የዮሐንስ ወንጌል

ኢየሱስ በሽተኞችን መፈወሱና ስለ ሥልጣኑ ከአይሁድ መሪዎች ጋር መከራከሩ (ዮሐ. 4፡43-5፡47)

፩. ሁለተኛው ምልክት፡ ኢየሱስ የሹሙን ልጅ ፈወሰ (ዮሐ 4:43-54) አንዳንድ ጊዜ የፈውስ ስጦታ ያለው ሰው በመካከላችን ከሌለ እግዚአብሔር ሰዎችን የሚፈውስ አይመስለንም። ወይም ደግሞ ታማሚውን ሰው የፈውስ አገልግሎት ወደሚካሄድበት ቤተ ክርስቲያን እንወስዳለን። ልጁ እንዲፈወስለት ወደ ኢየሱስ የመጣው ሹምም እንዲህ ዓይነት አመለካከት ነበረው። ኢየሱስ ወደ ቤቱ መጥቶ ልጁን እንዲዳስስለት ፈለገ። ኢየሱስ ግን የሹሙን ሰው እምነት በአንድ ደረጃ አሳደገለት። ኢየሱስ ወደ ቤቱ መሄድ (መምጣት) እንደማያስፈልገው ነገረው። ሰውየው ማድረግ ያለበት ኢየሱስ የተናገረውን ቃል ማመን ብቻ ነው። ሰውየውም እንዲሁ አደረገ፤ ልጁም ዳነለት። ይህ ሁለተኛው (ምልክት) ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ በመሆኑ ኃይል እንዳለው አሳይቷል። ኢየሱስ መለኮታዊ ፈዋሽ ነው። ነገር ግን እንደ ሌሎች ሰዎች እርሱ ከበሽተኛው አጠገብ የግድ መገኘት አያስፈልገውም። ኢየሱስ ከየትም ስፍራ ሆኖ መፈወስ ይችላል። ይህ ኢየሱስ አሁን በመንግሥተ ሰማይ አለ። ከእኛ ርቆ እንደሚኖር ልናስብና ዳስሰው ሊፈውሱን ወደሚችሉ ሌሎች ሰዎች ለመሄድ እንፈልግ ይሆናል። እንዲህ በማድረጋችን ግን ኢየሱስ ስሰማይ ሆኖ ልክ በአጠገባችን እንዳለ ያህል ሊፈውሰን እንደሚችል እንዘነጋለን። ሹሙ ሰውዬ የነበረውን ዓይነት እምነት ሊኖረን ይገባል። ኢየሱስ ከፈቀደ ከየትኛውም ዓይነት በሽታ ሊፈውሰን እንደሚችል ማመን አለብን። እምነታችንን በሰው (የፈውስ አገልጋይ)፥ በቦታ (የተለየ ቤተ ክርስቲያን)፥ በተለየ ፕሮግራም ወይም ሥርዓት ላይ መመሥረት የለብንም። ኢየሱስ ብቸኛ የመለኮታዊ ፈውስ ምንጭ ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ) ኢየሱስ ሰዎችን ሊፈውስ ያየህባቸውን አጋጣሚዎች ዘርዝር። ለ) በፈውስ ጊዜ በፈዋሹ፥ በስፍራው ወይም በሥርዓቱ ላይ ከፍተኛ አጽንኦት ማድረጉ ትክክል ያልሆነው ለምንድን ነው? ፪. ኢየሱስ አንድ በሽተኛን በቤተ ሳይዳ ፈወሰ (ዮሐ 5፡1-15) ዮሐንስ የጠቀሰው ሦስተኛው ምልክት ለ 38 ዓመት ታሞ የነበረውን (ምናልባትም ሽባ የነበረውን) ሰው ታሪክ ነው። ለጥቂት ጊዜ የታመመን ሰው መፈወስ ቀላል ይመስላል፤ ይሁንና ለረጅም ዘመን የታመመውን እንዲህ ያለውን ሰው ለመፈወስ ከቶ የማይሞከር ነው። ለመሢሑ ለኢየሱስ ግን ለአንድ ሳምንት የታመመን ሰው መፈወስ ቀላል እንደ ሆነ ሁሉ፥ ለ38 ዓመት የታመመውንም ሰው መፈወስ ቀላል ነው። ዮሐንስ እንደገለጸው፥ ኢየሱስ ይህን ተአምር በፈጸመበት ጊዜ የአይሁድ በዓል እየተከበረ ነበር። በዚህ ክፍል የተጠቀሰው በዓል የትኛው በዓል እንደሆነ ሊቃውንት ከስምምነት ላይ አልደረሱም። በዓሉ ምናልባት የአይሁድ ወንዶች ሁሉ ሊያከብሩ ከሚገቧቸው ሦስት በዓላት፥ ማለትም ፋሲካ፥ በዓለ ኀምሳና የመገናኛ ድንኳን እንዱ ሳይሆን አይቀርም። ይህ በዓል የፋሲካ በዓል ከሆነ፥ የክርስቶስ ይፋዊ አገልግሎት ለምን ያህል ጊዜ እንደ ቆየ ለመወሰን ይረዳል። ዮሐንስ ሌሎች ሦስት የፋሲካ በዓሎችን ጠቅሷል (ዮሐ 2፡13፤ 6፡4፤ 11፡55)። ይህ የፋሲካ በዓል ከሆነ፥ የክርስቶስ አገልግሎት የቆየው ከሦስት እስከ አራት ዓመት ያህል ነበር ማለት ነው። በዓሉ ፋሲካ ካልሆነ ግን፥ የክርስቶስ አገልግሎት የቆየው ለሁለትና ሦስት ዓመት ብቻ ነበር ማለት ነው። ዮሐንስ 5፡4 በመጀመሪያው ቅጂ ላይ ስለመኖሩ በሊቃውንት ዘንድ ክርክር አለ። አብዛኞቹ ሊቃውንት የውኃው «መናወጥ» ምን እንደሆነ ለማብራራት ሲባል ከጊዜ በኋላ የተጨመረ አሳብ ነው በሚለው ይስማማሉ። ኢየሱስ የፈጸማቸው አብዛኞቹ ተአምራት የተከናወኑት በበሽተኞቹ ጥያቄ ሲሆን፥ በዚህ ስፍራ ግን ክርስቶስ ያለ ማንም ጥያቄ በሽተኛውን ሲፈውስ እንመለከታለን። ቤተሳይዳ በሚባል የውኃ ኩሬ አካባቢ ሲመላለስ ብዙ ሰዎች ተኝተው አገኛቸው። ክርስቶስ ሁሉንም ለመፈወስ አለመሞከሩ አስደናቂ ነገር ነው። ነገር ግን ለብዙ ዓመት በዚያ ተኝቶ ወደነበረው ሰው ሄደ። ውኃውን እግዚአብሔር በሚያናውጥበት ጊዜ መጀመሪያ የገባ ሰው ይፈወስ ነበር። ይህ ሰው ግን ወደ ውኃው የሚያስገባ ዘመድም ሆነ ጓደኛ አልነበረውም። አንድ ቀን እፈወሳለሁ የሚል ተስፋ ስለነበረው ብቻ ዘመኑን ሁሉ በዚያ ቆየ። በመሢሑ የማመን ምንም ምልክት ሳይታይበት ኢየሱስ ግን ፈወሰው። ይህ ሦስተኛው ምልክት የሚያስተላልፍልን መልእክት ምንድን ነው? በመጀመሪያ፥ ኢየሱስ የትኛውንም ዓይነት በሽታ ለመፈወስ ኃይል እንዳለው ያሳያል። ለኢየሱስ የሚያቅተው ምንም ነገር የለም። ነገር ግን ይህ ሰው ኃጢአተኛነታችንን የሚወክል ምሳሌ ሊሆን ይችላል። ድነት (ደኅንነት) የምናገኘው ከምንወስነው ውሳኔ ወይም ለራሳችን ከምንሰጠው መፍትሔ የተነሣ አይደለም። በመንፈሳዊ ሁኔታችን ክርስቶስ እንደ ፈወሰው ሰው ረዳት የለሾችና ተስፋ ቢሶች ነን። ነገር ግን ሕይወታችን ምንም ያህል ክፉ ቢሆንና ሁኔታችንም ምንም ያህል ምስኪን ሲሆን፥ ክርስቶስ ሲዳስሰን ሕይወታችንን ይለውጠዋል። ከዚህ በኋላ ክርስቶስ ሰውየውን አገኘውና ዳግመኛ ኃጢአት እንዳይሠራ ነገረው። ክርስቶስ የሰውየውን ሥጋዊ ሕይወት ብቻ ሳይሆን መንፈሳዊ ሕይወትም ለመፈወስ ፈልጓል። መንፈሳዊ ፈውስ የሌለው ሥጋዊ ፈውስ ጊዜያዊ መፍትሔ ብቻ ነው። የዘላለም ሞት ከጊዜያዊ የሥጋ በሽታ የከፋ ነው። እንደዚሁም፥ ዘላለማዊ ሕይወት ከሥጋዊ ጤንነት የላቀ ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ስላየኸው አንድ ፈውስ ግለጽ። ለ) አብዛኛውን ክብር የሚወስደው የፈውስ አገልጋዩ ነው ወይስ ክርስቶስ? ሐ) ግለሰቡ ከመፈወሱ በፊትም ሆነ በኋላ የታየው መንፈሳዊ ጉዳይ ምንድን ነው? መ) አብዛኞቹ የፈውስ አገልጋዮች ትኩረት የሚሰጡት ለጊዜያዊ ነው ወይስ ለዘላለማዊ ፈውስ? መልስህን አብራራ። ፫. ክርስቶስ ስለ ሥልጣኑ ከአይሁድ መሪዎች ጋር ተከራከረ ( ዮሐ 5፡16-47) ዮሐንስ በሃይማኖት መሪዎች አስተባባሪነት ኢየሱስን ለመቃወም የተነሡ ሰዎችን «አይሁድ» በማለት ነው የሚጠራቸው። ኢየሱስ በሽተኛውን ሰው ተአምራዊ በሆነ መንገድ በመፈወሱ ደስ ሊሰኙ ሲገባ፥ አይሁዶች የተፈወሰው ሰውዬ በሰንበት ቀን አልጋውን ተሸክሞ በመሄዱ ተቹት። ይህ ሥራ በብሉይ ኪዳን ሕግ ይከለከላሉ ከሚባሉት ነበር። ዮሐንስ እንደሚለው፥ አይሁዶች ኢየሱስን እንዲያሳድዱት ያደረገው የመጀመሪያው ምክንያት በሰንበት ቀን ሰዎችን ማገልገሉ ነበር። ዮሐንስ፥ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ለማሳየት እርሱ የፈጸመውን ተአምር ለመጀመሪያ ጊዜ ጠቅሷል። ክርስቶስ ከአይሁድ መሪዎች ጋር ያደረገው ክርክር የሚከተሉትን ነጥቦች ያጠቃልላል፡- ሀ. እግዚአብሔር በሰንበትም ቀን ሆነ ሁልጊዜም ስለሚሠራ፥ ክርስቶስ በሰንበት ቀን መፈወሱ ስሕተት አልነበረም (ዮሐ 5፡17)። እግዚአብሔር በሰንበት ቀን ሕፃናትን ወደ ዓለም ያመጣል፥ ምግብን ይሰጣል፥ ከክፉ ይጠብቃል፥ ሕይወትን ይሰጣል፥ ሕይወትን ይጠብቃል። እግዚአብሔር ለአንዲት ሰከንድ መሥራቱን ቢያቆም የፈጠረው ዓለም ሁሉ ይናጋል። ኢየሱስ መለኮትና ልዩ የእግዚአብሔር ልጅ ነው። ስለሆነም፥ ሁልጊዜ በሰንበት ቀን ይሠራል። በሰንበትም ቀን መፈወሱ ከሥራዎቹ አንዱ ዓይነት ብቻ ነው። አይሁዶች እግዚአብሔርን «አባቴ» ብለው ለመጥራት አይችሉም። አንዳንድ ጊዜ «አባታችን» ሌላ ጊዜ ደግሞ «በሰማይ ያለህ አባታችን» ይሉ ነበር። ክርስቶስ እግዚአብሔርን «አባቴ» በሚልበት ጊዜ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር እኩል እንዳደረገ ተነዘቡ፤ ይህ ደግሞ ከቶ የማይታሰብ ነበር። ለ. አይሁድ፥ ኢየሱስ «እግዚአብሔር አባቴ ነው» በማለቱ ራሱን «ከእግዚአብሔር ጋር እኩል» እንዳደረገ ተገነዘቡ (ዮሐ 5፡18-30)። ዮሐንስ የአይሁድ መሪዎች ኢየሱስን ለመግደል የፈለጉበት ሁለተኛው ምክንያት ይሄ እንደነበር ገልጾአል። ይህ አሳብ እግዚአብሔርን መሳደብ ነው የሚል አመለካከት ነበራቸው። ክርስቶስ የራሱን መለኮትነት ከመደበቅ ይልቅ ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ልዩ ግንኙነትና የዚህንም ግንኙነት ትርጉም በትክክል አብራራ። ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደመሆኑ፥ በባሕርይም ሆነ በችሎታ ከእግዚአብሔር ጋር እኩል ነው። በሥልጣን ግን ለእግዚአብሔር አብ ይታዘዛል። ስለሆነም፥ የራሱን ሥልጣን ከመጠቀም ይልቅ እግዚአብሔር አብ ያዘዘውን ያደርጋል። እግዚአብሔር አብም ለልዩ ልጁ ካለው ፍቅር የተነሣ ሊያደርግ የሚገባውን ሁሉ አሳይቶታል። እግዚአብሔር አብ ከሚያደርጋቸውና ልጁ እንዲፈጽም ሥልጣን ከሰጣቸው ነገሮች አንዱ፥ ሙታንን ማስነሣት ነው። ዮሐንስ በዚህ ስፍራ ለመግለጽ የፈለጋቸው ሁለት ነገሮች አሉ። በመጀመሪያ፥ ሥጋዊ ሕይወትና የሙታን ትንሣኤ አለ። የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ክርስቶስ አልዓዛርን ከሞት እንዳስነሣው እኛንም ከሞት ያስነሣል (ዮሐ 11)፡፡ ክርስቶስ ሰዎችን ሁሉ ከሥጋዊ ሞት ያስነሣቸዋል። ከዚያም በእርሱ ለማመን ፈቃደኛ ያልሆኑ ሁሉ ይኮነናሉ። በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ ግን የዘላለም ሕይወትን ይቀበላሉ። ሁለተኛ፥ ዮሐንስ ክርስቶስ በእርሱ ለሚያምኑ ሰዎች ስለሚሰጣቸው መንፈሳዊ ሕይወት ይናገራል። ክርስቶስ በኃጢአታቸው ምክንያት በመንፈስ ሙት ለሆኑ ሰዎች መንፈሳዊ ሕይወትን ይሰጣል። ክርስቶስ ስለ ድነት (ደኅንነት) መንገድ የተናገረውን ቃል ሰምተው ክርስቶስን በላከው በእግዚአብሔር አብ የሚያምኑ ሰዎች ከማያምኑ ሰዎች ጋር ወደ ሲኦል አይወርዱም። ሌላው እግዚአብሔር ለልጁ የሰጠው ሥራ በመጨረሻው ቀን በሰዎች ላይ መፍረድ ነው። ሰዎች የሚፈርዱት ውጫዊ ነገርን ለምሳሌ ዘርን፥ ትምህርትን ወይም ሀብትን አይተው ነው፤ ኢየሱስ የሚፈርደው ግን ውስጣዊ ነገርን አይቶ ነው።

ኢየሱስ በሽተኞችን መፈወሱና ስለ ሥልጣኑ ከአይሁድ መሪዎች ጋር መከራከሩ (ዮሐ. 4፡43-5፡47) Read More »

ኢየሱስ ድነትን (ደኅንነትን) ለሳምራዊቷ ሴት አብራራ (ዮሐ. 4፡1-42)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ የጾታ፥ የጎሣና የኢኮኖሚ ደረጃ ላይ በሚገኙ ሰዎች መካከል የምታያቸውን የመናናቅ ሁኔታ ዘርዝር። እነዚህ አሉታዊ የመናናቅ ሁኔታዎች አንዳንድ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚንጸባረቁት እንዴት ነው? ለ) እነዚህ የመናናቅ ሁኔታዎች አንዳንድ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚከሰቱት እንዴት ነው? ሐ) ክርስቶስ በእነዚህ ሁለት የተለያዩ ቡድኖች መካከል ያለው ግንኙነት ምን ዓይነት መልክ እንዲኖረው ነው የሚፈልገው? በማኅበረሰቡ ውስጥ ሥር የሰደደ መናናቅ አብዛኛውን ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን የሚጎዳ መርዝ ነው። ወንዶች ሴቶችን ይንቃሉ። አንዱ ጎሳ ከሌላው እበልጣለሁ ብሎ ያስባል። የተማሩት ያልተማሩትን ይንቃሉ። የከተማ ሰዎች ከገጠር ሰዎች እንሻላለን ብለው ያስባሉ። ነጋዴዎች ወይም ገበሬዎች ደግሞ ከሸክላ ሠሪዎችና ከቀጥቃጮች እንሻላለን ብለው ያስባሉ። መናናቅ ሌላው የትዕቢት ገጽታ ነው፤ እግዚአብሔር ደግሞ ትዕቢትን ይጠላል። (ያዕ. 4፡6፤ 2፡1-7 አንብብ።) አይሁዶች ሌሎች ሕዝቦችን ክፉኛ ይንቃሉ። አሕዛብን እጅግ ስለሚጠሉ እግዚአብሔር ለአሕዛብ ፍቅርም ሆነ ዕቅድ የለውም ብለው ያስቡ ነበር። አሕዛብ ልክ እንደ አረም ተነቅለው መጣል አለባቸው ይሉ ነበር። ግማሽ ጎናቸው አይሁድ ግማሽ ጎናቸው ደግሞ አሕዛብ የነበሩትንና ከይሁዳ በስተ ሰሜን በገሊላና በይሁዳ መካከል ይኖሩ በነበሩት ሳምራውያን ላይ የነበራቸው ጥላቻ የከፋ ነበር። በ722 ዓ.ዓ እስራኤል ወደ አሦር በምርኮ ከሄደችና ከየቦታው ተግዘው የመጡ አሕዛብ በሰማርያ እንዲሰፍሩ ከተደረገ በኋላ፥ በሳምራውያንና በአይሁዳውያን መካክል የከረረ ጠላትነት ሰፍኖ ቆይቷል። በመቃቢያን ዘመን ይህ ጠላትነት እጅግ ከማየሉ የተነሣ፥ አይሁዶች በሺህ የሚቆጠሩ ሳምራውያንን ገድለዋል። ይህ ጥላቻ እጅግ እየከፋ በመምጣቱ ማንኛውም አይሁዳዊ በሰማርያ በኩል አያልፍም ነበር። አይሁዶች ሰማርያን አልፈው ወደ ገሊላ ለመሄድ ተጨማሪ ብዙ ኪሎ ሜትሮችን ለመጓዝ ተገድደዋል። ኢየሱስ ይጠላው የነበረ ሌላም መናናቅ ነበር። ይህም በወንዶችና በሴቶች መካከል የነበረው መናናቅ ነው። ከአይሁድ ወገን የሆኑ ወንዶች ብዙውን ጊዜ፥ «እግዚአብሔር ሆይ፥ ሴት አድርገህ ስላልፈጠርኸኝ አመሰግንሃለሁ» በማለት ይጸልዩ ነበር። ነገር ግን ኢየሱስ ለሴቶች የነበረው አመለካከት በዚያን ዘመን ከነበሩት አይሁዳዊ ወንዶችና ዛሬም በብዙ አብያተ ክርስቲያናት ከሚገኙ ምእመናን የተለየ ነበር። ኢየሱስ የመናናቅ ሕይወትን አውግዟል። እግዚአብሔር ሰዎችን ሁሉ እንደሚወድ ለደቀ መዛሙርቱ አስተምሯል። በኢየሱስና በሳምራዊቷ ሴት ታሪክ ውስጥ የኢየሱስን ልብ በግልጽ ማየት ይቻላል፤ ኢየሱስ የጥላቻን ግድግዳ አፍርሶ አንዲት የተናቀች ሴት በእርሱ እንድታምን አደረገ። ይህ የክርስቶስና የሳምራዊቷ ሴት ታሪክ፥ ለሰዎች እንዴት መመስከር እንደምንችል የሚያሳይ ግሩም ምሳሌ ነው። ከዚህ ታሪክ ብዙ እውነቶችን መማር ቢቻልም፤ ከዚህ በታች ስድስት ዐበይት እውነቶች ቀርበዋል፡- ኢየሱስ ከሌሎች ጋር ለመወዳደር አልፈለገም። የእርሱ እውቅና ማግኘት ከመጥምቁ ዮሐንስ ጋር የውድድር መንፈስ እንዳስከተለ ሲያውቅ፥ ይሁዳን ትቶ ወደ ገሊላ ተመለሰ። ከሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ወይም ቤተ እምነቶች ጋር ለመወዳደር (ለመፎካከር) እንዳልተጠራን ሁልጊዜ ልብ ማለት ይኖርብናል። በኢየሱስ የሚያምኑ ሁሉ እውነተኛ መንፈሳዊ ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን ናቸው። ስለሆነም፥ ልንወዳቸውና ልንቀበላቸው ይገባል። እግዚአብሔር ሌላውን ግለሰብ ወይም ቤተ ክርስቲያን ከእኛ በላይ ቢጠቀም፥ ከእነርሱ ጋር ከመፎካከር ይልቅ በእግዚአብሔር መንግሥት መስፋፋት ደስ ልንሰኝ ይገባል። ኢየሱስ በሰማርያ በኩል ማለፍ ነበረበት። በዚያን ዘመን አንድ ሰው ከይሁዳ ወደ ሰማርያ ለመሄድ የሚያስችሉት ሦስት ሁኔታዎች ነበሩ። ከእነዚህ ሁሉ ቀጥተኛው በሰማርያ በኩል ማለፍ ነው፤ ይሁን እንጂ አይሁዶች ሳምራውያንን በብርቱ ስለሚጠሏቸው ይህን መንገድ እምብዛም አይጠቀሙም ነበር። ወይም ደግሞ ከሰማርያ በስተ ምዕራብ በኩል ከተጓዙ በኋላ ወደ ገሊላ መመለስም ይቻል ነበር። ሦስተኛው መንገድ ደግሞ የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግረው ከሰማርያ በስተ ምሥራቅ ከሄዱ በኋላ እንደገና የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግረው ወደ ገሊላ መመለስም ይቻላል። ብዙውን ጊዜ አይሁዶች በቀጥታ በሰማርያ በኩል ከማለፍ ይልቅ ሁለተኛውንና ሦስተኛውን መንገድ ይመርጡ ነበር። እንግዲህ ኢየሱስ በሰማርያ በኩል ለማለፍ የተገደደው መንገዱ ይሄ ብቻ ስለሆነ ሳይሆን፥ እግዚአብሔር ሳምራዊቷን ሴት እንዲያገኝ ስለነገረው ነው። ኢየሱስ ከሳምራዊቷ ሴት ጋር በተነጋገረበት ጊዜ ሁለት የምስክርነት መርሖዎችን ተጠቅሟል። አንደኛው፥ ንግግሩን የጀመረው ሴቲቱ ከምትፈልገው ነገር በመነሣት ነበር። ሴቲቱ ውኃ መቅዳት ሰልችቷት ነበር፤ እርሱ ግን መንፈሳዊ ውኃ አቀረበላት። ሁለተኛው፥ ከምታውቀው ተነሥቶ ወደማታውቀው ወሰዳት። የውኃ ጥማቷን መንፈሳዊ ጥማቷን ለመግለጽ ተጠቀመበት። አንዲት ሴት ውኃ ለመቅዳት እኩለ ቀን ላይ መሄድ እንግዳ ነገር ነው ምክንያቱም ይህ ሰዓት ሙቀቱ እጅግ የሚበረታበት ሰዓት ስለሆነ ነው። ሌቶች ውኃ ለመቅዳት የሚሄዱት ጠዋት ወይም ማታ ነው። ነገር ግን ይህች ሳምራዊት ሴት በማኅበረሰቡ የተጠላችና ሌሎችም ሰዎች የሚያውቋት ዘማዊ በመሆኗ ማንም ሰው በሌለበት ሰዓት ውኃ ለመቅዳት ወረደች። ምናልባትም ስላሳለፈችው ሕይወት ነፍስና ሥጋዋን የሚለያይ ሐሜት ሰምታ ይሆናል። በውኃው ጉድጓድ አካባቢ የሚሰበሰቡ ሌሎች ሴቶች አግልለዋትም ሊሆን ይችላል። ኢየሱስ ለዚህች ሴት ስለ ወንጌል ሊነግራት አስቦ፤ ንግግሩንም ጥያቄ በማንሣት ጀመረ። ይህ በአይሁዳውያን ዘንድ እጅግ እንግዳ ተግባር ነበር። በተለይም አንድ አይሁዳዊ ወንድ አንዲትን ሴት ይህን አድርጊልኝ ሊላት አይችልም። ኢየሱስ ይህን ጊዜ የተጠቀመው እርሱ ብቻ ሊሰጣት ስለሚችለው «ሕያው ውኃ» ማለትም ዘላለማዊ ሕይወት ሊነግራት ነው። (ማስታወሻ፡- በአይሁድ አፈ-ታሪክ መሠረት መሢሑ በመጣ ጊዜ ይሰጠናል ብለው ከሚያስቡት ነገሮች መካከል አንዱ ሙሴ እስራኤላውያን በምድረ በዳ በነበሩ ጊዜ ከዓለት ውኃ እንዳፈለቀላቸው ሁሉ መሢሑም የማያቋርጥ ውኃ እንደሚሰጣቸው ነበር።) ሴቲቱ ኢየሱስ የሚናገረው ስለ ምድራዊ ውኃ መሰላት። ስለዚህ ሊሰጣት ያሰበው ውኃ የዘላለምን ሕይወት ውኃ እንደሆነ አብራራላት። ነገር ግን ለሰው ኢየሱስ የሚሰጠውን በረከት ብቻ ማወቅ በቂ አይደለም፤ እያንዳንዱ ሰው በኃጢአቱ መገሠጽ አለበት። ስለሆነም ኢየሱስ አምስት ባሎችን ያገባችና በወቅቱ ባሏ ካልሆነ ሰው ጋር የምትኖር ኃጢአተኛ መሆኗን ገለጸላት። ክርስቶስ ይህን ያደረገው የእግዚአብሔር ጸጋ እንደሚያስፈልጋት ለማመልከት ነበር። በሕይወታችን ውስጥ ያለውን ኃጢአት ለመቀበል እጅግ አስቸጋሪ ነው። የምንመሰክርላቸው ስዎችም ሆኑ እኛ አብዛኛውን ጊዜ ርእሰ ጉዳዩን ወደ ሌላ አቅጣጫ ለማዞር እንጥራለን። ስለዚህ ሴቲቱ ትክክለኛው የአምልኮ ስፍራ ሳምራውያኑ የሚያመልኩበት የገሪዛን ተራራ ነው ወይስ አይሁዳውያኑ የሚያመልኩባት ኢየሩሳሌም ስትል አንድ ነገረ መለኮታዊ ጥያቄ አነሣች። ኢየሱስ ግን ውይይቱ ወደ ሌላ አቅጣጫ እንዳያመራ አደረገ። ይልቁንም፥ ወደ አምልኮ ዋነኛ አሳብ በማምራት የሚከተለውን አስተማራት። ሀ. አምልኮ በእውነት ላይ መመሥረት አለበት። ይህ እውነት በሁለት መንገዶች ተመልክቷል። አንደኛው፥ በእግዚአብሔር ቃል ላይ ከተመሠረተ አምልኮ የሚመጣ እውነት አለ። ክርስቶስ የአይሁዶች አምልኮ የተመሠረተው በብሉይ ኪዳን ላይ በመሆኑ፥ የትክክለኛ አምልኮ ምንጭ እንደሆነ ገልጾላታል። መሢሑ ከመጣ በኋላ ግን ዐቢዩ ጥያቄ የሰዎች ልብ እንጂ  የአምልኮ ስፍራ አይደለም። ሁለተኛው፥ እውነት ከምናምነውና የእግዚአብሔርም ቃል ከሚናገረው እንጻር የምንኖረውን ሕይወት ያመለክታል። ብዙ ክርስቲያኖች ክርስቶስ ብቸኛ የድነት (የደኅንነት) መንገድ እንደሆነ ይናገራሉ። ይሁንና ወደ ጠንቋዮች ይሄዳሉ፤ መልካም ሥራ በመሥራት ወደ መንግሥተ ሰማይ ለመግባት ይጥራሉ፤ ወይም ደግሞ በክርስቲያን ቤተሰብ ውስጥ በመወለዳቸው ድነትን (ደኅንነትን) እንደሚያገኙ ይናገራሉ። አንዳንድ ሰዎች የክርስቶስ ተከታይ እንደ ሆኑ ይናገራሉ። ይሁንና በቤት ወይም ከቤተ ክርስቲያን ውጭ የሚያደርጉት ነገር ከእግዚአብሔር ቃል ጋር አይስማማም። የብዙ ክርስቲያኖች ሕይወት በመንፈሳዊ ግብዝነት የተሞላ ነው። ስለዚህ ክርስትናቸው ከልብ በሆነ እውነት ላይ የተመሠረተ አይደለም። በእውነት ማምለክ የግብዝነት ተቃራኒ ነው፤ ግብዝነት መንፈሳዊነታችንን ለማሳየት የምንጣጣርበት መንገድ ነው። ለ. አምልኮ በመንፈስ ላይ መመሥረት አለበት። ይህም ሁለት መሠረታዊ አሳቦችን ይዟል። አንደኛው፥ አምልኮ በመንፈስ ቅዱስ ላይ መመሥረት አለበት። መንፈስ ቅዱስ ወደ ግለሰቡ ልብ ውስጥ መንፈሳዊ ሕይወትን ከማምጣቱም በላይ ግለሰቡ እግዚአብሔርን እንዲያመልክ ያነሣሣዋል። እግዚአብሔርን በንጽሕና ልናመልክ የምንችለው መንፈስ ቅዱስ ልባችንን በሚያንቀሳቅስበት ጊዜ ብቻ ነው። ሁለተኛው፥ አምልኮ በመንፈስ ከተዘጋጀ ልብ መፍለቅ አለበት። ዳግም መወለዱ ብቻ ሳይሆን፥ የምንዘምራቸው መዝሙሮች፥ የምንጸልያቸው ጸሎቶችና የምንሰማቸው ስብከቶች ሁሉ፥ አክብሮታችንንና ፍቅራችንን ለእግዚአብሔር ለመግለጽ ከሚሻ ልብ ሊመነጩ ይገባል። አምልኮ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንመጣ ብቻ የሚፈጸም ተግባር ሊሆን አይገባም። ነገር ግን ሳምንቱን ሁሉ የምንመላለስበት የታዛዥነትና የፍቅር ሕይወት ሊሆን ይገባል። አምልኮ ሁለት ነገርችን ያካትታል። አምልኮ በልማድ ወይም በስሜት ላይ መመሥረት የለበትም። ነገር ግን

ኢየሱስ ድነትን (ደኅንነትን) ለሳምራዊቷ ሴት አብራራ (ዮሐ. 4፡1-42) Read More »

መጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርቱን ወደ ኢየሱስ አመለከታቸው (ዮሐ. 3፡22-36)

ራስ ወዳድነት የምእመናን ብቻ ሳይሆን የመሪዎችም ሁሉ ትልቁ ችግር ነው። ሕይወታችንን የገዛው ራስ ወዳድነት ካልተወገደ በቀር ኢየሱስ የሚፈልገውን ዓይነት አመራር ተግባራዊ ልናደርግ አንችልም። ይህ ራስ ወዳድነት የተለያዩ ገጽታዎች አሉት። አንደኛው፥ አንድ መሪ የግል ጥቅሙን (ገንዘብ፥ ክብር) በሚፈልግበት ጊዜ፥ ራስ ወዳድነት ግላዊ ሊሆን ይችላል። ሁለተኛው፥ አንድ መሪ ከጠቅላላው የእግዚአብሔር ቤተሰብ ይልቅ የራሱን ቤተሰብ ወይም ጎሳ ለመጥቀም በሚፈልግበት ጊዜ፥ ራስ ወዳድነት ቤተሰባዊ ገጽታ ይይዛል። ሦስተኛው፥ እግዚአብሔር አንድን ሰው በሚባርክበት ጊዜ መሪው ኃይልን፥ ሥልጣንንና ክብርን በመሻት የቅንዓት ስሜት ሊያድርበት ይችላል። እነዚህ ሦስቱም ለቤተ ክርስቲያን መሪ አደገኛ መርዞች ናቸው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህ ሦስት የራስ ወዳድነት ምሳሌዎች ቤተ ክርስቲያንን ሲያቆስሉ ያየህባቸውን እጋጣሚዎች ግለጽ። ለ) ለትክክለኛ መንፈሳዊ አመራር የሚበጀው አመለካከት የትኛው ነው? በቅንዓትና በራስ ወዳድነት መንፈስ ሳይያዙ እንዴት ትክክለኛ አመራር መስጠት እንደሚቻል ለመገንዘብም ሆነ ለመማር መጥምቁ ዮሐንስ ጥሩ ምሳሌ ነው። መጥምቁ ዮሐንስ የኢየሱስ ዘመድ ነበር። ከኢየሱስ በዕድሜ የሚበልጥ ከመሆኑም በላይ አገልግሎቱንም የጀመረው ከእርሱ ቀድሞ ነው። ስለሆነም እንደ አይሁዶች ልማድና እንደ እኛም ግምት፥ ዮሐንስ ከኢየሱስ የበለጠ ክብር ይገባው ነበር። የመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርት፥ ኢየሱስ ከእርሱ የበለጡ ተከታዮችን እያፈራና አብዛኞቹም ደቀ መዛሙርት ኢየሱስን እየተከተሉ መሆኑን ሲነግሩት፥ በቅንዓት ተይዞ የኢየሱስን አገልግሎት ለማደናቀፍ መሞከር ይችል ነበር። ዮሐንስ ግን ነገሮችን የሚመራው እርሱ ሳይሆን እግዚአብሔር እንደሆነ ተገንዝቦ ነበር። ስለሆነም እግዚአብሔር እስከ ከበረ ድረስ በቅንዓትና በራስ ወዳድነት መንፈስ ከመነሣት ይልቅ ሌሎችን በአገልግሎታቸው ለማበረታታት ችሏል። መጥምቁ ዮሐንስ ስለ ራሱና ስለ ኢየሱስ የተገነዘባቸውን ነገሮች አስተውል። ሀ. እግዚአብሔር የነገሮች ሁሉ ምንጭ ነው። አንድ ሰው በቤተ ክርስቲያን ላለው ሥልጣን መንፈሳዊ ስጦታ፥ ተወዳጅነት፥ ስኬት ሁሉ ምንጩ እግዚአብሔር ነው። ሁሉም የሚመጣው «ከሰማይ» ነው። ለ. መጥምቁ ዮሐንስ በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ ያለውን ስፍራ ያውቅ ነበር። ዮሐንስ “የሙሽራው ወዳጅ” እንደመሆኑ መጠን፣ የሙሽራው ማለትም የኢየሱስ ስኬት ተካፋይ መሆን እንዳለበት ያምን ነበር። ደስታው ኢየሱስ ሲከብርና እግዚአብሔርም የሰጠውን ተግባር ሲፈጽም ማየት ነበር። ምንም እንኳ የዮሐንስ አገልግሎት እያበቃና ተከታዮቹም እየቀነሱ ቢመጡም፥ ይህ ግን ለእርሱ ምኑም አልነበረም። ራሱ ዮሐንስ እንደተናገረው «እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ይገባኛልና» ብሏል። መጥምቁ ዮሐንስ ኢየሱስ የመሢህነቱን ተግባር ሲያከናውን በመመልከቱ በደስታ ተሞልቷል። አንድ መሪ ሌላው ከእርሱ የበለጠ ሲወደድና ፍሬያማ ሲሆን ሲያይ ደስ ሊሰኝ የሚችለው ብስለት ሲኖረው ነው። አንድ መሪ ይህን ለማድረግ የሚችለው ለእርሱም ሆነ ለሌላው መሪ አገልግሎትንና ፍሬን የሚሰጥ እግዚአብሔር እንደሆነ ሲያስብ ብቻ ነው። ሁለቱም የሙሽራው , ወዳጆች በመሆናቸው በራሳቸው ሳይሆን በክርስቶስ ክብር ደስ ሊሰኙ ይገባል። የመንፈሳዊ መሪ ትልቁ ምኞት እርሱ ሳይሆን እግዚአብሔር ከብሮ ማየት ነው። እግዚአብሔር በወጣትና ይበልጥ ተወዳጅ በሆነ መሪ ሊተካው ሲፈልግ እንኳ፥ ይህንን መቀበል አለበት። ከሁሉም የሚልቀው የቤተ ክርስቲያን ዕድገትና የክርስቶስ መክበር ነውና። ሐ. ኢየሱስ ክርስቶስ «ከላይ» ማለትም ከሰማይ ነው። እርሱ አምላክ ነው፤ ዮሐንስ ግን «ከምድር» ነው። በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ፥ ክርስቶስ ከሌላው ሰው መላቅና መከበር አለበት። አንድ መሪ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች በመፈወሱ ምክንያት ሰዎች ከኢየሱስ ይልቅ እርሱን የሚመለከቱ ከሆነ ችግር አለ ማለት ነው። አንድ መሪ ፍሬያማ ነው የሚባለው፥ ሰዎች ክርስቶስን እንዲመለከቱ ሲያደርግ ነው። የጀማ ስብከት የሚያካሂዱ ታዋቂ መሪዎችንና የፈውስ አገልጋዮችን ከምንመረምርበት መንገድ ውስጥ አንዱ፥ «እየከበረ ያለው ማን ነው? አገልጋዩ ነው ወይስ ክርስቶስ? ይበልጥ ታዋቂነትን እያገኘ ያለው ማን ነው?» ብለን በመጠየቅ ነው። መ. እውነትን በትክክል መናገር የሚችለው ኢየሱስ ብቻ ነው፤ ምከንያቱም እግዚአብሔርን ያየም ሆነ የመንግሥተ ሰማይን እውነቶች ሁሉ የሚያውቅ እርሱ ክርስቶስ ነው። የኢየሱስ ቃል የእግዚአብሔር ቃል በመሆኑ ልንታዘዘው ይገባል። እግዚአብሔር ለማንም የሰው ልጅ ያልሰጠውን መንፈስ ቅዱስን በምልአት ለክርስቶስ ሰጥቶታል። እግዚአብሔር ክርስቶስን ስለሚወደው በምድር ላይ ሥልጣንን ሰጥቶታል። ሠ. የሰው ልጆች ምርጫ ቀርቦላቸዋል። መጥምቁ ዮሐንስን ተቀበሉም አልተቀበሉም ይሄን ያህል ወሳኝ አይደለም፤ ነገር ግን ክርስቶስን ይቀበሉት ይሆን? ኢየሱስ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ፥ ኢየሱስ ስለ ራሱ የሰጠውን ምስክርነት የተቀበሉ ጥቂቶች ናቸው። ይሁን እንጂ በታሪክ ሁሉ ውስጥ ከኢየሱስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ኢየሱስን በተመለከተ ትልቅ ልዩነት (መከፋፈል) ሆኖአል። ኢየሱስን የድነታቸው (የደኅንነታቸው) ምንጭ አድርገው ያልተቀበሉ ሰዎች፥ የእግዚአብሔርን ቁጣና ዘላለማዊ ቅጣት ይቀበላሉ። ነገር ግን ኢየሱስን የድነታቸው (የደኅንነታቸው) ምንጭ አድርገው የተቀበሉ ሰዎች፥ እግዚአብሔር ለዘላለም ለልጆቹ የሚሰጠውን ልዩ ሕይወት ያገኛሉ። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ዮሐንስ ስለ ራሱ አገልግሎት የነበረውን ግንዛቤና የድነትን (የደኅንነትን) ግልጽ መልእክት አብራራ። ለ) እንደ መሪዎች ይህን አሳብ መረዳታችንና እግዚአብሔር ለሌሎች እንድናካፍል የሚፈልገውን መልእክት በትክክል መረዳታችን የሚጠቅመን እንዴት ነው? ሐ) ከመጥምቁ ዮሐንስ አገልግሎት ለሕይወትህና በቤተ ክርስቲያንህ ላለህ አገልግሎት ልትጠቀምባቸው የምትችላቸውን ነገሮች ዝርዝር። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

መጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርቱን ወደ ኢየሱስ አመለከታቸው (ዮሐ. 3፡22-36) Read More »

ኢየሱስ አዲስ ልደት ምን እንደሆነ ለኒቆዲሞስ ገለጸለት (ዮሐ. 3፡1-21)

በወንጌላት ውስጥ ፈሪሳውያን በቡድን ሆነው ኢየሱስንና አገልግሎቱን እንደ ተቃወሙ በሰፊው ተጠቅሷል። ኢየሱስ የመጣው እነርሱ ከጠበቁት በተለየ መንገድ ስለነበረ፥ የሃይማኖት መሪዎቹ መሲሕ መሆኑን ሊቀበሉ አልቻሉም፡፡ ደግሞም ኢየሱስ ሃይማኖታዊ ሕጎቻቸውን ባለመከተሉ፥ መንፈሳዊነቱንም ሊገነዘቡ ተስኖአቸው ነበር። ነገር ግን ኢየሱስ ከሃይማኖታዊነታቸው ባሻገር፥ ወደ ልባቸው ዘልቆ በመመልከት፥ በግብዝነታቸው ገስጾአቸዋል። ይህ በኢየሱስና በፈሪሳውያን መካከል የነበረው ግንኙነት ፍጥጫና ውጥረት የበዛበት ነበር። ይህም ሆኖ፥ ከፈሪሳውያኑ አንዱ ጥልቅ መንፈሳዊ ራብ ነበረው። ኢየሱስ የፋሲካን በዓል ለማክበር ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ ሳለ፥ ኒቆዲሞስ የሚባል ፈሪሳዊ መንፈሳዊ ጥያቄዎችን ይዞ ወደ እርሱ ቀረበ። ኒቆዲሞስ በጨለማ የመጣው ምናልባት ኢየሱስን ለብቻው የሚያገኝበት ሰዓት በዚያን ጊዜ ብቻ በመሆኑ ነበር። ወይም ደግሞ ሌሎች ከኢየሱስ ጋር ለመነጋገር መሄዱን እንዳያውቁበት አስቦ ይሆናል። ኢየሱስ ከኒቆዲሞስ ጋር ባደረገው ንግግር፥ መንፈሳዊነት ምን ማለት እንደሆነ በሚገባ አስረድቶታል። ኒቆዲሞስ ከእግዚአብሔር ጋር የሚደረግ ግንኙነት የተመሠረተው፡- አይሁድ ሆኖ በመወለድ የብሉይ ኪዳን ሕግጋትን በመጠበቅና የአይሁዶችን ሃይማኖታዊ ትእዛዛት በመከተል እንደሆነ ያስብ ነበር። ኢየሱስ ግን ኒቆዲሞስ የወንጌልን ዋና ሃሳብ እንዲገነዘብ ለማድረግ እጅግ እንግዳ አገላለጾችን ተጠቅሟል። አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት ለማድረግ እነዚህ ሦስት ነገሮች ከቶ እንደማያስችሉት ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ ገለጸለት። ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ ግንኙነት ለማድረግ የሚፈልግ ሰው፥ የግድ «ዳግም መወለድ» እንዳለበት አብራራለት። የግሪኩ ቃል «ከላይ መወለድ» የሚል ፍች አለው። ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ለማድረግ ወይም ድነትን (ደኅንነትን) ለማግኘትና ለመግለጽ በአዲስ ኪዳን ገብተው የምናገኛቸው ቁልፍ ቃሎች የተነገሩት፥ በኢየሱስ ነው። እስቲ የሚከተሉትን እውነቶች በጥሞና ተመልከት። ሀ. ድነትን (ደኅንነትን) ለማግኘት ወይም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት፥ አንድ ሰው ከውኃና ከመንፈስ መወለድ አለበት። ውኃው ምንድን ነው? ለዚህ ጥያቄ ሁለት ምላሾች ተሰጥተዋል። አንደኛው፥ በውኃ ስለ መጠመቅ የሚናገር ሊሆን ይችላል። ከመጥምቁ ዮሐንስ፥ ከኢየሱስና ከሐዋርያት ዘመን ጀምሮ፥ በኢየሱስ ያመነ ሰው ወዲያውኑ በውኃ እንዲጠመቅ ይደረጋል። ይህም የቀድሞዎቹ ክርስቲያኖች አብዛኛውን ጊዜ እምነትንና ጥምቀትን እንደ አንድ ተግባር አድርገው ይመለከቱ እንደ ነበር ያሳያል። ስለዚህ ውኃው አንድ ሰው ድነትን (ደኅንነትን) ባገኘ ጊዜ የሚፈጽመውን ንስሐ፥ እምነትና ጥምቀት የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ሁለተኛው፥ ቃሉ ይበልጥ የሚያመለክተው ሥጋዊ ልደትን ሊሆን ይችላል። አንድ ሕፃን በእናቱ ማኅፀን ውስጥ ሳለ በውኃ ተከብቦ ይኖራል። ሕፃኑ በሚወለድበት ጊዜ በመጀመሪያ ውኃው ከዚያም ሕፃኑ ይወለዳል። ስለሆነም፥ ኢየሱስ ይህን ምሳሌ ያመጣው አንድ ሰው መጀመሪያ በሥጋ እንደሚወለድና ከዚያም ከመንፈስ ቅዱስ ዳግም እንደሚወለድ ለመግለጽ ነው። ከመንፈስ መወለድ ምንድን ነው? ይህ በኢየሱስ ክርስቶስ ባመንን ጊዜ በልባችን ውስጥ የሚፈጸም መንፈሳዊ ልደት ነው። ጳውሎስ በክርስቶስ ከማመናችን በፊት ሙታን እንደነበርን ገልጾአል። (ኤፌ 2፡1-5 አንብብ።) ስለሆነም በሥጋዊ ልደት አማካይነት፥ የምድራዊው ቤተሰብ አባል በመሆን የምድር ሕይወታችንን እንደምንጀምር ሁሉ፥ በመንፈሳዊ ልደት ወደ እግዚአብሔር ቤተሰብ በመቀላቀል መንፈሳዊ ሕይወታችንን እንጀምራለን። ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት ሥጋዊም ሆነ መንፈሳዊ ልደት አስፈላጊዎች ናቸው። ለ. መንፈሳዊ ልደት በዓይን አይታይም። የሚታየው የተለወጠው ሕይወታችን ብቻ ነው። ከእግዚአብሔር በቀር መንፈሳዊ ልደት የሚፈጸምበትን ቀን የሚያውቅ ማንም የለም። ኢየሱስ ይህንን እውነታ ያነጻጸረው በዓይን ከማይታይ ነፋስ ጋር ነው። ይሁንና ነፋስ ፊታችንን ሲገርፍ ወይም የዛፍ ቅጠሎችን ሲያወዛውዝ ህልውናውን እንደምናስተውል ሁሉ፥ የመንፈሳዊ ልደትንም መኖር የምናውቀው የአንድን ሰው ሕይወት ሲለውጥ ነው። ጳውሎስ ይህንን አዲስ ልደት «አዲስ ፍጥረት» ይለዋል (1ኛ ቆሮ. 5፡17)። ሐ. ኢየሱስ የመንፈሳዊ ልደት ማዕከል ነው። ምክንያቱም እርሱ የመጣው ከሰማይ ነው። በብሉይ ኪዳን እንደተሰቀለው የነሐስ እባብ (ዘኁ. 21፡4-9 አንብብ) እርሱም ይሰቀላል ይላል። ያንን የተሰቀለ የነሐስ እባብ የተመለከቱ ሰዎች እንደተፈወሱ ሁሉ፥ ኢየሱስም በመስቀል ላይ ይሰቀላል፤ ለሰዎችም ሁሉ ፈውስ ይሆናል። መ. ድነት (ደኅንነት) በራሱ የሚሆን ነገር ሳይሆን የሰዎችን ስሜትና አቀባበል የሚሻ ነው። ለመዳን የሚፈልጉ ሰዎች በኢየሱስ ማመን አለባቸው። ማመን ያለባቸው ምንድን ነው? ኢየሱስ ኃጢአታቸውን በመስቀል ላይ እንደ ተሸከመ ማመን አለባቸው። ምክንያቱም በእነርሱ ምትክ ሞቷል። ስለዚህ ከእነርሱ የሚጠበቀው በምትካቸው የሞተውን ኢየሱስ ማመን ብቻ ነው። ድነትን (ደኅንነትን) ለማግኘት የተለየ የመዳኛ ሥራ መሥራት አይጠበቅባቸውም። ይህን ጊዜ ሰው ክርስቲያን ሆኖ ይወለዳል የሚለው የተሳሳተ አመለካከታቸው ይወገዳል። የድነት (የደኅንነት) ተስፋቸው ሁሉ የሚያርፈው ኢየሱስ በመስቀል ላይ የፈጸመላቸውን ሥራ በማመን ብቻ ይሆናል። ሠ. የድነት (የደኅንነት) ወይም በኢየሱስ አነጋገር የዘላለም ሕይወት ምንጩ እግዚአብሔር ነው። እንዲወለድና እንዲሞት ኢየሱስን ወደዚህ ዓለም የላከው እግዚአብሔር አብ ነው። የላከውም ፍርድንና መንፈሳዊ ኩነኔ እንዲያመጣ አይደለም። ይልቁንም ኢየሱስን ወደ ዓለም የላከው፥ ለሰዎች ካለው ፍቅሩ የተነሣ ነው። ልጆቹ እንድንሆንና እንድንድን ስለወደደ ይህን አደረገ፡፡ በኋላ እንደምንመለከተው፥ የሚያምኑትን ሁሉ መርጦ ለኢየሱስ የሚሰጠው አብ ነው (ዮሐ 6፡35-40፤ 15፡16)። ረ. የአንድ ሰው ውሳኔ ዘላለማዊ ውጤት አለው። ሰዎች የእግዚአብሔርን ስጦታ ከናቁ በዘላለም ኩነኔ ሥር ለመኖር መርጠዋል ማለት ነው። «ቀድሞውንም ተኮንነዋል» ማለት ነው። ስለዚህ እነዚህ ሰዎች በመንፈስ ሙታን ናቸው። ከእግዚአብሔርም በረከት ስለራቁም፥ አንድ ቀን ቅጣታቸው ፍጻሜ አግኝቶ ለዘላለም በሲኦል ይጣላሉ። ነገር ግን ሰዎች በኢየሱስ ብቻ ካመኑ፥ የዘላለም ሕይወት አላቸው። ይህም ሕይወት ልዩ ሕይወት ነው፤ ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት የምናደርግበትና የእግዚአብሔርን ቤተሰብ ፍቅር የምንካፈልበት ሕይወት ነው። ይህንን ሕይወት ይበልጥ ሙሉ በሆነ በረከት የምንወርሰው በመንግሥተ ሰማይ ነው። ከሞት በኋላ ማንም ሰው ሁኔታን መለወጥ አይችልም። ሰ. በጥቅሉ ሲታይ ብዙ ሰዎች የዓለም ብርሃን የሆነውን ክርስቶስን አይቀበሉም። ለምን? ምክንያቱም ለእግዚአብሔር ለመገዛትና እርሱንም ለመታዘዝ ስለማይፈልጉ ነው። የእግዚአብሔርን «የብርሃን» መንገድ ጠልተው በኃጢአት ሕይወት ደስ ይሰኛሉ። አንድ ሰው ድነትን (ደኅንነትን) የሚያገኘው ጀርባውን ለኃጢአት ጽልመት ሰጥቶና ከዐመፅ ተለይቶ ወደ እግዚአብሔር ብርሃን ሲመለስ ብቻ ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ዮሐንስ 3፡16ን በቃልህ አጥና። ለ) ይህንን ጥቅስ መሠረት አድርገህ ወንጌል ምን እንደሆነ ከ50 በማይበልጡ ቃላት ጻፍ። ለአንድ ሰው ስለ ኢየሱስ ለመናገር 3 ደቂቃ ብቻ ቢሰጥህ፥ በኢየሱስ አምነው ለመዳን እንዲችሉ ምን ትነግራቸዋለህ? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ኢየሱስ አዲስ ልደት ምን እንደሆነ ለኒቆዲሞስ ገለጸለት (ዮሐ. 3፡1-21) Read More »

ኢየሱስ ነጋዴዎችን ከቤተ መቅደስ አባረረ (ዮሐ. 2፡12-25)

ኢየሱስ ሦስት አስፈላጊ ሃይማኖታዊ በዓሎች ላይ ለመገኘት ወደ ኢየሩሳሌም የሄደ ይመስላል። ዮሐንስ የሚያቀርባቸው ቀጣዮቹ ታሪኮችም በእነዚያ በዓላት ሰሞን የተካሄዱ ነበሩ። የመጀመሪያው በዓል ፋሲካ ነው። ከሦስት ዓመት በኋላ ኢየሱስ በዚህ ዕለት ይሞታል። ኢየሱስ በዚህ ዕለት በቤተ መቅደስ ውስጥ የነበረውን አምልኮ በተመለከተ ጊዜ ስግብግብ ነጋዴዎች አምላኪዎቹን ይበዘብዙና የአምልኮውም መንፈስ በእንስሳት ግዢውና በገንዘብ ልውውጡ ምክንያት በተፈጠረው ጩኸት ታውኮ ነበርና ልቡ በቁጣ ተሞላ። የገመድ ጅራፍ አበጅቶ እንስሳቱን እና ነጋዴዎቹን ከመቅደሱ አባረራቸው። ተመሳሳዮቹ ወንጌላት ኢየሱስ ነጋዴዎቹን ያባረረው በምድር ያለውን አገልግሎቱን ጨርሶ ከመምጣቱ ጥቂት ቀደም ብሎ እንደሆነ ሊያሳዩ፥ ዮሐንስ ግን በመጀመሪያው ላይ እንደሆነ አድርጎ ያቀርበዋል። ምናልባትም ኢየሱስ ሁለት ጊዜ፥ ማለትም በምድር አገልግሎቱ መጀመሪያና መጨረሻ ላይ፥ አድርጎት ሊሆን ይችላል። ይህ የኢየሱስ ድርጊት ሁለት ተቃራኒ ውጤቶችን አስከትሏል። አንደኛው፥ ለኢየሱስ ተከታዮች ከፍተኛ እምነትና መረዳት አስገኝቶላቸዋል። በዚህ ውስጥ በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ላይ መሲሑ ለእግዚአብሔር ቤት ስለሚኖረው ቅናት የተገለጸው ሲፈጸም አዩ። ሁለተኛ፥ ለማመን ያልፈለጉት ሰዎች፥ ኢየሱስ ይህንን ለማድረግ ሥልጣን እንዳለው የሚያረጋግጥ ልዩ ምልክት ከእግዚአብሔር እንዲሰጣቸው ጠየቁ። ምንም እንኳ ኢየሱስ ብዙ ተአምራትን ቢሠራም፥ የትኞቹም ቢሆኑ የሃይማኖት መሪዎቹን ለማሳመን በቂ አልነበሩም። ስለዚህ ኢየሱስ እርሱ መሲሑ መሆኑን ለማሳየት ወደ ሞቱና ትንሣኤው ብቻ አመለከታቸው ኢየሱስ ወደ ፈውስ ተአምራቱና አጋንንትን ወደ ማውጣቱ ተአምር አልጠቆማቸውም። ኢየሱስ ከሚፈጽማቸው ተአምራት ውስጥ በጣም ታላቁና የመሲሕነቱ የመጨረሻ ማረጋገጫ (ምልክት) ሞቱና ትንሣኤው ነበር። የውይይት ጥያቄ፡- እኛ እንዴት ነው አንዳንድ ጊዜ ኢየሱስ ከሞት በመነሣቱ ተአምር ይበልጥ ከመደሰት ይልቅ በፈውስ ተአምር ልንደሰት የምንችለው? ዮሐንስ የሕዝቡንም ምላሽ ገልጾአል። እነርሱ «በስሙ አመኑ።» «ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር፤ ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር፤ ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና» (ዮሐ 2፡24-25) ተብሎ ተነግሮናል። በዚህም ዮሐንስ ከሁለት ዓይነት እምነት ጋር አስተዋውቆናል። አሁን እንደተገለጸው ዓይነት ጥልቅ ያልሆነ፥ እኔነት የሞላበት እምነት አለ። በዚህ ዓይነቱ እምነት ሰዎች ኢየሱስን የሚከተሉት ከእርሱ ስለሚያገኙት ነገር ብለው ነው። ኢየሱስ እነርሱ የሚፈልጉትን ነገር እስካደረገ ድረስ፥ ሊከተሉት ፈቃደኞች ናቸው። ነገር ግን የጠበቁትን ወይም ስግብግብ ፍላጎታቸውን ካላሟላላቸው፥ እንዲህ ዓይነት እምነት ያላቸው ሰዎች ፈጥነው ኢየሱስን ይከዳሉ። ለዚህ ነው ኢየሱስ ስለ እምነታቸው ያልተደሰተው። ወደ በኋላ የምናየው ሌላ ዓይነት እምነትም አለ፥ በኢየሱስ ማንነት ላይ እርግጠኛ ሆኖ የተደላደለ እምነት። ይህም ምድራዊ በረከቶች ቢኖሩም ባይኖሩም በስደት ውስጥም እንኳ ቢሆን፥ የግለሰቡ እምነት ጽኑ ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በቤተ ክርስቲያናችሁ ውስጥ ያሉ አብዛኞቹ ሰዎች የትኛው ዓይነት እምነት አላቸው ብለህ ነው የምታስበው? ለ) ትክክለኛው ዓይነት እምነት እንዳለን ለማረጋገጥ እንዲረዳን ልባችንን እና ኢየሱስን የምንከተልበትን ምክንያት መመርመሩ አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ኢየሱስ ነጋዴዎችን ከቤተ መቅደስ አባረረ (ዮሐ. 2፡12-25) Read More »

የኢየሱስ የመጀመሪያው ምልክት፡- ውኃን ወደ ወይን ጠጅ ለወጠ (ዮሐ. 2፡1-11)

የኢየሱስ አገልግሎት ከይሁዳ ወደ ገሊላ ተሸጋገረ። ዮሐንስ ኢየሱስ በገሊላ ሳለ ስላጋጠመው ሁኔታ ብዙም የነገረን ነገር የለም። ሌሎች ተመሳሳይ ወንጌላት በገሊላ ላይ ሲያተኩሩ፣ ዮሐንስ ግን በይሁዳ ላይ ትኩረት አድርጓል። ኢየሱስ በገሊላ ሳለ ቤተሰቡና ደቀ መዛሙርቱ ለሰርግ ታድመው ነበር። እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ በአይሁዳውያንም ዘንድ ጋብቻ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶ ለአያሌ ቀናት የሚሰነብት ሥርዐት ነበር። ለእንግዳው ሁሉ የሚበቃ ምግብና መጠጥ አለማቅረቡ ደግሞ እንደ እኛው ሁሉ በአይሁድ ባሕልም አስነዋሪ ተግባር ነበር። እንዲህ ዐይነት ችግር የተከሰተበት ሰርግ ከዚያ በኋላ በቂ የወይን ጠጅ ባለማቅረቡ ሲፌዝበት ይሰነብት ነበር። ምናልባትም የኢየሱስ እናት የሆነችው ቅድስት ማርያም የሰርገኞቹ ዘመድ ወይም የቅርብ ወዳጅ ሳትሆን አትቀርም። ስለሆነም ወይኑ እንዳለቀ ስትሰማ ወደ ልጇ ዘወር ብላ ችግሩን ያስወግድላቸው ዘንድ አንድ ተአምር እንዲያደርግ ጠየቀችው። ለዚህ ጥያቄ ኢየሱስ የሰጠው ምላሽ ለእኛ ከረር ያለ ይመስላል። ነገር ግን ኢየሱስ ለእናቱ አክብሮት የጎደለው ምላሽ ሰጥቷል ማለቱ የማይመስል ነው። «አንቺ ሴት» የሚለው አገላለጽ ለድብ ሳይሆን፣ ሴቶችን መጥራት የሚቻልበት ሌላው መንገድ ነበር። ኢየሱስ ይህን ሲል ምን ማለቱ ነው? ለሚለው ጥያቄ የሚቀርቡ ሁለት መልሶች አሉ። አንደኛው፥ የወይኑ አለመኖር እኔንና አንቺን ለምን ያሳስበናል? ወይም ደግሞ በእኔና በአገልግሎቱ ላይ ምን ሥልጣን አለሽ? ማለቱ ነው። በዚህም ኢየሱስ በሁለት እውነቶች ላይ እያተኮር ሊሆን ይችላል። ሀ. የኃላፊነቱ ሥልጣን የኢየሱስ እንጂ የእናቱ አልነበረም። ኢየሱስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር የተለየ ግንኙነት ስለነበረው፥ ሊያደርግ የሚገባውን የሚነግረው እግዚአብሔር ነበር (ዮሐ 5፡36)። ይሁን እንጂ እግዚአብሔር ኢየሱስ ውኃን ወደ ወይን ጠጅ በመለወጡ የተአምር ተግባሩን እንዲጀምር አልነገረውም፡፡ ይህ ኢየሱስ ለእናቱ የተናገረው ቃል በሉቃስ 2፡49 ላይ ለወላጆቹ የአባቱ የሥራ ተካፋይ መሆን እንዳለበት ከተናገረው ጋር ተመሳሳይ ነበር። ለ. በሁለተኛ ደረጃ ፥ ኢየሱስ በጊዜው ላይ ትኩረት እያደረገ ነበር። ዮሐንስ በወንጌሉ ኢየሱስ፥ ውስን የጊዜ ሰሌዳ እንዳለውና አገልግሎቱም በመስቀል እንደሚደመደም ገልጾአል። በይፋዊ አገልግሎቱ ሁሉ ወደዚያው መስቀል እያመራ ነበር (ዮሐ 7፡6፣ 8፣ 30፤ 8፡20 እና 12፡23፣ 27፤ 13፡1፤ 16፡32፤ 17፡1።) ማርያም በመጠኑም ቢሆን ኢየሱስ ተአምር ሊሠራ እንዳለው አውቃለች፤ ምክንያቱም፣ ለአገልጋዮቹ ኢየሱስ የሚላቸውን እንዲያደርጉ ነግራቸዋለች። ኢየሱስም ለማንጻት ሥርዓት የሚሆን ውኃ የሚያጠራቅሙባቸውን ስድስት የድንጋይ ጋኖች ውኃ እንዲሞሏቸው አላቸው። ከዚያም ውኃው ወደ ወይን ጠጅ ተቀየረ። ዮሐንስ ይህንን የኢየሱስ የመጀመሪያ ተአምር «ምልክት» ይለዋል። ለመሆኑ ኢየሱስ በተአምሩ አማካይነት ሊያሳይ የፈለገው ምልክት ምንድን ነበር፥ ዮሐንስስ ይህንን ተአምር መጽሐፉ ውስጥ ለምን አካተተው? ብዙ አማራጮች አሉ። መጀመሪያ፣ አይሁዶች ስለ መሲሑ መምጣት ካሏቸው ትውፊቶች ውስጥ አንዱ ያ ጊዜ የመብልና ወይን የመጠጥ ወቅት ይሆናል የሚል ነው። አንዳንድ ምሑራን የውኃው ወደ ወይን ጠጅ መለወጥ መሲሑ ኢየሱስ አሁን በመካከላቸው እንዳለ የሚያሳይ ምልክት ነው ብለው ያስባሉ። ሁለተኛ፣ ምናልባትም የውኃው ወደ ወይን ጠጅ መቀየር የመለወጥ ምልክት ሊሆን ይችላል። ኢየሱስ ተራውን ውኃ ወደ ልዩ ወይን ጠጅ እንደለወጠው ሁሉ፥ እንዲሁ የተራ ሰዎችን ሕይወት ልዩ ሰዎች እንዲሆኑ፥ ባዶ ሕይወቶችን ወደ ሙሉ ሕይወቶች፥ እና ደስታ የለሽ ሕይወቶችን ወደ ደስተኛ ሕይወቶች ሊለውጥ ይችላል። ሐዋርያው ዮሐንስ ተአምሩ በተከናወነበት ስፍራ ሆኖ ይመለከት እንደነበረ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ ምክንያቱም ስለ ተአምሩ ብዙ ዝርዝር ጉዳዮችን ያውቃል፥ ይኸውም ምን ያህል ጋኖች እንደ ነበሩ፥ ጋኖቹ ምን ያህል ትልቅ እንደ ነበሩ፥ እና የድግሱ ኃላፊ ምላሽ ምን እንደ ነበረ። ዮሐንስ እንደሚነግረን የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ይህንን ተአምር በተመለከቱ ጊዜ ሁለት ነገሮች ሆኑ። አንደኛ፥ ተአምሩ የኢየሱስ ማንነት እና የክብሩ መገለጸ ነበር። ሁለተኛ፥ ደቀ መዛሙርቱ በኢየሱስ ላይ ያላቸውን እምነት የመጨመሩን ሂደት ጀመሩ፡፡ ስለ ኢየሱስ ብዙ ባወቁ ቀጥር፥ እምነታቸውም እያደገ ይመጣ ነበር። የምናምነውን የበለጠ ባወቅነው መጠን፣ እምነታችን ያድጋል። እምነታችን ደካማ ከሆነ፥ ይሄ የሚያመለክተው ስለ ኢየሱስና ስለ እግዚአብሔር አብ ያለን እውቀት ደካማ መሆኑን ነው። የውይይት ጥያቄ- ሀ) ኢየሱስን የበለጠ ባወቅኸው ጊዜ እምነትህ እንዴት አደገ? ለ) ይሄ አዳዲስ ክርስቲያኖች እምነታቸው እንዲያድግ ስለ ኢየሱስ በደንብ ማስተማር እንደሚያስፈልገን ምን ያስገነዝበናል? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የኢየሱስ የመጀመሪያው ምልክት፡- ውኃን ወደ ወይን ጠጅ ለወጠ (ዮሐ. 2፡1-11) Read More »

መጥምቁ ዮሐንስ ኢየሱስን ለመግለጥ ያደረገው አገልግሎት (ዮሐ 1፡19-51)

የውይይት ጥያቄ፡- ዮሐ 1፡19-2፡25 አንብብ ሀ) ይህ ክፍል ስለ ኢየሱስ ምን ይነግረናል? ለ) በኢየሱስ ስለ ማመንና እርሱን ስለ መከተል ምን እንማራለን? ሌሎች ወንጌላት ቀደም ብለው ይህንኑ እንዳደረጉ ስለሚያውቅ ሐዋርያው ዮሐንስ ስለ ኢየሱስ መጠመቅ አልጻፈም። ከዚህ ይልቅ መጥምቁ ዮሐንስ ስለ ኢየሱስ በሰጠው ምስክርነት ላይ አትኩሯል። ዮሐንስ ስለ ራሱና ስለ ኢየሱስ ማንነት ግልጽ ግንዛቤ ነበረው። ሀ. መጥምቁ ዮሐንስ ስለ ራሱ ለሃይማኖት መሪዎች የሰጠው መግለጫ ( ዮሐ 1፡19-28) መጥምቁ ዮሐንስ አይሁዶች «የምትመጣው መሢሕ አንተ ነህ ወይ?» በማለት በጠየቁት ጊዜ መልሱ «እኔ አይደለሁም» የሚል ነበር። መጥምቁ ዮሐንስ ኤልያስ አልነበረም። በሌሎች ወንጌላት ኢየሱስ መጥምቁ ዮሐንስን ኤልያስ እያለ ሲጠራ እንመለከታለን (ማቴ. 11፡13-14)። እንግዲህ ልዩነቱ ምንድን ነው? ምናልባትም የሚናገሩት ስለ ሁለት የተለያዩ ሰዎች ሊሆን ይችላል። በመጀመሪያ፣ ሞትን ሳይቀምስ ወደ ሰማይ የተወሰደ ኤልያስ የሚባል ነቢይ ነበር። አይሁዶች መሢሑ ሊመጣ ሲል ይህ ወደ ሰማይ ተወስዶ የነበረው ኤልያስ ተመልሶ ይመጣል ብለው ያምኑ ነበር። መጥምቁ ዮሐንስ እርሱ ወደ ሰማይ ተወስዶ የነበረው ኤልያስ እንዳልሆነ ገልጾላቸዋል። በኋላ ኢየሱስ ወደ ሚልክያስ 4፡5 በማመልከት ስለ ኢየሱስ ምጽአት የሚያውጅ ተምሳሌታዊ ኤልያስ እንደሚመጣ ገልጾላቸዋል። መጥምቁ ዮሐንስ ይሄኛው ኤልያስ ነው። መጥምቁ ዮሐንስ ነቢዩ አይደለም (ዘዳግ 18፡15፣ 18 አንብብ)። አይሁዶች ሙሴ አንድ ልዩ ነቢይ እንደሚመጣ እንደተነበየ ያውቁ ነበር። አይሁዶች ይህ ነቢይ ከመሢሑ የተለየ ነው ብለው ያስቡ ነበር። ሐዋርያው ዮሐንስ  በመጽሐፉ ከሚያሳያቸው ነገሮች መካከል አንዱ፥ ኢየሱስ መሢሕም ነቢይም እንደሆነ ነው። ስለሆነም ዮሐንስ ራሱን አይሁዶች ሲጠብቁ የኖሩት ነቢይ አድርጎ አላቀረበም። መጥምቁ ዮሐንስ ለመሢሑ መንገድ ለማዘጋጀት የተላከ መልእክተኛ ነበር። ከመሢሑ ጋር ሲነጻጸር፣ መጥምቁ ዮሐንስ የመሢሑን የጫማ ክሮች ለመፍታት እንደማይገባው ባሪያ ነበር። ለ. መጥምቁ ዮሐንስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር በግ እንደሆነ መስክሯል (ዮሐ 1፡29-34)። እግዚአብሔር በመሢሑ ላይ መንፈስ ቅዱስን በርግብ አምሳል እንደሚያወርድ ለመጥምቁ ዮሐንስ ገልጾለታል። ምንም እንኳ ጥምቀቱ ተለይቶ ባይገለጽም፣ መጥምቁ ዮሐንስ ርግብ በኢየሱስ ላይ ሲወርድ አይቷል። ነገር ግን ዮሐንስ ኢየሱስ ከፖለቲካዊ መሢሕ በላይ እንደሆነ ያውቅ ነበር። ስለዚህም ኢየሱስን «የእግዚአብሔር በግ» ሲል ጠርቶታል። ምሑራን ይህ ሐረግ ከብሉይ ኪዳን እንደ መጣ ቢያውቁም፣ ከየትኛው የብሉይ ኪዳን ክፍል እንደሆነ ይጠይቃሉ። ዮሐንስ አብርሃም ልጁን ለመሠዋት በሄደ ጊዜ፥ እግዚአብሔር ስለሰጠው በግ (ዘፍጥ. 22፡1-14) መናገሩ ይሆን? ወይስ ይህ ለመሥዋዕትነት የሚቀርበውን የፋሲካ በግ (ዘጸ 12፡1-11፣ 21) የሚያመለክት ይሆን? ምናልባት በኢሳ 53፡7 የተጠቀሰውን በግ ያመለክት ይሆን? ዮሐንስ የትኛውን ለማመልከት እንደፈለገ በግልጽ ባናውቅም፣ የመሥዋዕቱ አሳብ ግን በሚገባ የሚታወቅ ነው። በብሉይ ኪዳን ለኃጢአት ስርየት በግ ዋነኛው መሥዋዕት እንደ ነበረ ሁሉ፣ ኢየሱስም ለሰው ልጆች ኃጢአት የሚሞት መሥዋዕት ነበር። የእግዚአብሔር ፍጹም መሥዋዕት እንደ ሆኑ፤ ኢየሱስ ለአይሁዶች ብቻ ሳይሆን ለሰዎች ሁሉ ኃጢአት መሥዋዕት ሆኖ ይቀርባል። ሐ. ከመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ሁለቱ ኢየሱስን ተከተሉ (ዮሐ 1፡35-51)። የኢየሱስ የመጀመሪያ ደቀ መዛሙርት የመጡት ከየት ነበር? በገሊላ እርሱን ያገኙት ሰዎች ነበሩ? አልነበሩም። የመጀመሪያዎቹ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት የመጡት ከመጥምቁ ዮሐንስ ነበር። ኢየሱስ ከተጠመቀ ከጥቂት ቀናት በኋላ፣ መጥምቁ ዮሐንስ ኢየሱስ ሲያልፍ ተመለከተ። ከዚያም ወደ ደቀ መዛሙርቱ መለስ ብሎ፣ ለሁለተኛ ጊዜ ኢየሱስ የእግዚአብሔር በግ እንደሆነ ነገራቸው። ቀደም ሲል ኢየሱስ ከእርሱ እንደሚልቅ ገልጾላቸው ነበር። በዚህም ጊዜ ከመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ሁለቱ ተከተሉት። የዮሐንስ ወንጌል ከእነዚህ የመጀመሪያዎቹ ደቀ መዛሙርት መካከል የአንዱን ስም ብቻ ይነግረናል። እርሱም እንድርያስ ነው። ሁለተኛውስ ደቀ መዝሙር ማን ነበር? ምናልባትም ራሱ ሐዋርያው ዮሐንስ ላይሆን አይቀርም። በዚያኑ ዕለት እንድርያስ ወንድሙን ስምዖን ጴጥሮስን ወደ ኢየሱስ አመጣው። ጴጥሮስም የመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዝሙር ነበር። በመጥምቁ ዮሐንስ ምስክርነት ምክንያት እንድርያስ ኢየሱስ ተራ ሰው ሳይሆን መሢሕ እንደሆነ ተገንዝቦ ነበር። ጴጥሮስ ከኢየሱስ ጋር ሲገናኝ፣ ኢየሱስ ስሙን ኬፋ በማለት ለወጠው። የጴጥሮስ የመጀመሪያ ስሙ ስምዖን ነበር። ኢየሱስ ይህንን ስም ወደ ኬፋ (በአረማይስጥ) ወይም ጴጥሮስ (በግሪክ) ለወጠው። እነዚህ ሁለቱም ስሞች «ዓለት» የሚል ፍች አላቸው። ይህም ከኢየሱስ ትንሣኤ በኋላ ጴጥሮስ ከዋንኞቹ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች አንዱ እንደሚሆን ያመለክታል። እንድርያስ ለሌሎች ለመመስከር ምሳሌ ሆነ። ምስክርነቱ የተወሳሰበ አልነበረም። ያደረገው ነገር ቢኖር ለወንድሙ ስለ ኢየሱስ በመናገር ጴጥሮስ ከኢየሱስ ጋር እንዲገናኝ ማድረግ ነበር። በቀጣዩ ዕለት ተጨማሪ ደቀ መዛሙርት ወደ ኢየሱስ መምጣት ጀመሩ። በመቀጠል ኢየሱስ ወደ ራሱ የጠራው ደቀ መዝሙር ፊልጶስ ነበር። ፊልጶስ ኢየሱስን በመከተል ላይ እንደ ነበሩት ሌሎች ደቀ መዛሙርት ሁሉ የገሊላ ሰው ስለነበር፣ እርሱም የመጥምቁ ዮሐንስ ተከታይ ሳይሆን አይቀርም። ፊልጶስ ናትናኤል የሚባል ሰው አገኘ። ፊልጶስ ኢየሱስ ክርስቶስ የብሉይ ኪዳን ትንቢቶች ፍጻሜ እንደሆነ ተገንዝቦ ነበር። ናትናኤል ኢየሱስ ከናዝሬት ገሊላ እንደመጣ ሲሰማ ጥርጣሬ አደረበት። ገሊላ ብዙም ሃይማኖታዊ እንቅስቃሴ የማይታይባት ኋላቀር የእስራኤል ክፍል ነበረች። በእርሱ አስተሳሰብ መሢሑ ንጹሕና አጥባቂ አይሁዶች ከሚገኙበት የይሁዳ ክፍል መምጣት ነበረበት። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እንድርያስና ፊልጶስ በዚህ ታሪክ ውስጥ የምስክርነት ምሳሌዎች ሆነው የቀረቡት እንዴት ነው? ለ) ብዙ ክርስቲያኖች ምስክርነት የወንጌላውያን ኃላፊነት እንደሆነ አድርገው የሚያስቡት እንዴት ነው? ሐ) ይህ ክፍል ምስክርነት ከሁላችንም እንደሚጠበቅ የሚያሳየው እንዴት ነው? ኢየሱስ ከናትናኤል ጋር በተገናኘ ጊዜ ለመጀመሪያ ጊዜ ተራ ሰው ሳይሆን መለኮታዊ አምላክ እንደሆነ አሳይቷል። ይህንንም ያደረገው ከሰዎች ጋር በአካል ላይገናኝ ልባቸውን እንደሚያውቅ በመግለጹ ነው። ኢየሱስ ከዚህ በፊት ከናትናኤል ጋር ተገናኝቶ ባያውቅም፣ አምላክ ስለሆነ “እውነተኛ እስራኤላዊ” መሆኑን ተረድቶ ነበር። ይህም ናትናኤል በሥጋ ብቻ ሳይሆን በመንፈስም እስራኤላዊ ሰመሆን እግዚአብሔርን ይወድ እንደ ነበር ያመለክታል። ይህ ናትናኤልን አስደንቆታል። ከዚያ በኋላ ግን ኢየሱስ በአካል ባይኖሩም ሰዎች የሚያደርጓቸውን ነገሮች ለማወቅ እንደሚችል አሳይቶታል። ኢየሱስ ናትናኤል ከበለስ በታች ሲቀመጥ በሥጋዊ ዐይኑ ባይመለከትም፣ ሁሉን አዋቂ አምላክ በመሆኑ ይህ ችሎታ ነበረው። ይህ ችሎታ ናትናኤልን ስላስደነቀው በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ስለ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅነት ሊመሰክር በቅቷል። በዚህ ጊዜ ኢየሱስ ከዚህ የሚበልጥ ታያለህ ሲል፤ ወደፊት ተጨማሪ ተአምራትን እንደሚያይ ገልጾአል። ነገር ግን ኢየሱስ ለናትናኤል «ሰማይ ተከፍቶ መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያለህ» ሲል ምን ማለቱ ነበር? ይህ ለመረዳት የሚያስቸግር አገላለጽ ነው። አንዳንድ ምሑራን ምናልባት ናትናኤል ከዛፍ ሥር ተቀምጦ መላእክት ከሰማይ በመሰላል ሲወጡና ሲወርዱ የሚያሳየውን የአብርሃምን ሕልም ታሪክ እያነበበ ሳይሆን እንደማይቀር ይገምታሉ። በዚህ ጊዜ ኢየሱስ እርሱ በሰማይና ምድር መካከል እንደ መሰላል የሚያገለግል መሆኑን እየተናገረ ነበር። ከእርሱ ጋር ባላቸው ግንኙነት፣ ተአምራቱን መመልከታቸው፣ ትምህርቱን መስማታቸውና ሞቱንና ትንሣኤውን መመልከታቸው የመንግሥተ ሰማይን ምሥጢራት ሁሉ እንደ መረዳት ነበር። እንደ መንፈሳዊ መሰላል፣ ኢየሱስ እግዚአብሔርን ለደቀ መዛሙርቱ ይገልጥላቸዋል። የደቀ መዛሙርቱንም ፍላጎቶች ለእግዚአብሔር ያስተላልፋል። ዮሐንስ በተጨማሪም ከእግዚአብሔር ርቃ ከተቅበዘበዘችው የቀድሞዋ እስራኤል (ያዕቆብ) በተቃራኒ ፍጹም እስራኤል እንደሆነ እያመለከተ ነበር። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

መጥምቁ ዮሐንስ ኢየሱስን ለመግለጥ ያደረገው አገልግሎት (ዮሐ 1፡19-51) Read More »

የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ (ዮሐ. 1-18)

አንድ ጊዜ፣ «ኢየሱስ ክርስቶስ መኖር የጀመረው ከመቼ ጀምሮ ነው? የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው መቼ ነው?» የሚል ጥያቄ ለቤተ ክርስቲያናችን መሪ አቀረብሁለት። ይህ የቤተ ክርስቲያን መሪ ወዲያው በማቴዎስና ሉቃስ ወንጌል ውስጥ ስለተጠቀሰው የኢየሱስ ታሪክ አስታወሰ። «መኖር የጀመረው ከማርያም ከተወለደበት ጊዜ አንሥቶ ነው። እግዚአብሔር በማርያም ማኅፀን ውስጥ ሳለ ሕይወትን ስለ ሰጠው እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ ነው» ሲል መለሰልኝ። ብዙ ሰዎች ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ፥ የገና በዓል በመጣ ቁጥር ኢየሱስ በተአምር ከማርያም መወለዱን የሚያመለክት ታሪክ እንናገራለን። ምንም እንኳ ስለ ወደፊቱ ማሰብ ቢቀልለንም፣ ያለፈውን ጊዜ እንደዚያ ማሰቡ ቀላል አይሆንም፡፡ ስለሆነም እግዚአብሔር በተለይም ኢየሱስ ክርስቶስ ሁልጊዜ የመኖሩን አሳብ መረዳቱ አስቸጋሪ ይሆንብናል። ነገር ግን አእምሮአችን ስለ ወደፊቱ ረጅምና ከእግዚአብሔር ጋር አብረን ስለምንኖርበት ጊዜ እንደሚያስብ ሁሉ፣ ወደ ኋላም በመመልከት እግዚአብሔር ፍጻሜ የሌለው አጀማመር እንደነበረው መረዳት ይኖርብናል። ዮሐንስ ስለ ኢየሱስ ሕይወት የጻፈውን ይህንን መግቢያ የጀመረው በዚሁ ፍጻሜ በሌለው አጀማመር ሁኔታ ነው። ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት ትክክለኛ ግንዛቤ ለማግኘት ዮሐንስ ስለ ኢየሱስና እንዴት ከእርሱ ጋር ኅብረት ልናደርግ እንደምንችል የሚናገረውን መረዳት ይኖርብናል። የውይይት ጥያቄ፡- ዮሐ 1፡1-18 አንብብ። ሀ) ዮሐንስ የኢየሱስን መለኮታዊ ባሕርይ እንዴት እንደሚገልጽ ዘርዝር። ለ) የኢየሱስን ሰብአዊ ባሕርይ የሚገልጹትን ነገሮች ዘርዝር ሐ) ዮሐንስ ስለ ድነት (ደኅንነት) ምን እንደሚያስተምር ዘርዝር። በዚህ ክፍል ዮሐንስ ከኢየሱስና ከመጥምቁ ዮሐንስ ጋር ያስተዋውቀናል። በተጨማሪም የኢየሱስን ሕይወት፣ ሞትና ትንሣኤ ውጤቶች ይገልጽልናል። ዋና ዋና ትምህርቶቹ ሁሉ በዚህ ክፍል ተጠቅሰዋል። ዮሐንስ በኢየሱስ ሕይወት አማካይነት የሚያስተምረውን አሳብ ለመረዳት፣ ይህንን መግቢያ ማወቅ ይኖርብናል። ሀ. ኢየሱስ ዘላለማዊ የእግዚአብሔር ቃል ነው (ዮሐ 1፡1-2)፡፡ ዮሐንስ የኢየሱስን ታሪክ የጀመረው ከመጀመሪያው ነው። የምን መጀመሪያ? ይህ ኢየሱስ በማርያም ማሕፀን ውስጥ ከመፀነሱ በፊት ያለው ጊዜ አይደለም። እግዚአብሔር ነገሮችን ሁሉ የፈጠረበት መጀመሪያም አይደለም። ዮሐንስ የሚናገረው ከዘላለም ዘመናት በፊት ስለነበረው ጊዜ ነው። ሰዎች ማሰብ እስከሚችሉበት ድረስ እንኳን ወደ ኋላ ቢመለሱ ኢየሱስ እንደ ነበር ዮሐንስ ያስረዳል። ዮሐንስ መጀመሪያ ብሎ የሚጠራው ይህንን ጊዜ ነው። ነገር ግን ኢየሱስ መጀመሪያ የለውም። ዮሐንስ ኢየሱስን ቃል (ወይም በግሪክ ሎጎስ) በማለት የጠራው ለምንድን ነው? ለዚህ ሁለት አማራጮች አሉ? አንደኛው፥ አይሁዶች በብሉይ ኪዳን ላይ ተመሥርተው ይህንን አሳብ ሊረዱ ይችሉ ነበር። በብሉይ ኪዳን “የእግዚአብሔር ቃል” በተለያዩ መንገዶች አገልግሏል። አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር በሥራ ላይ መሆኑን ያመለክታል። በፍጥረት ጊዜ ሁሉም ነገር የተፈጠረው ከእግዚአብሔር አፍ በወጣው ቃል ነበር (ዘፍ. 1፡3፣6)። ስለሆነም እግዚአብሔር አንድን ነገር ለማድረግ በሚፈልግበት ጊዜ፥ በአብዛኛው ነገሮች የሚከውነው ከአፉ በሚወጣው ቃል ነው [መዝ. (119)፡25፣ (105)፣ (169)]። አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን መግለጹን ያመላክታል (1ኛ ሳሙ. 3፡21)። ስለሆነም ዮሐንስ ይህንን የተለየ ስም ለኢየሱስ ሲሰጥ፥ ኢየሱስ የፍጥረት እንደራሴ እንደሆነ መግለጹ ነው። (ማስታወሻ፡ በአዲስ ኪዳን ለኢየሱስ ይህንን ስም የተጠቀመው ዮሐንስ ብቻ ነው።) በተጨማሪም ኢየሱስ እግዚአብሔር ነገሮችን ለመግለጽ የመረጠበት መንገድ ነው። ለዚህ ነው ዮሐንስ እኔን ያየ አብን አይቷል የሚለው (ዮሐ 14፡9)። የዕብራውያን ጸሐፊ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ፍጹም ነጸብራቅ፣ የመጨረሻና ከሁሉም የላቀ መገለጥ እንደሆነ አመልክቷል (ዕብ 1፡3)። ቃል ለሚለው አገላለጽ ሁለተኛው አማራጭ ከግሪኮች የተገኘ ነው። ይህ ግሪኮች ለዓለም ምክንያትና ዓላማ በመስጠት ወደ ልዩ ፍጻሜ ስለሚመራው አመክኒዮአዊ መርሕ የሚሰጡት ስያሜ ነበር። ዓለም በዕድል ሳይሆን በእግዚአብሔር ትመራለች። እግዚአብሔር ዓለምን በጥበቡ አማካይነት ንድፍ በመንደፍ፣ በመፍጠር፣ በመደገፍና አስቀድሞ ወደ ወጠናቸው ዕቅዶች በመምራት ያስተዳድራታል። ስለሆነም ዮሐንስ ለግሪክ አንባብያኑ ኢየሱስ ዓለምን ለመፍጠር የእግዚአብሔር እንደራሴ ብቻ ሳይሆን፥ ታሪክና ፍጥረት ሁሉ ፈቃዱን እንዲፈጽሙ የሚመራቸው መሆኑን አመልክቷል። የውይይት ጥያቄ፡- እነዚህ ሁለት ስለ «ቃል» የተነገሩን ነገሮች ኢየሱስን በተሻለ ሁኔታ እንድናውቀው የሚረዱን እንዴት ነው? ለ. ኢየሱስ አምላክም ከአብም የተለየ ነው። ዮሐንስ ኢየሱስ ቃል በመሆኑ በመጀመሪያው ይኖር እንደነበርና አምላክ በመሆኑ ደግሞ፥ ከእግዚአብሔር አብ የተለየ መሆኑን ገልጾአል። «የኢየሱስ ብቻ» (Only Jesus) እምነት ተከታዮች ኢየሱስና እግዚአብሔር አብ አንድ መሆናቸውን ቢናገሩም፣ ኢየሱስ አምላክ ቢሆንም፥ ከእግዚአብሔር አብ እንደሚለይ በዚህ ክፍል በግልጽ መገንዘብ ይቻላል። የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን አባቶች የሥላሴን ጽንሰ አሳብ እንዲመሠርቱ ካደረጉት ጥቅሶች አንዱ ይኼ ነበር። ሥላሴ አንዱ አምላክ በሦስት አካላት (አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ) እንደሚገለጽ የሚያስረዳ ትምህርት ነው። ሐ. ኢየሱስ የፍጥረት ሁሉ እንደራሴ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ሦስቱም የሥላሴ አካላት አባላት በፍጥረት ሥራ ላይ እንደ ተካፈሉ ያሳያል። እዚህ ላይ ትኩረት የተሰጠው በኢየሱስ ድርሻ ላይ ነው። ዮሐንስ ኢየሱስ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድና ከዚያም በኋላ በተፈጠሩት ሰዎችና ነገሮች አፈጣጠር ላይ ተሳታፊ እንደ ነበር ገልጾአል። መ. ኢየሱስ የሕይወት ምንጭ ነው። ሕይወት ላላቸው ነገሮች ሁሉ የሚያስፈልገውን አካላዊ ሕይወትና በተለይም በእርሱ ለሚያምኑ መንፈሳዊ ሕይወትን የሚሰጠው እርሱ ነው። ዮሐንስ ከሚወዳቸው ቃላት አንዱን በመጠቀም የኢየሱስን የሥራ ውጤቶች ይገልጻል። ይህም የዘላለም ሕይወት መስጠቱ ነው። ዮሐንስ ይህንን ቃል ከ40 ጊዜ በላይ የጠቀሰው ሲሆን፣ ይህም በተለይም ኢየሱስ በእርሱ ለሚያምኑት ሰዎች ስለሚሰጠው ሕይወት የሚያመለክት ነው። በኋላም ኢየሱስ እርሱ ሕይወት እንደሆነ ይገልጻል ( ዮሐ 14፡6)። በተጨማሪም ኢየሱስ ሰዎችን ከሞት ስለሚያስነሣ የትንሣኤ ሕይወት ምንጭ ነው (ዮሐ 11፡25-26)። ሠ. ኢየሱስ የብርሃን ምንጭ ነው። ዮሐንስ በቀዳሚነቱ የሚናገረው ስለ መንፈሳዊ ብርሃን ነው። ይህም በዮሐንስ 24 ጊዜ የጠቀሰው ሌላው ተወዳጅ ቃል ነው። ዮሐንስ ወደ በኋላ ኢየሱስ የዓለም ብርሃን እንደሆነ የተናገረውን አሳብ ያቀርባል (ዮሐ 8፡12)። በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ ብርሃን ሁለት ፍችዎች አሉት። በዚህ ስፍራ ብርሃን የሚለው ቃል ኢየሱስ የመንፈሳዊ ብርሃን ወይም የመንፈሳዊ መረዳት ምንጭ መሆኑን የሚያመለክት ይመስላል። ኢየሱስ እግዚአብሔርንና ፈቃዱን ለሰዎች ይገልጣል። ይህ ዳዊት የእግዚአብሔር ቃል የእግሬ መብራት ነው ካለው እሳብ ጋር ይመሳሰላል [መዝ. 119፡105]። ዮሐንስ ኢየሱስ የዘላለምን ሕይወት መንገድ እንደሚያበራና ሰዎች ግን እርሱንም ሆነ የሚሰጣቸውን ብርሃን እንዳልተገነዘቡ አመልክቷል። ብዙውን ጊዜ ይህ ብርሃን የሚለው ቃል ከጨለማ ጋር እየተነጻጸረ ቀርቧል። ጨለማ ክፉውን ዓለም፣ በእግዚአብሔር ላይ የሚሰነዘረውን ተቃውሞና ሰይጣን የሚቆጣጠረውን ሕይወት አቅጣጫ ያመለክታል። ብርሃን ከዚህ በተቃራኒው ለእግዚአብሔርና ለቃሉ መታዘዝን ያመለክታል። ረ. መጥምቁ ዮሐንስ ኢየሱስ ብርሃን እንደሆነ መሰከረ። አንዳንድ ምሑራን ከመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርት መካከል የመጥምቁ ድርሻ ምን እንደሆነና ከኢየሱስ ጋር እንዴት እንደሚዛመድ ያላወቁ ሰዎች ስለነበሩ፥ ሐዋርያው ዮሐንስ ይህንን ችግር ለማስወገድ እንደፈለገ ያስባሉ። ሐዋርያው ዮሐንስ መጥምቁ ዮሐንስ ሰዎችን ብርሃን ወደነበረው ኢየሱስ ያመለከተ ምስክር መሆኑን ገልጾአል። (ማስታወሻ፡ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን የተለያዩ ሰዎች እንደመሰከሩ የሚያስረዳው ሌላው የዮሐንስ ተወዳጅ ቃል «ምስክር» የሚለው ነው።) እውነተኛው የድነት (የደኅንነት) ብርሃን ኢየሱስ ብቻ ነው። ደማቅ ብርሃን በጨለማ ውስጥ መንገድን እንደሚመራ ሁሉ፣ መጥምቁ ዮሐንስ እንደ ብርሃን ወደ ኢየሱስ ያመለክት ነበር። ሰ. ብዙሃኑ ሕዝብ ቃል የሆነውን ኢየሱስን አልተቀበሉትም። ዮሐንስ ሰዎች ለኢየሱስ የሰጧቸውን የተለያዩ ምላሾች አመልክቷል። ሕዝቡ ኢየሱስን እንደ አዳኝ ባይቀበለውም፣ ኢየሱስ ለመስጠት የመጣውን የዘላለም ሕይወት አምነው የሚቀበሉ ጥቂቶች ነበሩ። ኢየሱስ ዓለምን የፈጠረ ቢሆንም፣ አሁን ወደ ዓለም የመጣው እንደ ሰብአዊ ሰው ነበር። የፈጠራቸው ሰዎች ግን ኢየሱስ ፈጣሪያቸው ወይም አዳኛቸው እንደሆነ አላወቁም ነበር። ሸ. በኢየሱስ ያመኑ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆናሉ። ኢየሱስ ልዩ የእግዚአብሔር ልጅ ነው። የኢየሱስን ያህል መለኮታዊ ማንነት ያለው ማንም የለም፡፡ (ይህ ሁላችንም አማልክት ነን ከሚለው የአዲሱ ዘመን ትምህርት ይለያል።) ነገር ግን ዮሐንስ በኢየሱስ የሚያምኑ ሰዎች የእግዚአብሔር ቤተሰብ አባላት እንደሆኑ ገልጾአል። ይህም የእግዚአብሔር ልጆች ያደርጋቸዋል። (ማስታወሻ፡ በኢየሱስ ስም ማመን ማለት በኢየሱስ ማመንን የሚያመለክት የአይሁዶች አገላለጽ ነው። ስም የስሙን ባለቤት ያመለክታል) መንፈስ ቅዱስ አዲስ ልደት ስለሰጣቸው ከእግዚአብሔር ተወልደዋል። በዮሐንስ ምዕራፍ 3 ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ ስለ መንፈሳዊ ልደት ከሰጠው ማብራሪያ ወደፊት ስለዚሁ ጉዳይ ሰፋ አድርገን እንመለከታለን። ቀ. ኢየሱስ

የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ (ዮሐ. 1-18) Read More »

የዮሐንስ ወንጌል መዋቅር እና አስተዋጽኦ

፩. የዮሐንስ ወንጌል መዋቅር በትምህርት ቤት ጥሩ ጽሑፍ ለማዘጋጀት መግቢያውን፥ ፍሬ ነገሩንና መደምደሚያውን በሚገባ ማዋቀር እንዳለብን አስተማሪዎቻችን ይነግሩናል። የዮሐንስ ወንጌልም በዚህ መንገድ የተዘጋጀ ነው። መግቢያ (ዮሐ 1፡1-18)። የነገረ መለኮት ምሑር የሆነው ዮሐንስ፥ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ እያስተማረ ነበር። በመሆኑም በመግቢያው ላይ ቃል የተባለው ኢየሱስ ከዘላለም ዘመናት በፊት ከእግዚአብሔር አብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ወደ ነበረበት ጊዜ ይወስደናል። አስደናቂው ሁኔታ ይህ ዘላለማዊ አምላክ ሥጋን በመልበስ በፍጥረቱ መካከል እንደ ሰው ኖረ። ዮሐንስ የኢየሱስን ሕይወት ያጠቃለለው በጥቂት ዐረፍተ ነገሮች ነው። የእርሱ ወደሆኑት፣ ማለትም ወደ አይሁዶች ወይም ወደ ሰዎች ሁሉ ቢመጣም፣ እንደ አምላካቸው አውቀው አልተቀበሉትም። ነገር ግን የክርስቶስን አምላክነት ተረድተው በእምነት የተከተሉት ጥቂት ሰዎች ነበሩ። እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ለመሆን በቅተዋል። ፍሬ ነገር፤ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው የኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወት፣ ሞትና ትንሣኤ (ዮሐ 1፡19-20፡31)። ዮሐንስ መጽሐፉን የጻፈበት ዓላማ ሰዎች ኢየሱስን እንደ እግዚአብሔር ልጅ አምነው እንዲቀበሉት መሆኑን ገልጾአል። በዮሐ 1፡10-19፡42 ላይ ዮሐንስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ የሚያሳዩ ምልክቶችንና ትምህርቶችን አቅርቧል። ከዚያም ዮሐንስ ዋንኛ የመረጃ አካሉን ከ13-20፡31 ይቀጥላል። ይህ ክፍል ኢየሱስ በሞቱ እንዴት እንደ ከበረ የሚያመለክት በመሆኑ፣ ምሑራን «የክብር መጽሐፍ» ብለው ይጠሩታል። መደምደሚያ፤ ጴጥሮስ የኢየሱስን ይቅርታ ተቀበለ (ዮሐ 21)። ጴጥሮስና ዮሐንስ የቅርብ ጓደኛሞች ነበሩ። ብዙውን ጊዜ በወንጌላትም ሆነ በሐዋርያት ሥራ ውስጥ፥ ለምሳሌ ያህል፣ የሐዋ. 3) አብረው ተጠቅሰዋል። በዚህ ክፍል ዮሐንስ፥ ኢየሱስን ሦስት ጊዜ የከዳውን ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ በመጥራት የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን መሪ እንዲሆን እንዳበረታታው ያስረዳል። በዚህ ታሪክ፣ ዮሐንስ አንዳንድ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ዮሐንስ ከመሞቱ በፊት ይመለሳል በማለት የተናገሩትን የተሳሳተ አሳብ ተቃውሟል። ፪. የዮሐንስ ወንጌል አስተዋጽኦ መግቢያ፤ (ዮሐ ፡1-18) የኢየሱስ ይፋዊ አገልግሎት፣ የኢየሱስ ምልክቶችና ይፋዊ ትምህርቶች (ዮሐ 1፡19-12፡50) ሀ. የመጥምቁ ዮሐንስ ምስክርነት (ዮሐ 1፡19–34) ለ. ኢየሱስ በመጀመሪያ ከጥቂት ደቀ መዛሙርት ጋር ተገናኘ (ዮሐ 1፡35-51) ሐ. የኢየሱስ የመጀመሪያው ምልክት፤ ውኃን ወደ ወይን ጠጅ መለወጥ (ዮሐ 2፡1-11) መ. ኢየሱስ ቤተ መቅደሱን አጸዳ (ዮሐ 2፡12-25) ሠ. ኢየሱስ ከኒቆዲሞስ ጋር እንደ ተነጋገረ (ዮሐ 3) ረ. ኢየሱስ ከሳምራዊቷ ሴት ጋር ተነጋገረ (ዮሐ 4፡1-42) ሰ. የኢየሱስ ሁለተኛው ምልክት፡- ኢየሱስ የሹሙን ልጅ ፈወሰ (ዮሐ 4፡43-54) ሸ. የኢየሱስ ሦስተኛው ምልክት፡- ኢየሱስ በኢየሩሳሌም አንድ በሽተኛ መፈወሱና ለለ ራሱ ያቀረበው ትምህርት (ዮሐ 5) ቀ. የኢየሱስ አራተኛውና አምስተኛው ምልክት፡- ኢየሱስ አምስት ሺህ ሰዎችን መገበ፤ በውኃ ላይ ተራመደ፥ አስተማረ ዮሐ 6) በ. ኢየሱስ በመገናኛው ድንኳን በዓል ላይ አስተማረ ዮሐ 7-8) ተ. የኢየሱስ ስድስተኛው ምልክት፡- ኢየሱስ ዐይነ ስውሩን ፈወሰ፥ አስተማረ (ዮሐ 9) ቸ. መልካሙ እረኛ ኢየሱስ ከሃይማኖት መሪዎች ጋር ተከራከረ (ዮሐ 10) ኀ. የኢየሱስ ሰባተኛው ምልክት፡- ኢየሱስ አልዓዛርን ከሞት አስነሣ፥ አስተማረ (ዮሐ 11) ነ. ኢየሱስ ለመጭው ሞቱ ሲዘጋጅ፡- በድል ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱና በማርያም መቀባቱ (ዮሐ 12) የኢየሱስ ይፋዊ ያልሆነ አገልግሎት፡- ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን አስተማረ (ዮሐ 13-17) ሀ. ኢየሱስ ፋሲካን ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በላ (ዮሐ 13) ለ. ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን ለመጭው ሞቱ አዘጋጀ (ዮሐ 14-16) ሐ. ኢየሱስ ለራሱና ለደቀ መዛሙርቱ ወደ እግዚአብሔር አብ ጸለየ (ዮሐ 17) የኢየሱስ መታሰር፡- መመርመርና የጴጥሮስ ክህደት ዮሐ 18) ኢየሱስ ለዓለም ኃጢአት እንደ ፋሲካ በግ ሞተ (ዮሐ 19) የኢየሱስ ትንሣኤ (ዮሐ 20) ኢየሱስ ከትንሣኤ በኋላ ደቀ መዛሙርቱን አገለገለ (ዮሐ 21) ሀ. ኢየሱስ 153 ዓዎችን በማስገኘት የፈጸመው ተአምር (ዮሐ 21፡1-14) ለ. ኢየሱስ ጴጥሮስን ለተልዕኮ አሰማራ (ዮሐ 21፡15-25) (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የዮሐንስ ወንጌል መዋቅር እና አስተዋጽኦ Read More »

የዮሐንስ ወንጌል ልዩ ገጽታዎች

፩. ዮሐንስ ከመጽሐፉ አብዛኛውን ክፍል ያዋቀረው፥ ሰባት ሰባት ነገሮችን ባካተቱ ሁለት ምድቦች ከፋፍሎ ነው። ሀ. ሰባት ምልክቶች፡- ማርቆስ ኢየሱስ የፈጸማቸውን ተአምራት (ለምሳሌ፣ ፈውስ) የኃይል መግለጫዎች ወይም ተአምራት ብሎ ሲጠራ፣ ዮሐንስ ግን «ምልክቶች» ማለትን መርጧል። ምልክት ወደ ሌላ ነገር የሚያመላክት ክስተት ነው። ኢየሱስ የፈጸማቸው ተአምራት ሁሉ መለኮታዊነቱንና መሢሕነቱን የሚያሳዩ ነበሩ። ብዙዎቹ ምልክቶች ደግሞ የማስተማሪያ አጋጣሚዎች ነበሩ። ኢየሱስ የታመመውን ሰውዬ ከፈወሰ በኋላ፥ ከእግዚአብሔር ጋር እኩል በመሆኑ በሰንበት ላይ ሥልጣን እንዳለው ገልጾአል። አምስት ሺህ ሰዎችን እንጀራ ከመገበ በኋላም እርሱ መንፈሳዊ እንጀራ እንደሆነ አስተምሯል። ዮሐንስ ሰባት ምልክቶችን ዘርዝሯል:- ውኃን ወደ ወይን መለወጥ (ዮሐ 2፡1-11)። የሹሙን ልጅ መፈወስ (ዮሐ 4፡46-54)፡፡ በቤተ ሳይዳ መጠመቂያ፥ ለሠላሳ ስምንት ዓመት ታሞ የኖረ ሰው መፈወስ (ዮሐ 5፡1-15)፡፡ አምስት ሺህ ሰዎችን መመገብ (ዮሐ 6፡1-15)፡፡ በውኃ ላይ መራመድ (ዮሐ 6፡16-21)፡፡ ዐይነ ስውሩን መፈወስ (ዮሐ 9፡1-7)፡፡ አልዓዛርን ከሞት ማስነሣት (ዮሐ 11፡17-44)፡፡ የውይይት ጥያቄ፡- ዘጸአት 3፡14-15 አንብብ። እግዚአብሔር ስሙ ምንድን ነው? አለ። ምን ማለት ይመስልሃል? ለ. ሰባቱ የ«እኔ ነኝ» ዐረፍተ ነገሮች፡- አይሁዶች እጅግ ከሚያከብሯቸው የእግዚአብሔር ስሞች አንዱ፥ እግዚአብሔር በሲና ተራራ ለሙሴ የሰጠው ነው። ለአይሁዶች ይህ እጅግ የተቀደሰ ስም በመሆኑ ለመጥራት አይደፍሩም ነበር። ዛሬም እንዴት እንደሚጠራ በትክክል አይታወቅም። አንዳንዶች ያህዌ ሊሉ (ይሄኛው በይበልጥ ትክክል ይመስላል)፣ ሌሎች ደግሞ ጄሆቫ ብለው ይጠሩታል። «እኔ እኔ ነኝ» የሚለው ስም እግዚአብሔር በራሱ ሕያው እንደሆነ ያመለክታል። ለህልውና ወይም ለመኖር በማንም ወይም በምንም ላይ አይደገፍም። ከቶውንም ሳይለውጥ ሁልጊዜ በእርሱነቱ ይኖራል። እርሱ የተስፋ ቃሎቹን ለመፈጸም በሕዝቡ ፈንታ የሚሠራ አምላክ ነው። ስለሆነም ዛሬ ከእኛ ጋር የሚሠራው ከአብርሃም ጋር የሠራው እግዚአብሔር ነው። በዮሐ 8፡58 ላይ ኢየሱስ ከአብርሃም በፊት «እኔ ነኝ» ብሏል። ይህንን ሲናገር አይሁዶች ኢየሱስ የብሉይ ኪዳኑ የቃል ኪዳን አምላክ ነኝ እያለ መሆኑን ስለተገነዘቡ ሊገድሉት ፈለጉ። ኢየሱስ ስለ ባሕርዩ ቁልፍ እውነቶችን ለማሳየት ሲል ስሙን ታላቁ «እኔ ነኝ» ወደሚል አሳድጓል። ከእነዚህም መካከል ዮሐንስ ሰባቶቹን ዘርዝሯል:- እኔ የሕይወት እንጀራ ነኝ – የመንፈሳዊ ምግብ ምንጭ (ዮሐ 6፡35)። እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ – የመንፈሳዊ ብርሃን ምንጭ (ዮሐ. 8፡12)። እኔ በር ነኝ – ከእግዚአብሔር ጋር የሚደረግ ግንኙነት መንገድ (ዮሐ 10፡7)። እኔ መልካም እረኛ ነኝ – ለእግዚአብሔር ሕዝብ ፍላጎቶች የቆመ (ዮሐ 10፡11)። እኔ ትንሣኤና ሕይወት ነኝ – በመጀመሪያም ሆነ ከሞት በኋላ ሕይወትን የሚሰጥ (ዮሐ 11፡25)። እኔ መንገድ፣ እውነትና ሕይወት ነኝ – የእውነት ሁሉና የዘላለም ሕይወት ምንጭ ወደሆነው እግዚአብሔር አብ ለመቅረብ ብቸኛ መንገድ (ዮሐ 14፡6)። እኔ እውነተኛው የወይን ግንድ ነኝ – የበረከትና ከእግዚአብሔር ጋር የሚደረግ ግንኙነት ምንጭ (ዮሐ 15፡1)። ፪. ዮሐንስ፣ ሰዎች ከኢየሱስ ጋር ያደረጓቸውን የተለያዩ ቃለ ምልልሶች አቅርቧል። አንድ ሰው እንደ ገለጸው፣ በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ ሰዎች ከኢየሱስ ጋር ያካሄዱቸው 27 ቃለ ምልልሶች አሉ። ለአብነት ያህል፣ የኒቆዲሞስ፤ የሳምራዊቷ ሴት፣ የተፈወሰው ሰውዬና የሌሎችም ግለሰቦች ቃለ ምልልሶች ቀርበዋል። ፫. ምንም እንኳ ማቴዎስ፣ ማርቆስና ሉቃስ ከ20 ዓመታት በፊት ተጽፈው ለቤተ ክርስቲያንና ለዮሐንስ አገልግሎት ይሰጡ እንደ ነበር ባይጠረጠርም፣ ከዮሐንስ ወንጌል ውስጥ 90 በመቶው በሌሎች ወንጌሎች ውስጥ አይገኝም። ዮሐንስ ስለ ኢየሱስ ብዙ ተጨማሪ ነገሮችን ሊጽፍ ይችል እንደ ነበርና ኢየሱስ ያደረጋቸውን ነገሮች በሙሉ የሚይዙ መጻሕፍት እንደማይኖሩ ገልጾአል ዮሐ 21፡25)። ፬. ተመሳሳይ ወንጌላት፥ ኢየሱስ ብዙ ምሳሌዎችን ተጠቅሞ እንዳስተማረ ቢናገሩም፣ በዮሐንስ ውስጥ አንድም ምሳሌ አልተጠቀሰም። ይህም ሆኖ ዮሐንስ ኢየሱስ አሌግሪ የሚባል ሌላ ዐይነት ዘዴ እንደተጠቀመ አመልክቷል። ምሳሌ ከሕይወት ገጠመኝ የሚመነጭ ታሪክ ሲሆን፣ አሌጎሪ ግን በኢየሱስና በሌላ ነገር መካከል አነጻጻሪ ሆኖ የሚቀርብ ምሳሌ ነው። ለምሳሌ፡- ኢየሱስ ራሱን በር፣ የወይን ግንድ፣ መልካም እረኛ በማለት ጠርቷል። ፭. ዮሐንስ በሌሎች ወንጌላት ውስጥ ያልተጠቀሱትን ብዙ ነገሮች ገልጾአል። ከእነዚህም መካከል የዳግም ልደት ትምህርት፣ ኢየሱስ የሕይወት ውኃ መሆኑ፣ ኢየሱስ የሕይወት እንጀራ መሆኑ ተጠቅሰዋል። ፮. የዮሐንስ ወንጌል ከማንኛውም የአዲስ ኪዳን መጽሐፍ በላይ ስለ መንፈስ ቅዱስ አገልግሎት ዓላማ ያብራራል። በዮሐ 14-16 ላይ የሚገኘው ትምህርት መንፈስ ቅዱስ በኢየሱስ ክርስቶስና በእግዚአብሔር አብ እንዴት እንደሚላክ ይናገራል። የመንፈስ ቅዱስ አገልግሎት ትኩረት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። በመሆኑም መንፈስ ቅዱስ ሰዎችን ወደ ኢየሱስ በማምጣት፣ በኢየሱስ የሚያምኑትን ሰዎች በማስተማርና በኢየሱስ ማመን ማለት ምን ማለት እንደሆነ ለደቀ መዛሙርቱ በማስገንዘብ ያገለግላል። ፯. ዮሐንስ መንፈሳዊ እውነቶችን ለመግለጽ ተቃራኒ ቃላትን ይጠቀማል። ብዙውን ጊዜ፣ ብርሃንና ጨለማ፣ ከላይና ከታች፣ እውነትና ሐሰት፣ ሕይወትና ሞት፣ ፍቅርና ጥላቻ፣ ሕግና ጸጋ፣ መንፈሳዊ ልደትና ሥጋዊ ልደት፣ እንዲሁም ማመንና አለማመንን ጠቅሷል። ዮሐንስ ከሚወዳቸው ሌሎች ቃላት መካከል ሥራ፣ ዓለም፣ ሥጋ፣ ሰዓትና መቀበል፣ ፍቅር፣ እውነት፣ ማወቅ፣ ክብርና ምስክርነት ይገኙባቸዋል። ፰. ማቴዎስና ሉቃስ ጽሑፎቻቸውን የጀመሩት የኢየሱስን መፀነስና መወለድ በሚገልጹ ትረካዎች ሲሆን፣ ዮሐንስ መጽሐፉን የጀመረው ከዘላለም ዘመን ሲሆን ቃል ለዘላለም ከእግዚአብሔር ጋር ከነበረበት ጊዜ ይጀምራል። ዮሐንስ የኢየሱስን ዘላለማዊ ህልውና በመግለጽ ለሰብአዊ ሕይወቱ መድረክ ይከፍታል። ይህም ዮሐንስ ካቀረበው የፍጹም ሰብአዊነቱ ገለጻ ባሻገር፥ ኢየሱስ አምላክ እንደሆነ እንድንገነዘብ ይረዳናል። ፱. ሦስቱ ተመሳሳይ ወንጌላት ያተኮሩት በገሊላ ውስጥ በተፈጸሙት ጉዳዮች ላይ ሲሆን፣ ዮሐንስ በሰማርያና በይሁዳ ኢየሱስ ያከናወናቸውን አገልግሎቶች ገልጾአል። ፲. ዮሐንስ በመጽሐፉ የሰዎችን ማመንና አለማመን አመልክቷል። አንደኛው፥ ሰዎች በኢየሱስ ያምኑ ነበር። ይህ ግን ሰዎች ኢየሱስ የሚያስፈልጋቸውን ነገሮች እስካሟላ ድረስ መሢሕ መሆኑን ለመቀበል የሚፈቅዱበት ጥልቀት የሌለው እምነት ነበር። ሁለተኛው፣ በኢየሱስና በሃይማኖት መሪዎች መካከል የማያቋርጥ ግጭት/አለማመን ይካሄድ ነበር። ይህ አለማመን ወደ ሌሎችም አይሁዶች ይተላለፍ ጀመር። እነዚህ ሁለት ጉዳዮች እስከ ምዕራፍ ስድስት ከቀጠሉ በኋላ፥ ድንገተኛ የአቅጣም ለውጥ ይከሰታል። ግጭቱና አለማመኑ እስከ መስቀል ሞት ድረስ እያደገ የሚሄድ ሲሆን ኢየሱስ ከሰዎች የሚጠብቃቸው ነገሮች እየከበዱ ሲሄዱና ከመሢሑ የሚጠብቋቸውን የራስ ወዳድነት ፍላጎቶች ሳያሟላ ሊቀር፥ በኢየሱስ ላይ የነበራቸው እምነት እየቀነሰ ሊሄድ ችሏል። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የዮሐንስ ወንጌል ልዩ ገጽታዎች Read More »