ባለፉት የመጀመሪያዎቹ አሥር ሳምንታት ትምህርታችን ውስጥ ያጠናነው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር። በቀሪዎቹ አሥር ሳምንታት ደግሞ ኢየሱስ ለእኛ ደኅንነትን በማምጣት ስለፈጸመልን ሥራ እናጠናለን። ስለዚህ ኢየሱስ ስለሚሰጠን ደኅንነት አስፈላጊነት በማጥናት ትምህርቱን እንጀምራለን። ሰዎች ኃጢአተኞች ስለሆኑ ኢየሱስ የሚሰጣቸው ደኅንነት ያስፈልጋቸዋል። ኃጢአተኞች ሆነው ከመወለዳቸው በተጨማሪ፥ ሁሉም በሕይወት ዘመናቸው ኃጢአትን ይፈጽማሉ። ኃጢአት ሞትንና ከእግዚአብሔር መለየትን ያመጣል። በዚህና በሚቀጥለው ሳምንት፥ ከኃጢአታችንና ከእግዚአብሔር ከመለየታችን የተነሣ በከፍተኛ ሁኔታ እዳኝ እንደሚያስፈልገን እንማራለን። ኃጢአት ምንድን ነው? ኃጢአት ምን እንደሆነ መገንዘባችን በጣም ጠቃሚ ነው። ስለ ኃጢአት ምንነት የሚኖረን ግንዛቤ፥ ስለ እግዚአብሔር ማንነት፥ ስለ ሰዎችና ስለ ደኅንነት ምንነት ከሚኖረን መረዳት ጋር የተዛመደ ነው። እግዚአብሔርን ሕዝቡም ልክ እንደ እርሱ እንዲሆኑ የሚፈልግ በጣም ንጹሕና ቅዱስ አምላክ አድርገን ካሰብን፥ ሕጉንና ለባሕሪው የሚበጀውን በትንሹ መተላለፍ እንኳን ከባድ ሆኖ ይሰማናል። በአንጻሩ እግዚአብሔር ከእኛ የራቀና ስለ እኛ ሕይወትም ግድ የሌለው አድርገን ከወሰድነው፧ በዚህ አስተሳሰባችን ረገድ ኃጢአት ለእኛ ይህን ያህል ከባድ ነገር ሊሆንብን አይችልም። ሰዎች በመሠረቱ መልካም ናቸው የምንል ከሆነ ኃጢአት ሊያመጣቸው የሚችለውን አባዜ ራሳቸው በራሳቸው ሊወጡት ይችላሉ እንደ ማለት ነው። ሆኖም ሰዎች በመሠረቱ ክፉዎች ከሆኑ ኃጢአት ሊያስከትልባቸው የሚችለውን ፍዳ ለማሸነፍ አዳኝ ይሻሉ። ሰዎች ለሚያደርጉት ተጠያቂዎች መሆን ካለባቸው፥ ኃጢአታቸው በእግዚአብሔር ፊት ከባድ ይሆናል። ሁላችንም ኃጢአት ምን እንደሆነ በሚገባ ካልተገነዘብን በስተቀር ጠንካራ ክርስቲያኖች ሆነን ለማደግና ሌሎችንም ለማገልገል አንችልም። ስለ ኃጢአትና ስለ ደኅንነት ምንነት ለማጥናት ስንነሣ በመጀመሪያ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ኃጢአት ምንነት በሚሰጠው ትምህርት መጀመር ይገባል። 1. ኃጢአት እግዚአብሔር ወደሚፈልገው ደረጃ መድረስ አለመቻል ነው። ጥያቄ – ኃጢአት ምንድን ነው የሚለውን ጥያቄ የምታውቃቸው ሰዎች እንዴት ይመልሱታል? ስለ ኃጢአት ምንነት ሰዎች የተለያዩ አሳቦች አሉዋቸው። አንዳንድ ሰዎች ኃጢአት የቤተሰባቸውን ወይም የኅብረተሰባቸውን ሰላም የማናጋት ሁኔታ መሥራት ይመስላቸዋል። ይህ አድራጎታቸው በአካባቢያቸው ያሉትን ሰዎች የሚያስቸግር እስከሆነ ድረስ ይህን ያህል ጉዳት የለበትም ብለው ያምናሉ። ሌሎች ደግሞ ስለ ኃጢአት ምንነት ሲያስረዱ፣ ሌሎች ሰዎች መጥፎ ነው ብለው የሚያስቡትን ሁሉ ማድረግና በዚህም ተግባር ወንጀለኛ ሆኖ መያዝ ኃጢአት ነው ባይ ናቸው። ምንም ነገር ያድርጉ ተግባራቸው በሌሎች ሰዎች ተደርሶበት እስካልተያዙ ኃጢአት እንደ ሠሩ አያምኑም። ከዚህ ለየት የሚሉት ምክንያት አቅራቢዎች ደግሞ፥ ኃጢአት ማለት የእግዚአብሔርን ሕግ የሚጥስ ተግባር መፈጸም ነው ሲሉ ያስባሉ። እንደ እነርሱ እምነትም በውጫዊው ሁኔታዎች የእግዚአብሔርን ሕግ የሚታዘዙ እስከ መሰላቸው ድረስ፥ ኃጢአት ሠርተናል ብለው አያስቡም። የሰዎች አስተሳሰብ ይህ ሲሆን፥ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ኃጢአት ምንነት እንዴት ያስተምረናል? በዕብራይስጥ ለኃጢአት የተሰጠው ቃል «ኃቻታ» (hachata) የሚል ሲሆን፥ ይህም «ኃጢአት» ከሚለው የአማርኛ ቃል ጋር የተዛመደ ነው። የዚህ ቃል መሠረታዊ ትርጉም፤ «ዒላማን መሣት» (miss the mark) ማለት ነው። የግሪኩ ትርጉም ደግሞ ኃጢአትን «ሐማርቲያ» (hamatia) ይለዋል። የዚህም ትርጉም፥ «ዒላማን መሣት» የሚል ነው። የእነዚህ ቃላት መሠረታዊ ትርጉሞች ለመገንዘብ ቃል በቃል የተጠቀምንባቸውን ሁለት የምንባብ ክፍሎች ቀጥለን እንመለከታለን። ጥያቄ፡- መሳፍንት 20፡16 እንብቡ። ሀ) ከቢንያም ነገድ የሆኑ 700 ሰዎች ምን አደረጉ? ለ) ምሳሌ 19፡2 አንብቡ። አንድ ሰው ችኩል ቢሆን ምን ይደርስበታል? በመጽሐፈ መሳፍንት 20፡16 እና በምሳሌ 19፡2 ላይ ለኃጢአት በዕብራይስጡ የቃል በቃል አጠቃቀም ተቀምጦ እንመለከታለን። በዚሁ በመጽሐፈ መሳፍንት 20፡16 እንደተጻፈው፥ ከቢንያም ነገድ የሆኑ 70 ሰዎች በወንጭፍ ድንጋይ ሲወረውሩ ሌላው ቀርቶ «ጠጉር የማይስቱ ነበሩ» ይላል። እነዚህ ሰዎች ያነጣጠሩበትን ዓላማ አይስቱም ነበር። በምሳሌ 19፡2 ደግሞ፥ «ጥድፊያም መንገድን ያስታል» ይላል። እነዚህ ጥቅሶች ኃጢአትን መፈጸም ምን እንደሆነ የመጀመሪያውን አሳብ ይሰጡናል። ኃጢአትን ማድረግ ማለት፥ እግዚአብሔር ያስቀመጠውን ዒላማ መሳት ነው። እግዚአብሔር የወሰነልንን ያመለከተንን መንገድ መሣትም ነው። ኃጢአትን መፈጸም ማለት እግዚአብሔር በሚፈልገው ደረጃ ላይ አለመገኘት ማለት አይደለም። ኃጢአት ሲባል፥ ዒላማን መሳት ነው ብለን በምናስብበት ጊዜ አንደ ድንጋይ ወንጫፊ ዓላማውን ለመምታት ወርውሮ እንደሚስት ሁሉ፡ እግዚአብሔር ወደሚፈልግብን ደረጃ ለመድረስ ጥረት አድርገን ከደረጃ ወ ሳንደርስ እንደ መቅረት አድርገን ብቻ እንወስደው ይሆናል። ያለጥርጥር ኃጢአት የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ለመፈጸም ሞክረን ሳይሆንልን መቅረትንም ይጨምራል። ነገር ግን የኃጢአት ትርጉም፥ «ዒላማ ለመምታት ሞክሮ መሳት» ብቻም አይደለም። አንድ ሰው ሆን ብሎ በተሳሳተ ዒላ ላይ በማነጣጠር ዒላማ መሳቱንም ደግሞ ያጠቃልላል። አንድ ሰው ትክክለኛ ያልሆነውን መንገድ በመምረጡ ምክንያት ትክክለኛውን መንገድ ሳተ ማለት ነው። አንዳንድ ጊዜ የእግዚአብሔር ትእዛዝ ለእኛ ምን እንደሆነ እያወቅን ዳሩ ግን በራሳችን ምርጫ ትእዛዙን እናፈርሳለን። ይህ ኃጢአት ነው። በሌላ ሁኔታ ደግሞ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ አናውቅ ይሆናል፥ ነገር ግን አውቀን አለመታዘዝን እንመርጣለን። ይህም ደግሞ ኃጢአት ነው። ኃጢአት ማለት የእግዚአብሔርን ደረጃ ልንደርስበት በምናደርገው ጥረትም ሆነ ፈልገንና አውቀን ዒላማውን ስንስት ነው። 2. ኃጢአት የእግዚአብሔርን ሕግ መጠበቅ አለመቻል ነው። ኃጢአት በምንፈጽምበት ጊዜ ምን ደረጃ እናጣለን? ኃጢአት የእግዚአብሔርን የሞራል ሕግ ዒላማ በሥራችን፣ ስዝንባሌያችንና በባሕርያችን መምታት ሲያቅተን ነው። ጥያቄ፡- 1ኛ ዮሐንስ 3፡4 አንብቡ። እንደ ዮሐንስ አጻጻፍ ኃጢአት ምንድን ነው? ጥያቄ፡- ሮሜ 2፡12፤ 4፡15 አንብቡ። ሀ) ጳውሎስ «ከሕግ በታች ስላሉት ብሎ ሊል ስለ እነማን መናሩ ይመስላችኋል? ለ) እነዚህ ከሕግ በታች ያሉ ፍርዳቸውን እንዴት ይቀበላሉ? ሐ) ሐዋርያው ጳውሎስ «ሕጉ ላይኖራቸው» ብሎ ሊናገር ስለ እነማን መግለጹ ነው? መ) ታዲያ «ሕግ ሳይኖራቸው» የተባሉት እንዴት ፍርዳቸውን ይቀበላሉ? መሠረታዊ የሆነ የኃጢአት ምንነት ትርጉም የሚገኘው በ1ኛ ዮሐንስ 3፡4 ውስጥ ነው። በዚህ ጥቅስ ኃጢአት «ዓመፅ» መሆኑ ተገልጾአል። እንዲህም ማለት ኃጢአት የእግዚአብሔርን ሕግ መጠበቅ አለመቻል ነው። የእግዚአብሔር ሕግ ሊባል ደግሞ አሥርቱ ትእዛዛት ብቻ ማለትም አይደለም። የእግዚአብሔር ሕግ ማለት የእግዚአብሔር ክቡርና ቅዱስ ምግባር ማለት ነው። ከእነዚህ ደረጃዎች ጥቂቶቹ በአሥርቱ ትእዛዛትና በተቀሩት የብሉይ ኪዳን ሕግጋት ውስጥ ተገልጠዋል። ነገር ግን ይህ የብሉይ ኪዳን ሕግ የእግዚአብሔር ፍጹማዊ የሞራል ሕግ ብቸኛው መገለጫም አይደለም። በመሆኑም አዲስ ኪዳንም ስለ እግዚአብሔር ደረጃዎችና ስለ ሞራል ሕጉ በርካታ ምሳሌዎችን አካትቶአል። ሰዎች ሁሉ፥ ብሉይም ይሁን አዲስ ኪዳን ቢኖራቸውም ባይኖራቸውም፥ ስለ እግዚአብሔር የሞራል ሕግ በልባቸውና በአእምሮአቸው የሚያውቁት ነገር አላቸው። ጳውሎስ በሮሜ ምዕራፍ 2 ላይ አይሁዶችም ሆኑ አሕዛብ ይህን የእግዚአብሔር የሞራል ሕግ እንደ መጠበቃቸው መጠን ፍርዳቸውን ይቀበላሉ ይላል። በሮሜ 2፡12 አይሁዶች «ከሕግ በታች ያሉ» ይላቸዋል። ምክንያቱም እግዚአብሔር የብሉይ ኪዳንን ሕግ ለአይሁዶች ሰጥቷቸዋልና ነው። አሕዛብን ደግሞ «ሕጉ ሳይኖራቸው» በማለት የብሉይ ኪዳን ሕግ እንደ ተሰጣቸው ያብራራል። ሆኖም ጳውሎስ አያይዞ ሁለቱም አይሁድም ሆኑ አሕዛብ የእግዚአብሔርን የሞራል ሕግ በጠበቁበት መጠን ፍርዳቸውን ይቀበላሉ ሲል ይናገራል። አይሁዶች የእግዚአብሔር የሞራል ሕግ መግለፃ ብሉይ ኪዳን ባይኖራቸውም፤ የእግዚአብሔር የሞራል ሕግ በልባቸው አለ። ያልተጻፈ ሕግ በልቦናቸውና በአእምሮአቸው ውስጥ አለ። የእግዚአብሔርን የሞራል ሕግ ሲጥሱ ሕሊናቸው ይወቅሳቸዋል፥ ደግሞም የእግዚአብሔርን የሞራል ሕግ በሚጠብቁበት ጊዜ ደስ እንዲሰኙ ያደርጋል። ስለዚህም አሕዛብ እንኳን ስለ እግዚአብሔር ሕግ መሠረታዊ የሆነ ግንዛቤ አላቸው። በመሆኑም እግዚአብሔር የሞራል ሕጉን በጠበቁበት መጠን ፍርዳቸውን ይሰጣቸዋል። አይሁድም ሆኑ ኦሕዛብ የእግዚአብሔርን የሞራል ሕግ ያውቃሉ። ስለዚህ አይሁድ ቢሆንም አሕዛብ የእግዚአብሔርን የሞራል ሕግ ባይጠብቁ ኃጢአት ይፈጽማሉ። ሌላው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የእግዚአብሔርን ሕግ ሳይፈጽሙ ስለ መቅረት የሚገልጸው ቃል «መተላለፍ» የተባለው ነው። ይህም ዘርዘር ሲደረግ፥ «ሕጉን መጣስ፥ ደረጃን ማለፍ፥ መግደፍ ማለት ይሆናል»። ጥያቄ፡- ሮሜ 4፡5 እንብቡ። ሕግ ከሌለ ሌላ ምን ይጎድላል? ጥያቄ፡- ሮሜ 2፡23 እንብቡ። ምንም እንኳን አይሁድ የእግዚአብሔርን ሕግ ተቀብለናል ብለው ቢመኩም፥ ምን የፈጸሙት ተግባር አለ? ጥያቄ፡– ዕብራውያን 2፡2 አንብቡ። «በመላእክት የተነገረውን መልእክት» የጣሱት ምን ሆኑ? ሮሜ 4፡15 እንደሚናገረው ሰው ሕግን ሲጥስ ያኔ ሕግን ይተላለፋል። ሕግ ባይኖር ኖሮ ሕግን መተላለፍ ባልኖረም ነበር። ነገር ግን ሕግ ባለበት በዚያ ያንን ሕግ የጣሰ ሁሉ ሕግ ተላላፊ ይሆናል ማለት ነው።