር ላይ ይገኛል (ኢሳ. 5፡26፤ 40፡15-17)። እግዚአብሔር የነገሥታትን ልብ ያንቀሳቅሳል (ምሳሌ 21፡1)። እርሱ የታሪክን ፍጻሜ ወስኗል። እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የሚያምፁትን ሁሉ እንዴት እንደሚያንበረክካቸው ከራእይ መጽሐፍ እንመለከታለን። ይህንን ዓለም ከፍጻሜ ካደረሰ በኋላ፥ ፈቃዱ ብቻ የሚከናወንበትን አዲስ ዓለም ፈጥሯል። እግዚአብሔር የሁሉም ተቆጣጣሪና የነገሮችንም ፍጻሜ የወሰነ አምላክ በመሆኑ፥ ወደፊት የሚከሰተውን መለኮታዊ ዕቅድ ልንለውጥ አንችልም። ነገር ግን የዘላለማዊ መንግሥቱ አካል እንሆን ዘንድ ፈቃዳችንን ከፈቃዱ ጋር እንድናስማማ ያሳስበናል። አሁን የምናደርገው ውሳኔ የዘላለም ዕጣ ፈንታችንን ይወስነዋል። የውይይት ጥያቄ፦ ምንም ያህል ሁኔታዎች ክፉ ቢመስሉም እንኳ፥ እግዚአብሔር ሁልጊዜ ነገሮችን እንደሚቆጣጠር ማስታወስ አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው? ፪. እግዚአብሔር ከሰው ጋር ያለው ግንኙነትና የዓለም በኃጢአት መበከል የትም ብንሄድ ዓለም በኃጢአት ተበክላ እናገኛታለን። በየዓመቱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን የሚገድሉ በሽታዎች አሉ። እንደ ድርቅና ጎርፍ የመሳሰሉ የተፈጥሮ አደጋዎችም የእግዚአብሔርን ፍጥረት ሰላም በመንሳት ላይ ናቸው። በአገሮች፥ በሕዝቦችና በጎሳዎች መካከል መከፋፈልና ጦርነት በመቀስቀሱ ምክንያት በሺህ የሚቆጠሩ ወገኖች ሕይወት እየተቀጠፈ ነው። እነዚህ ሁሉ ከየት መጡ? መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሁለተኛው የኃጢአት ጭብጥም ይነግረናል። በዘፍጥረት 3 ላይ እንደተናገረው፥ እነዚህ ሁሉ ችግሮች የተከሰቱት በአዳምና በሔዋን ኃጢአት ምክንያት ነው። ጳውሎስ በሮሜ 5፡12-13 ላይ እንደተናገረው፥ ከአንዱ ሰው ከአዳም የተነሳ ኃጢአትና ሞት በሰዎች ሁሉ ላይ ደረሰ። ይህ በአዳምና በሔዋን የተጀመረው የዓመፀኛነት መንፈስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሁሉ ተንጸባርቋል። የአዳምና የሔዋን ልጆችም የኃጢአትን መንገድ ተከተሉ፤ ከዚያም ቃየን አቤልን ገደለ። ከጥፋት ውኃ በፊት ዓለም ሁሉ በዓመፅ ስለተበላሸች የጥፋት ውኃ ጠርጎ ወሰዳቸው። የተመረጡት
የብሉይና አዲስ ኪዳናት ዐበይት ጭብጦች Read More »
